07/21/2026
በዚህ ሳምንት 49 ዓመት ሞላኝ። በሚቀጥለው ዓመት ደግሞ 50 እገባለሁ። መጽሀፈ መክብብን ባነበብኩ ቁጥር እንደ ሰሎሞን ልቤ ይጠይቃል፤ “ዘመኖቻችንን እንዴት እንደምንቆጥር አስተምረን፤ ጥበበኛ ልብ እንድናገኝ” ይላል።
ዛሬ: ከ25 ዓመት በፊት በናይሮቢና በካኩማ ስደተኞች መጠለያ: ኬንያ ነበርኩ። ወጣት: የነብር ጣት: ያኔ 25 ዓመት ለእኛ ዘላለም ይመስለን ነበር። እግራችን አይደክምም፣ ሕልማችን አያልቅም፣ ነገም በጣም ሩቅ ይመስለን ነበር። ግን ዘመን እንደ ወንዝ አለፈ። በየቀኑ ፍጥነቱን አላሳየም፤ 25 ዓመታት ግን በአንድ ትንፋሽ አለፉ። ዛሬ ወደ ኋላ ስመለስ፣ ያለፈው ሕይወት እንደ ሕልም ይታየኛል፤ የደስታው፣ የሐዘኑ፣ የድሉ፣ የሽንፈቱ፣ የጓድኝነቱና የመለያየቱ ድምፅ እንደ ሩቅ አያስተጋባ ይሰማኛል። አሁን አንድ ጥያቄ ብቻ ከልቤ አይወጣም። ቀጣዩን 25 ዓመት እንዴት ልኑረው?
መጽሐፍ እንደሚለው፣ የሰው ልጅ ዘመን ሰባ፣ ቢበዛ ሰማኒያ ዓመት ነው። ከዚያ በላይ ጸጋ ነው። ግን ድካምም ነው። ይህን ሳስብ፣ ድንገት ብኖር: የሚቀጥለው ሩብ ምዕተ ዓመት አጭርም ይመስለኛል፣ ከባድም ይሆንብኛል። አሁን ባለው መልኩ ኖሬ ጡረታ ልውጣ? ልነግድ? ልጻፍ? ልጓዝ? ቤት ልስራ? ልፖትልክ? ወይስ በየቀኑ ፈጣሪ የሚሰጠኝን ጊዜ በእንዴት አይነት መልኩ ልኑርበት? ዛሬ የሚያስጨንቀኝ: ጊዜ ነው። አጭርም ረጅም የሚመስል ጊዜ ነው: ቀጣዩ 25 አመት።
ገንዘብ ቢጠፋ ሊመለስ ይችላል፤ ጤናም ቢዳከም ሊሻሻል ይችላል። ያለፈ ጊዜ ግን ፈጽሞ አይመለስም። የሚመጣውስ ጊዜ እንዴት ይሰላል: ይሳላል: ይመተራል: ይኖራል?
ዕድሜ ሲገፋ ሰው አዲስ ነገር ከመጨመር ይልቅ አላስፈላጊውን መቀነስ ይማራል። ጓደኞቹ ይመረጣሉ፤ ሕልሞቹ ይጠራሉ፤ ፍላጎቶቹ ይጠበባሉ። በመጨረሻም ሁለት ጥያቄዎች ብቻ ይቀራሉ: “እኔ ማን ሆኜ ነበር?” "ቀጣዮቹን አመታትስ ማን ልሁን?"
ከሁሉ በላይ የሚያስፈራኝ ሞት አይደለም። ኑሮ እንጂ። ቀጣዩን 25 አመት እንዴት ልኑረው?
ሰዎች የሚሞቱት በመቃብር ብቻ አይደለም፤ ሕልማቸውን ሲተዉ፣ ተስፋቸውን ሲያጡ፣ እውነታቸውን ሲሸሹም ይሞታሉ። ፈጣሪ ቢፈቅድ ከ25 ዓመት በኋላ ይህንን ጽሑፍ እንደገና አነበዋለሁ። ልክ የዛሬ 25 አመት ኬንያ ሆኜ: ይሄን ዘመን እንዳላሰብኩት: በዚያ ቀን የዛሬን እኔን እንዴት አየዋለሁ?
“ምነው ጊዜን በተሻለ መንገድ ተጠቅሜበት በነበር!” ወይስ…“ፈጣሪ የሰጠኝን ዘመን በተገቢው ኖሬዋለሁ።” ስለዚህ: የቀረኝን ዘመን ትርጉም የሚሰጠው ምንድን ነው? ትሬጉሜ ብትንትን አለ። እንዴት ልተልመው? እንዴትስ ልሳለው? ምክንያቱም መጪው 25: ልክ እንዳለፈው 25 ዓመት በድንገት ያልፋል። እንደ ትላንት ይሆናል። ከዚያም ዛሬን ወደ ኋላ እያየን እንነጋገራለን።
ስለዚህ … እስኪ፣ ከልብ ምከሩኝ። ማለትም: ሀሳብ ስጡኝ: መጪውን 25 አመት እንዴት ልኑረው? "አግባ: ውለድ: ባታገባም ውለድ" አትበሉኝ። እስኪ 25 አመቱን ተመኙልኝ። ተቀኙልኝ። ተንብዩልኝ። ተርጉሙልኝ። ምክንያቱም ሰው ሕይወቱን በዓመታት አይለካውም። በትርጉሙ ነው የሚለካው። እስኪ መጪውን 25 አመታት የምኖርበት ሀሳብ አዋጡ። ተርጉሙልኝ። መልካም ልደት ለኔ። wow 49 አመት።
Obbo Dereje Dadi የዛሬ 24 አመት: Nairobi ያነሳው photo ነው።