22/08/2026
ሰሞኑን ሰው ለማስታመም በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ተገኘሁ ። የሚታየው ነገር ሁሉ ህመም ላይ ይጥላል ።
የኤምአርአይ ፣ ሲቲስካን ፣ ኤክስሬይ ፣ አልትራሳውንድ ፣ የኩላሊት እጥበት ፣ የጨረር ህክምና መስጫ መሳሪያዎች በአንድ ጊዜ ብዙ ሺ ታካሚዎችን ስለሚያስተናግዱ በተለያየ ጊዜ ይበላሻሉ ።
በፅኑ ህሙማን ክፍል ተኝተው የሚታከሙ ታካሚዎች እነዚህን ምርመራዎች ለማድረግ ለሰአታት ወረፋ ይጠብቃሉ።
በመኝታ ክፍል ህንፃ ፡ ታካሚዎች ፣ ሀኪሞች ፣ አስታማሚዎች እንዲመላለሱበት ከተሰሩት ሊፍቶች ውስጥ የሚሰራው አንድ ብቻ ነው። እርሱም ለሊፍት አንቀሳቃሹ ሰው ከውስጥ በቀዳዳ የፎቅ ቁጥር በጩኸት እየተነገረው ነው የሚቆመው።
ለህክምና አገልግሎት አሰጣጥ አያመችም ። ከፅኑ ታካሚዎች ጋር አብረው የሚንቀሳቀሱ የመተንፈሻ መሳሪዎችንና የመሳሰሉትን ለመጫን ያዳግታል ። ቢበላሽ በሰከንዶች መዘግየት ምክንያት ህይወት ሊጠፋ ይችላል።
ዊልቸር ለማግኘት ከፎቅ ፎቅ መመላለስና ሌላ ታማሚ እስኪለቅ ለደቂቃዎች መጠበቅ ግድ ይላል ።
መድኃኒት ከቤቱ መድኃኒት ቤት ማግኘት ሱሚ ነው ፣ በብዙ ሺ ብሮች ከአስታማሚ ኪስ እየወጣ የሚገዛው ከውጪ ነው ። የእጅና የፊት መሸፈኛ ጭንብሎችን ጨምሮ ከፕላስተር አቅም ሆስፒታሉ አያቀርብም ፤ ለመግዛት ወደ ውጪ ሩጫ ነው ።
የሚታዘዙ መድኃኒቶችን ለመግዛት አንድ አስታማሚ ብቻ ያለው ሰው ገንዘቡ ቢኖረው እንኳን ውጪ ሄዶ እስኪመለስ ታካሚው አደጋ ላይ ሊወድቅ ይችላል ።
ገንዘብ የሌለው ሰው ከሌሎች አስታማሚዎች በሚገኝ የገንዘብ እርዳታና ለእነርሱ ታማሚ በተገዛ ትርፍ መድኃኒት ያዘግማል ። ቅሪታቸውን አሟጠው መኖሪያቸውን ሸጠው የሚያሳክሙም አልጠፉም ። አለፉ ሲልም ጥለው የሚጠፉ አስታማሚዎች አሉ።
ሆስፒታሉ የማይሰጣቸው የደም ምርመራ እና የማሽን ህክምናዎችም አሉ ።
ጤና መድህን ለሌለው ሰው የአልጋ እና የቀዶ ጥገና አገልግሎት ክፍያ እንኳን ከአስርና መቶብሮች ወደ ብዙ ሺ ብሮች ተመንድጓል ።
በዚህ ሁሉ ፈተና ውስጥ ግን የህክምና ባለሙያዎቹ ወገናቸውን ለማገልገል የሚያደርጉት ጥረት የሚመሰገን ነው ።
ይህንን ችግር እያሰብኩ መስኮት ዳር ቆሜ መቆዘም ያዝኩ ። ካለሁበት ጥቂት ኪሎሜትሮች ርቀት ላይ በሚገኘው ግዮን ሆቴል ውስጥ ብዙ ቢሊዮን ብሮች ወጥቶበት የተሰራው ሰው ሰራሽ የውሃ ፏፏቴ ሽቅብ እየተምዘገዘገ ቁልቁል እየወረደ በሙዚቃ ስልት በቀለማት አሸብርቆ ይደንሳል ።
ከዚህ ሀሳብ ሽንቴ ቀሰቀሰኝና ወደ መፀዳጃ ቤት አመራሁ ። ለመፀዳጃ ቤቱ
የተቀመጠው በርሜል ውሃ የለውም ። ከቧንቧ ውሃ ማግኘት የማይታሰብ ነው ።ግዴታ ለመጠቀም እሽግ ውሃ ይዤ መመለስ ነበረብኝ ።