በደቡብ ኦሞ ዞን ፍትህ መምሪያ የፍትሀብሄር ፍትህ አስተዳደር ዋና የስራ ሂደት

  • Home
  • Ethiopia
  • Jinka
  • በደቡብ ኦሞ ዞን ፍትህ መምሪያ የፍትሀብሄር ፍትህ አስተዳደር ዋና የስራ ሂደት

በደቡብ ኦሞ ዞን ፍትህ መምሪያ የፍትሀብሄር ፍትህ አስተዳደር ዋና የስራ ሂደት የስራ ሂደቱን አገልግሎት ማስተዋወቅ እና በተለያዩ የህግ ጉ?

18/02/2025
21/02/2021

Fitsum Yitsedal
# # # # በሰው አካል ላይ ጉዳት የማድረስ ወንጀል ከባድ ወይም ቀላል የአካል ጉዳት ወንጀል መሆኑ ስለሚመዘንበት አግባብና የሰበር አቋም # # # #
የኢፌድሪ የወንጀል ህግ በምዕራፍ ሁለት ከአንቀጽ 553 እስከ 560 ድረስ በሰው ልጅ አካልና ጤና ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎችን የተደነገጉ ሲሆን በተለይም ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነኝን ከባድ አካል ጉዳት ማድረስ ወንጀል አንቀጽ 555 እና ቀላል አካል ጉዳት ማድረስ ወንጀል አንቀጽ 556ን የፌደራል ጠቅላይ የፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ በችሎት በቅጽ 24 ሰ/መ/ቁ ላይ ከወሰነው አስገዳጅ ትርጉም አንጻር ለመዳሰስ ወደድኩ።
አንቀጽ 553 (1) ላይ በመርህ ደረጃ ማንም ሰው አስቦ ወይም በቸልተኛነት በማናቸውም ነገር ወይም ዘዴ የሌላውን ሰው አካል ያጎደለ ወይም ጤንነቱን የጎዳ እንደሆነ በሰው አካል ወይም ጤና ላይ ጉዳት በማድረስ ወንጀል እንደሚቀጣ ይደነግጋል። ከዚህም መረዳት የሚቻለው ....በማንኛውም ነገር ወይም ዘዴ የአካል ጉዳቱ የተፈጸመ ከሚለው ሀረግ መረዳት የሚቻለው ድርጊቱ የአካል ጉዳት ለማድረስ በሚችል ማንኛውም ነገር ለምሳሌ በዱላ፣ በድንጋይ፣ በብረት ወይም ማንኛውም ግዙፍነት ባለው ነገር ወይም ያለምንም ነገር የሰውነት አካልን በመጠቀም ለምሳሌ፦ በቦክስ፣ በቴስታ፣ በእርግጫ ወዘተ ሌላውን ሰው በመምታት በአካል ወይም ጤና ላይ ጉዳት ማድረስን የሚገልጽና ህጉ የወንጀል ድርጊቱን ለመፈጸም የተጠቀምንበትን መሳርያ/ነገር/ ወይም ዘዴ ላይ ምንም የልዩነት ሳያደርግ በነዚህ መንገድ በሌላ ሰው ላይ ጉዳት ከደረሰ የድርጊቱ ፈጻሚ የወንጀል ኃላፊነት እንዳለበትና እንደሚቀጣ ይደነግጋል።
አንቀጽ 554 ላይ ደግሞ የፍርድ ቤቱ ስለአንድ አካል ጉዳት ጉዳይ ባህሪ፣ ስለሚያስከትለው ለውጤት፣ ወይም ስለከባድነቱ የሚያጠራጥር ሲሆን ጉዳዩን ለመወሰን የተፈጸመውን ድርጊት በህክምና ምርመራ ለውጤት ወይም በሚያውቅ ባለሙያ ለማረጋገጥ እንደሚችል የተደነገገ ሲሆን የህመም በድንጋጌ በግልጽ የሚያስረዳው የደረሰው አካል ጉዳት ቅለትና ክብደትን ለማረጋገጥ ፍርድ ቤቶች ከግምት ክሚያስገቧቸው መለክያዎች ውስጥ አንዱና ዋነኛው በተበዳይ ላይ የደረሰውን የጉዳት መጠንና ደረጃ የሚያስረዳው የህክምና ምርመራ ለውጤት ወይም የህክምና ባለሙያው አስተያየት እንደሆነ ልብ ሊባል ይገባል። ስለሆነም በአንድ ሰው ላይ የደረሰው የአካል ጉዳት በክብደትና ቅለትን ከሳሽ ዐቃቤ ህግ ከግምት በማስገባት በምርመራ ወጤቱ መሰረት በድርጊቱ ፈጻሚ ላይ ተገቢውን የወንጀል ህግ በመጥቀስ ክስ ማቅረብ የተለመደና በሀገራችን የፍትህ ከስርዓት በተግባር ላይ በመዋል ላይ የሚገኝ አሰራር ሲሆን የፍርድ ቤቶችም በዚህ ለካ ተመዝኖ የቀረበላቸውን ክስ በተከሳሽ ስለመፈጸሙ ከማስረጃዎች ካረጋገጡ በኃላ በዐቃቤ ህጉ ቀላል ወይም ከባድ ተብሎ የቀረበው ክስ ከህክምና ምርመራ ማስረጃውና ከውንጀሉ ማቋቋምያ ድርጊት አንጻር መርምረው ውሳኔ በመስጠት ላይ የገኛሉ።
አንቀጽ 555 መሰረት ታስቦ የሚፈጸም የአካል ጉዳት ማድረስ ወንጀልን የሚያቋቁሙ ድርጊቶች ከሀ እስከ ሐ የተዘረዘሩ ሲሆን ድርጊቱን ከባድ አካል ጉዳት ለማለት ድንጋጌው ያስቀመጠው በተፈጸመው ድርጊት በተበዳዩ አካል ወይም ጤና ላይ የደረሰውን የጉዳት መጠን (ውጤትን) መሰረት በማድረግ ጉዳቱ የተበዳይን በህይወት የሚያሰጋ፣ በሰውነቱም ሆነ አእምሮው ላይ የዘወትር ጠንቅ የሚያተርፍ ጉዳት ከደረሰ፣ ከአካሉ ወይም አስፈላጊ ከሆኑ ብልቶቹ አንዱ ከጎደለ ወይም እንዳያገለግሉት ካደረገ ወይም በሚያሳቅቅና ጉልህ ሆኖ በሚታይ ሁኔታ መልኩን ካበላሸ ወይም በማናቸውም ሌላ መንገድ ከባድ የሆነ ጉዳትን ወይም በሽታን ማድርስ እንደሆነ ይደነግጋል።
አንቀጽ 556 ታስቦ የሚፈጸም የአካል ጉዳትን አስመልክቶ በንዑስ ቁጥር 1 ላይ በአንቀጽ 555 ላይ ከተመለከቱት ሁኔታዎች ወጪ ታስቦ በሰውአካል ወይም ጤና ላይ የደረሰ ጉዳት በቀላል አካል ጉዳት ማድረስ ወንጀል እንደሚያስቀጣ ሲደነግግ ከዚህ በድንጋጌ የምንረዳው ቁልፍ ነጥብ በአንቀጽ 555 ላይ ከተደነገገት ጉዳቶች ወጪ የደረሰ ጉዳት ቀላል የአካል ጉዳት ማድረስ ወንጀል እንደሆነና አንድን የተፈጸመ አካልጉዳት የማድረስ ወንጀል ቀላል ወይም በአንቀጽ 556 ስር ለመጣል አንዱ መስፈርት በተፈጸመው ድርጊት የደረሰው ጉዳት በአንቀጽ 555 ሰር ከተዘረዘሩት የጉዳት ዓይነቶች ውስጥ ይካተታል ወይስ አይካተትም የሚለው ነጥብ ነው። ተያይዞም ህጉ የድርጊቱ ፈጻሚ ወንጀሉን ለመፈጸም የተጠቀመበትን መሳርያ መሰረት በማድርግ ጉዳቱ የደረሰው በመርዝ ወይም በገዳይ መሳርያ ከሆነ ከሱ በወንጀል ክስ አቅራቢነት እንደሚያስቀጣና ቅጣቱም እንደሚከብድ ይደነግጋል። ጥፋተኛው የሙያ ወይም ሌላ ግዴታን በመተላለፍ ቀላል የአካል ጉዳት ካደረሰ እና ጉዳት የደረሰበት ተበዳይ ደካማ፣ በሽተኛ ወይም ራሱን መከላከል የማይችል ከሆነ በተመሳሳይ መልኩ ወንጀሉ በወንጀል ክስ አቅራቢነት የሚያስቀጣና ከባድ የቅጣት እንድሚያስከትል ይደነግጋል። ስለሆነም የወንጀል ድርጊቱ የተፈጸመበት መሳርያ ወይም ዘዴን አደገኛነት ህጉ እንደ የቅጣት ማክበጃ ከመደንገግ ባለፈ የወንጀል ድርጊቱን ለመፈጸም ተከሳሹ የተጠቀመበት መሳርያ ወይም ዘዴ ራሱን ችሎ የተፈጸመውን ወንጀል ቀላልነት ለመመዘን በመስፈርትነት አልተደነገገም።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ሰሞኑን የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ባሳተመውና ተደራሽ ባደረገው ቅጽ 24 ላይ የያዝነውን ጉዳይ በሚመለክት በስ/መ/ቁ 168166 ላይ በቀን 28/09/2011 ዓ.ም በሰጠው ውሳኔ አንድ ከባድ የአካል ጉዳት ማድረስ ወንጀል ፈጽመሀል ተብሎ የተከሰሰ ተከሳሽ ድርጊቱን ለመፈጸም የተጠቀመበት መሳርያ የሌለ መሆኑ በማስረጃ በተረጋገጠበት ሁኔታ በከባድ የአካል ማድረስ ወንጀል ጥፋተኛ ሊባል የማይገባ ስለመሆኑ የሰጠው ውሳኔ ከላይ ባሰፈርኩት ትንታኔ መሰረት የወንጀሉን የክብደት ወይም ቅለት ለመወሰን ድርጊቱን ለመፈጸም ጥቅም ላይ የዋለው መሳርያ እንደ አንድ መመዘኛ መስፈርት መወሰዱ ለአብዛኞቻችን እንግዳ የሆነና ግርታን የፈጠረ ውሳኔ ነው።
1. የነገሩ አመጣጥ
ከሳሽ ዐቃቤ ህግ ለወረዳ የፍርድ ቤቱ ተከሳሽ የወንጀል ህግ አንቀጽ 555 (1) ን በመተላለፍ ከባድ የአካል ጉዳት ማድረስ ወንጀል ፈጽሟል በሚል ተከሳሽ በክሱ ላይ በተጠቀሰው ቀን ሰዓትና ቦታ የግል ተበዳይን በቦክስና በቴስታ በግራ በኩል አገጩን በመምታት የግራ መንጋጋ አጥንት እንዲሰበር አድርጓል የሚል በዝርዝር ከሰው ማስረጃና የህክምና ምርመራ ለውጤት የሰነድ ማስረጃ ጋር ለፍርድ ቤቱ አቀረበ
ተከሳሽም የቀረበበትን ወንጀል ከዶ በመከራከሩ የዐ/ህግ ማስረጃዎች ከተሰሙ በኻላ የፍርድ ቤቱ የተከሰሰበትን በድንጋጌ ወደ አንቀጽ 556 (1) ሰር በመቀየር እንዲከላከል ከበየነ በኻላ ተከሳሽ የመከላከያ ማስረጃ አቅርቦ ካሰማ በኻላ የፍርድ ቤቱ ተከሳሽ የቀረበበትን ክስ ስለተከላከለ በነጻ አሰናብቶታል።
አቃቤ ህግም በውሳኔው ቅር በመሰኝት ይግባኝ ለከፍተኛ የፍርድ ቤት ቢያቀርብም የፍርድ ቤቱ ይግባኙን ሰርዞታል።
በድጋሚ ዐ/ህግ ጉዳዩን ለደቡብ ክልል ጠቅላይ የፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ በችሎት ያቀረበ ሲሆን ፍርድ ቤቱም የስር ፍርድ ቤትን ውሳኔ በመሻር ተከሳሽን በአንቀጽ 555 (ሐ) ሰር ጥፋተኛ በማለት የቅጣት አስተላልፎበታል።
ተከሳሽም በክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ውሳኔ ቅር በመሰኘት ለፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሰበር አቤቱታ ካቀረበ በኻላ የሰበር በችሎቱ ቅሬታውን መርምሮ የስር ፍርድ ቤትን ውሳኔ በማሻሻል ተከሳሽ በአንቀጽ 556 (1) ሰር ጥፋተኛ በማልት የቅጣት ውሳኔ አስተላልፏል።
የሰበር ችሎቱ ይህን ውሳኔ ለመስጠት በምክንያትነት ያፈራቸው በርካታ ነጥቦች ቢኖሩም የህንድ ውሳኔ ለመስጠት የተጠቀመበት በዝርዝር ትንታኔ ለጉዳዩ እግባብነት የሌለው ሲሆን የ
የሰበር ችሎቱን ውሳኔ በግርድፉ ስንመለከተው አንድን የአካል ጉዳት ከባድ ወይም ቀላል ለማለት ሚዛን ላይ ከሚቀመጡ መስፈርቶች ውስጥ ድርጊቱን ለመፈጸም ጥቅም ላይ የዋለው ነገር/መሳርያ ከግምት ሊገባ እንደሚገባና በከባድ የአካል ጉዳት የተከሰሰ ሰው ድርጊቱን ለመፈጸም የተጠቀመበት ምንም አይነት መሳርያ ከሌለ ተከሳሹ በከባድ አካል ጉዳት ማድረስ ወንጀል ጥፋተኛ እንደማይባል ሲሆን ይህም አንድ ሰው በቴስታ ወይም በቦክስ ሌላ ሰውን መቶ ጥርስ ቢያወልቅ ድርጊቱን ለመፈጸም የተጠቀመበት መሳርያ ስለሌለ ተከሳሽ በአንቀጽ 555 (ሀ) ሰር ሊከሰስ እና ጥፋተኛ ሊባል አይችልም ወደሚል ድምዳሜ የሚያደርስ ይመስላል።
ይሁን እንጂ ምንም እንኳን ከሰበር በችሎቱ ውሳኔ ሀተታ ላይ የሀሳብ ከፍሎ እና የወንጀል ማቋቋምያ መስፈርቶችን በመጥቀስ ለደረሰበት ድምዳሜ ተገቢ ያልሆነና ግልጽነት የጎደለው ትንታኔ መስጠቱ እንደተጠበቀ ሆኖ በተያዘው ጉዳይ ላይ የቀረበው ክስ 555 (1) ን ተላልፏል የሚል ሲሆን (1) ለማለት የተፈለገው (ሀ) ን እንደሆነ እንዲረዳና የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ደግሞ ጥፋተኛ ነው በሚል ውሳኔ የሰጠው በአንቀጽ 555 (ሐ) ሰር በመሆኑ የፌደራሉ ሰበር ውሳኔ በጥቅሉ ከባድ አካል ጉዳት ማድረስ ወንጀል ከማለት ይልቅ በዚህ ንዑስ አንቀጽ ስር የተከሰሰ ተከሳሽ ጥፋተኛ ሊባል የሚችለው ምን መስፈርት ተሟልቶ ሲገኝ ነው የሚለው ነጥብ የሰበር የውሳኔው ማጠንጠኛ መሆን ነበረበት። ይህ ንዑስ አንቀጽ የሚደነግገው ማንም ሰው በአንቀጽ 555 (ሀ) እና (ለ) ከተደነገጉት ሁኔታዎች ወጪ በማንኛውም ነገር በሌላ ሰው ላይ ከባድ ጉዳት ያደረሰ እንደሆነ ሲሆን ይህ በድንጋጌ በ "ሀ" እና በ "ለ" ከተደነገጉት የጉዳት ዓይነትንና መጠንን መሰረት ካደረጉ ከባድ ጉዳቶች ወጪ በተለየ መንገድ ጉዳቱን ከባድ ለማለት ድርጊቱ የተፈጸመበትን መሳርያ መሰረት በማድረግ ተደንግጓል። የህመም ማለት በአንቀጽ 553 ላይ እንደተደነገገው የአካል ጉዳት" በማንኛውም ነገር" ወይም "ዘዴ" ሊፈጸም እንደሚችል የተደነገገ በመሆኑ 555 (ሐ) ከ 553 ጋር በማያያዝ ስንተረጉመው አንድ ሰው በአንቀጽ 555 (ሐ) ሰር ጥፋተኛ ለማለት የደረሰው ጉዳት ከባድ መሆኑ እና ድርጊቱን ለመፈጸም አንዳች ነገር ወይም መሳርያ የተጠቀመ ሆኖ ሲገኝ በመሆኑ ከዚህ አንጻር የፌደራል ሰበር በችሎቱ ውሳኔ ተቀባይነት ያለው ሆኖ እግኝቸዋለሁ።
@@@@@እናንተስ በዚህ ላይ ምን አስተያየት አላችሁ @@@@

08/05/2020

# #እንወቅ እንጠንቀቅ እንጠበቅ # #

የኮሮና ቫይረ ወረርሽኝን ለመቆጣጠር፡ ለመከላከልና ስርጭቱን ለመግታት በፌደራል መንግስት የሚኒስትሮች ምክር ቤት የታወጀ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቁጥር 3/2012 ማስፈጸምያ ደንብ ፡፡

በዞናችን የሚገኝ ማንኛዉም ግለሰብ፡ የህብረተሰብ ክፍል፡ የመንግስትም ሆነ የግል ድርጅቶችና አገልግሎት ሰጪ ተቋማት የሚከተሉትን ክልከላዎችና ግዴታዎች መተላለፍ የወንጀል ተግባር ሆኖ እስከ ሶስት ዐመት በሚደርስ ቀላል እስራት ወይም ከ 100 ሺ እስከ 200 ሺህ ብር እንደሚያስቀጣ ያዉቃሉን?


የተከለከሉ ተግባራት !

1. ለሀይማኖታዊ ወይም ማህበራዊ አላማ፣ ለመንግስታዊ ወይም ፖለቲካዊ ስራ ወይም ሌላ መሰል አላማ አምልኮ በሚደረግባቸው ቦታዎች፣ በመንግስት ተቋማት፣ በሆቴሎች፣ በማናቸውም የመሰብሰቢያ አዳራሾችና በማናቸውም ቦታ አራትና ከዚያ በላይ ሆኖ በአንድ ቦታ ላይ መገኘት የተከለከለ ነው !

2. ማንኛውም ሰው ለሰላምታና ሌላ ማንኛውም አላማ በእጅ መጨባበጥ ክልክል ነው!

3. ማንኛውም ሀገር-አቋራጭ የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጥ ሰው በማንኛውም ጊዜ ከተሸከርካሪው ወንበር ብዛት 50% በላይ ሰዎችን ጭኖ መንቀሳቀስ የተከለከለ ነው!

4. ማናቸውም የከተማ ውስጥ የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጥ ታክሲ፣ አውቶቡስ፣ የፐብሊክ ሰርቪስ ሰራተኞች ትራንስፖርት አገልግሎት ድርጅት አውቶቡስ ከተሸከርካሪው የወንበር ቁጥር 50% በላይ ሰዎችን ጭኖ መንቀሳቀስ የተከለከለ ነው!

5. ማንኛውም የግል ተሸከርካሪ ሾፌሩን ሳይጨምር ከተሸከርካሪው የወንበር ቁጥር 50% በላይ ሰዎችን ጭኖ መንቀሳቀስ የተከለከለ ነው!

6. ማንኛውንም ታራሚን ወይም ተጠርጣሪን በአካል በመገኘት በማረሚያ ቤት ወይም ፖሊስ ጣቢያ መጠየቅ ክልክል ነው! ሆኖም ይህ ድንጋጌ በፖሊስ ጣቢያ ለሚገኝ ተጠርጣሪ፣ ከተጠርጣሪው ጋር በአካል ሳይገናኙ ስንቅ ማድረስን አይከለክልም!

7.በጭፈራ ቤቶችና በመጠጥ ቤቶች ማናቸውንም የመጠጥና መዝናኛ አገልግሎት መስጠት የተከለከለ ነው!

8.በማናቸውም ቦታ የሺሻ ማስጨስና ጫት ማስቃም አገልግሎት መስጠት የተከለከለ ነው!

9. የሲኒማ፣ ቲያትርና በአንድ ቦታ ብዙ ሰዎችን የሚያሰባስቡ መሰል የመዝናኛ አገልግሎቶችን መስጠት ክልክል ነው!

10.ሆቴሎች፣ ካፌዎች ወይም ምግብ ቤቶች አገልግሎት በሚሰጡበት ጊዜ በአንድ ጠረጴዛ ላይ ከሶስት ሰው በላይ እንዲቀመጥ ማድረግ የተከለከለ ሲሆን ተገልጋዮች በሚቀመጡባቸው ጠረጴዛዎቹ መካከል ያለው ርቀትም ሁለት የአዋቂ እርምጃ መሆን አለበት፡፡ ሆኖም ተገልጋዮች የሚገለገሉት በጠረጴዛ ላይ ካልሆነ በመካከላቸው የሚኖረው ርቀት ሁለት የአዋቂ እርምጃ መሆን አለበት፡፡በድንበር አካባቢዎች በሚገኙ ኬላዎች በኩል ወደ ሀገር ውስጥ መግባትም ሆነ ወደ ውጪ መውጣት የተከለከለ ነው!

11.ማንኛውም የመኖሪያም ሆነ የንግድ ድርጅት ቤት አከራዮች በተከራዩ ስምምነት ካልሆነ በስተቀር ቤቱን እንዲለቅ ማድረግ ወይም የቤት ኪራይ ዋጋ ጭማሪ ማድረግ የተከለከለ ነው!

12.ማናቸውም በአዋጅ ቁጥር 1156/2011 መሰረት የሚተዳደሩ ሰራተኞችን የሚያስተዳደሩ የግል ድርጅቶች በስራቸው ያሉ ሰራተኞችን የስራ ውል ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከሚያስቀምጠው ስርአት ውጪ ማቋረጥ የተከለከለ ነው!

13.ማንኛውም የመንግስትም ሆነ የግል ትምህርት ተቋም በትምህርት ቤት ወይም በሌላ ማናቸውም ቦታ አስተማሪና ተማሪዎች በአካል ተገናኝተው መማር ማስተማር ስራ እንዲሰራ ማድረግ ወይም ማስተማር የተከለከለ ነው!

14.ማንኛውም ሁለትና ከዚያ በላይ ሰው በመሆን የሚጫወቱባቸውን ጨዋታዎች፣ ማጫወትም ሆነ መጫወት የተከለከለ ነው!

15.ማናቸውንም የስፖርት ውድድሮች ወይም የቡድን ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎችን ማድረግ የተከለከለ ነው!

16.የህፃናት ማጫዎቻ ቦታዎች አገልግሎት መስጠት የተከለከለ ነው!

17.ማንኛውም ሰው የባንክ አገልግሎት በሚሰጥባቸው አካባቢዎች፣ በገበያዎች፣ በትራንስፖርት መሳፈሪያ ቦታዎች፣ በሱቆች፣ በመድሀኒት መሸጫ አካባቢዎች፣ ህዝባዊ አገልግሎት በሚሰጥባቸው ቦታዎችና ሌሎች ህዝብ በሚበዛባቸው መሰል አካባቢዎች ከሁለት የአዋቂ እርምጃዎ በታች በሆነ ርቀት መቆምም ሆነ መቀመጥ የተከለከለ ነው!

18.መሰረታዊ አገልግሎት የሚሰጡ ተቋማት እንደ መብራት ሀይል፣ ከውሃ አቅርቦት ጋር ግንኙነት ያለው ስራ የሚሰሩ ተቋማት ፣ ኢትዮ ቴሌኮም፣ የህክምና ተቋማት፣ ባንኮች፣ ከምግብ አቅርቦት ጋር ግንኙት ያለው ስራ የሚሰሩ ተቋማት፣ የጽዳት ስራዋችን የሚሰሩ ተቋማትና ባለሙያዎች፣ ከድንገተኛ ና የእሳት አደጋ መከላከል ጋር የተያያዙ ስራዎችን የሚሰሩ ተቋማት፣ ከጥበቃና ደህንነት ጋር የተያያዙ ድርጅቶች እና ተቋማት በማንኛውም መልኩ ስራን አለመስራት ማቋረጥ ማስተጓጎል እና መሰል ተግባራትን መፈጸም የተከለከለ ነው!

19.የደረቅና የፈሳሽ ጭነት አገልግሎትን፣ የምርት ስራን፣ የእርሻ ስራን ወይም የግንባታ ስራን ማቋረጥ፣ ማሰተጓጎል ወይም አለመስራት የተከለከለ ነው!

20.ኮቪድ-19ኝና ተያያዥ ጉዳዮችን በተመለከተ ማህበረሰቡ እንዳይረጋጋ የሚያደርግና በማህበረሰቡ ላይ ስነ-ልቦናዊ ጫና የሚፈጥር ማናቸውንም መረጃ ማሰራጨት የተከለከለ ነው!

በአዋጁ የተደነገጉ ደንቦችን ካከበሩ ዝንድ የመተባበር ግዴታን እንዲወጡ አጥብቀን እንጠይቃለን !

1. ማንኛውም ኮቪድ-19 እንዳለበት የተጠረጠረ ሰው ወይም ወደ ሀገር የሚገባ አለማቀፍ መንገደኛ ኳራንታይን የመደረግና የኮቪድ-19 ምርመራ የማድረግ ግዴታ አለበት!

2. ወደ ሀገር የገባ አለማቀፍ መንገደኛ ኳራንታይን በሚደረግበት ጊዜ የራሱን ወጪ የመሸፈን ሀላፊነት ያለበት ሲሆን፣ መንገደኛው የመክፈል አቅም የሌለው ከሆነ መንግስት ለዚሁ አላማ ባዘጋጀው ቦታ እንዲቆይ ይደረጋል!

3. በኮቪድ-19 መያዙ የተረጋገጠ ማንኛውም ሰው መንግስት በሚያዘጋጀው ለይቶ ማቆያ ክፍል የመቆየት ግዴታ አለበት!

4. በጉዞ ወቅት ኮቪድ-19 አለበት ተብሎ የሚጠረጠር መንገደኛ ሲኖር የማጓጓዣ አንቀሳቃሹ በአቅራቢያው ላለው ወይም ለሚያርፍበት የመግቢያና መውጫ ኬላ ሀላፊ ወይም የኮቪድ- 19 ምርመራ ለሚያደርግ ቡድን የማሳወቅ ሀላፊነት አለበት!

5. ኮቪድ-19 ያለበት ወይም አለበት ተብሎ የሚጠረጠር ሰው ሰለመኖሩ የሚያውቅ ማንኛውም ሰው ለጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ወይም ለፖሊስ የማሳወቅ ግዴታ አለበት!

6. የባንክ አገልግሎት በሚሰጥባቸው አካባቢዎች፣ በገበያዎች፣ በትራንስፖርት መሳፈሪያ ቦታዎች፣ በትራንስፖርት ውስጥ፣ በሱቆች፣ በመድሀኒት መሸጫ አካባቢዎች፣ ህዝባዊ አገልግሎት በሚሰጥባቸው ቦታዎችና ሌሎች ህዝብ በሚበዛባቸው መሰል አካባቢዎች የሚገኝ ማንኛውም ሰው አፍና አፍንጫው ላይ መሸፈኛ የማድረግ ግዴታ አለበት!

7. በዚህ አንቀፅ ንዑስ አንቀፅ 6 የተመለከተው የአፍና አፍንጫ መሸፈን ግዴታ ለዚሁ አላማ ተብሎ በፋብሪካ በተሰራ፣ በቤት ውስጥ ከተለያዩ ጨርቃጨርቆች በተዘጋጀ ወይም በማናቸውም አይነት ልብሶች ሊፈጸም ይችላል!

8. ማንኛውም አገልግሎት የመንግስትም ሆነ የግል አገልግሎት ሰጪ ተቋም አገልግሎቱን ለማግኘት ወደ ተቋሙ ለሚመጡ ተገልጋዮች ቫይረሱን ለመከላከል የሚያስችሉ የንፅህና መጠበቂያ ቁሶችን ማዘጋጀትና ተገልጋዮች አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረጋቸውን የማረጋገጥ ሀላፊነት አለበት!

9. ማናቸውም አገልግሎት የሚሰጡ የመንግስትም ሆነ የግል ተቋማት አገልግሎት ለማግኘት ወደ ተቋማቱ የሚሄዱ ተገልጋዮች ሁለት የአዋቂ እርምጃ ተራርቀው የሚቆሙበትን ቦታ ምልክት የማድረግ ሀላፊነት አለባቸው!

10.የመንግስት የኮሙኒኬሽን ባለሙያዎችና የግል የሚዲያ ተቋማት ኮቪድ-19ኝና ተያያዥ ጉዳዮችን በተመለከተ የሚያስተላልፏቸው መረጃዎች፣ የዜና ትንተናዎች ወይም ፕሮግራሞች ሳይጋነኑ ወይም ሳይቃለሉ ተገቢው መረጃ ወደ ሕዝቡ የማድረስ እና አላግባብ የሆነ ድንጋጤና ሽብርን የማይፈጥሩ መሆን አለባቸው !

11.ማንኛውም በፌዴራልም ሆነ በክልል የሚገኙ የመንግሥትም ሆነ የግል ተቋማት በተቋሙ ስር ለሚገኙ ሰራተኞች ስለቫይረሱ አስፈላጊውን መረጃ የተለያዩ ዘዴዎችን በመጠቀም የማድረስ፣ በመግቢያና መውጫ በሮችና ሌሎች አስፈላጊ ቦታዎች ላይ ቢያንስ እጅ ለመታጠብ የሚያስችል ውሃና ሳሙና ማዘጋጀት ፣ በተቻለ መጠን ሌሎች የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት የሚረዱ የጥንቃቄ ቁሳቁሶችን ማቅረብ ይኖርባቸዋል!

12.ማንኛውም በፌዴራልም ሆነ በክልል የሚገኙ የመንግሥትም ሆነ የግል ተቋማት በተቋሙ ስር የሚገኙ ሰራተኞች በአንድ ክፍል ውስጥ፣ በአንድ መስሪያ ቦታ ወይም በአንድ ትራንስፖርት ውስጥ ተጨናንቀውና አካላዊ ርቀትን ለመጠበቅ በማያስችል መልኩ እንዳይሰሩ ለማድረግ አስፈላጊውን ፈረቃ ማመቻቸት፤ ሰራተኞቹ ቤታቸው ሆነው የሚሰሩበትን ሁኔታ ወይም እረፍት በመውሰድ ስራ ቦታ እንዳይመጡ የማመቻቸት ሀላፊነት አለበት!

13.ማንኛውም የፌዴራልም ሆነ የክልል የመንግስት ተቋምና በአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ ቁጥር 1156/2011 መሰረት የሚተዳደሩ ሰራተኞችን የሚስተዳድር የግል ድርጅት ሰራተኞቹ ወደ ስራ ቦታ ለመሄድ ትራንስፖርት መጠቀም አስፈላጊ ከሆነ በስራ ላይ ለሚገኙ ሰራተኞች
የትራንስፖርት አገልግሎት የማመቻቸት ሀላፊነት አለበት!

14.ፖሊስ ኮሚሽን ወይም ማረሚያ ቤት ተጠርጣሪዎች ከጠበቆቻቸው ጋር የሚገናኙበትን ሁኔታ የማመቻቸት ሀላፊነት አለበት!
15.ማንኛውም የቤት፣ የሆቴል፣ የአፓርታማ፣ የተሽከርካሪ፣ የአዳራሽ ወይም የማንኛውም ንብረት ባለቤት መንግስት የኮቪድ-19 ሥርጭትን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠር እና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ ለሚያደርገው ጥረት አስፈላጊ የሆነ ንብረቱን ለዚህ አላማ አገልግሎት ላይ እንዲውል በሚኒስትሮች ኮሚቴ ወይም ኮሚቴው ውክልና በሰጠው የመንግስት አካል ሲወሰንና ሲጠየቅ ንብረቱን ለእለት ከእለት ፍጆታው የሚጠቀምበት ካልሆነ በሰተቀር ውሳኔውን ተግባራዊ የማድረግ ግዴታ አለበት!

16.ማንኛውም አምራች ወይም አገልግሎት ሰጪ ድርጅት፣ የኮቪድ-19 ሥርጭትን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠር እና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ ለሚያደርገው ጥረት አስፈላጊ የሆነ አግለግሎት እንዲሰጥ፣ አገልግሎቱን እንዲያሰፋ፣ ምርት እንዲያመርት፣ የሚያመርተውን ምርት መጠን እንዲጨምር፣ አዲስ ምርት አይነት እንዲያመርት ወይም ምርቱን መንግስት በሚወስነው ተመጣጣኝ ዋጋ ለመንግስት፣ ለሾማቾች ወይም ለህብረት ስራ ማህበራት እንዲሸጥ በሚኒስትሮች ኮሚቴ ወይም ኮሚቴው ውክልና በሰጠው የመንግስት አካል የሚሰጠውን ትዕዛዝ ተግባራዊ ማድረግ አለበት!

17.ሆቴሎች ለደንበኞቻቸው አገልግሎት በሚሰጡበት ጊዜ የእጅ መታጠቢያ ውሀና ሳሙና የማቅረብ ሀላፊነት ያለባቸው ሲሆን፣ የሆቴሉ ተጠቃሚዎችም እጃቸውን መታጠባቸውንና አስፈላጊውን ንፅህና አጠባበቅ ስርአት ተግባራዊ ማድረጋቸውን የማረጋገጥ እንዲሁም ደንበኞች ከተጠቀሙ በኋላ የተገለገሉባቸውን ጠረጴዛዎች፣ ወንበሮችና ሌሎች እቃዎች የማከም ግዴታ አለባቸው!

18.ማንኛውም በስራ ላይ ያለ፣ ጡረታ የወጣ ወይም በትምህርት ላይ ያለ የጤና ወይም የሌላ ሙያ ባለቤት ወይም ማንኛውም ዜጋ የኮቪድ-19 ሥርጭትን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠር እና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ በሚደረገው ጥረት አስተዋፅዖ እንዲያደርግ በመንግስት ጥሪ ሲደረግለት የመተባበር ግዴታ አለበት!

ለጠንቃቄ ቅድሚያ እንስጥ !
ህግን አለማወቅ ይቅርታ አያሰጥም!!
***የደቡብ ኦሞ ዞን ዐቃቤ ህግ መምሪያ***

01/03/2020

♠♠♠ስለ የወንጀል ክስ ማንሳት♣♣♣
ሰሞኑን በሀገራችን አንዳንድ ክልሎችና በፌደራል መንግስት በዐቃቤ ህግ የተመሰረቱ ክሶች ዉሳኔ ሳይሰጥባቸዉ ክስ የተነሳበትና በጥበቃ ስር የሚገኙ ተከሳሾች መለቀቃቸዉ ይታወሳል፡፡ እኛም በዚህ አጋጣሚ በጉዳዩ ላይ ተፈፃሚነት ያላቸዉን ህጎችና ተያያዥነት ያላቸዉን ሀሳቦች በማንሳት የሚከተለዉን ፅሁፍ ለዉይይት መነሻ እንዲሆን ለማቅረብ ወደድን፡፡
1.የወንጀል ክስን ማንሳት ምን ማለት ነው፡- ለዚህ ጽንሰ ሀሳብ ወጥ የሆነና ሁሉንም የሚያግባባ ትርጉም ለመስጠት አዳጋች ቢሆንም ስለጉዳዩ ከሚደነግጉት ህጎች አንጻር ክስን ማቋረጥ ማለት አንድ በፍርድ ቤት የቀረበን የወንጀል ክስ ከውሳኔ በፊት ክሱን ያቀረበው አቃቤ ህግ በህግ ክስን ለማቋረጥ የተቀመጡ መስፈርቶች ተሟልተው ሲገኙ የክስ መሰማት ሂደቱ እንዳይቀጥል ማድረግ ወይም ክሱን ማቋረጥ ማለት ነው፡፡ በአለማችን ውስጥ ባሉ የተለያዩ ሀገራት ለዚህ ጽንሰ ሀሳብ በህጋቸው ግልጽ የሆነ ትርጉም የሰጡት ሲሆን ለዚህም አውስትራሊያንና የህንድ ወንጀል ህግን መጥቀስ ይቻላል፡፡
ይሁን እንጂ በሀገራችን ኢትዮጵያ አዋጅ ቁጥር 185/1961 የወንጀል ሥነ ሥርዓት ህግም ሆነ የጠቅላይ አቃቤ ህግ መቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 943/2008 (6)(3)(ሠ) ስለ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ስልጣንና ተግባር በጥቅሉ ከመደንገግ ውጪ ስለ ክስ ማንሳት ትርጉም አልሰጡም፡፡
2.የክስ ማንሳት አስፈላጊነት፡- ምንም እንኳን በሥነ ሥርዓት ህጉም ሆነ በማቋቋሚያ አዋጁ ላይ በግልጽ የክስ ማንሳት አላማውን አስመልክቶ በግልጽ የተቀመጠ ድንጋጌ ባይኖርም ከድንጋጌዎቹ ይዘትና ከሀገሪቱ የወንጀል ፍትህ ፖሊሲ አንጻር የወንጀል ክስ ማንሳት አላማዎች የሚከተሉትን ያካትታል፡፡
#የህዝብ ጥቅም፡-በአዋጅ ቁጥር 943/08 እና በወ/መ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ 42 (1)(መ) መሰረት የወንጀል ክስ መዘጋት እና መነሳት አላማው የህዝብ ጥቅም እነንደሆና የክሱ መነሳት ለህዝብ ጥቅም ሲባል አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ወይም ለህዝብ ጥቀም ሲባል ክሱ እንዲነሳ የፍርድ ሚንስተር ትዕዛዝ ሲሰጥ ክሱ ሊዘጋ ወይም ሊነሳ መቻሉን እንረዳለን፣
#የሀገር ጥቅም፡- የክሱ መነሳት ከሀገሪቱ ማህበራዊ፣ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ፍላጎት አንጻር ከፍተኛ ጠቀሜታ ሲኖረው የሀገሪቱን ጥቅም ለማስከበር ክስ ሊነሳ እንደሚችል እንረዳልን፣
#ለፍትህ አስተዳደሩ ውጤታማነት፡-በወ/መ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ 122 መሰረት በመንግስት ትዕዛዝ ሲሰጥ እና ለፍትህ አስተዳደሩ ውጤታማነት ሲባል ክስ እንደሚነሳ መረዳት እንችላለን፡፡
#የስነ ስርዓት ግድፈትን ለማረም፡-በክስ አመሰራረት ወቅት አቃቤ ህግ የፈጸማቸውን መሰረታዊ ስህተቶችን ለማረም የሚችልበትን ዕድል በመፍጠር የወንጀል ፍትህ አስተዳደርን ውጤታማነት መረጋገጥም ሌላው የህጉ አላማ ነው፡፡
3.የወነጀል ክስ ማንሳት ከህግ ማዕቀፍ አንጻር፣
የወንጀል ክስ ማቋረጥን አስመልክቶ የወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ህግ እና የጠቅላይ አቃቤ ህግ ማቋቋሚያ አዋጅ ከሚደነግጉት ውጪ በጉዳዩ ላይ ተፈጸሚ የሚሆን ሌላ ህግ ባለማግኘቴ ጉዳዩን ከሁለቱ አዋጆች አንጻር እንመልከት፡፡
3.1 የጠቅላይ አቃቤ ህግ ማቋቋምያ አዋጅ
በፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ ማቋቋምያ አዋጅ ቁጥር 943/08 አንቀጽ 6 መሰረት ጠቅላይ አቃቤ ህግ መንግስትን በመወከል የወንጀል ክስ እንደሚያቀርብ፣ እንደሚከራከር፣ ለህዝብ ጥቅም አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ የተጀመረውን የወንጀል ምርመራ ወይም የወንጀል ክስ እንደሚያቋርጥ ይደነግጋል፡፡ በተጨማሪም ጉዳዩ ሀገራዊ ይዘት ካለው በጠቅላይ ሚንስትሩ አማካሪነት ክሱ የሚቋረጥበትን መመርያ እንደሚያወጣ ይደነግጋል፡፡ ከዚህ አዋጅ አንጻር የምንረዳቸው ቁም ነገሮች የሚከተሉትን ያካትታል፡፡ ምንም እንኳን ለህዝብ ጥቅም አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ አቃቤ ህግ ለፍርድ ቤት የቀረበን የወንጀል ክስ ለማንሳት ስልጣን እንዳለው ቢደነግግም አዋጁ የህዝብ ጥቅም ምን ማለት እንደሆነና ምን አይነት መስፈርቶች ሲሟሉ የህዝብ ጥቅም እንደሚባል በዝርዝር አልደነገገም፣ አዋጁ የወንጀል ክስ ሲነሳ የወንጀል ሰለባ የሆኑ አካላትን ወይም ቤተሰቦቻቸውን በተፈጸመው ወንጀል ምክንያት የደረሰባቸውን ጉዳት ከግምት ለማስገባት ወይም የሚመዘንበት እድል የማይሰጥ መሆኑ፣ የተጀመረ ክስን የማቋረጥና የተቋረጠ ክስን የማስቀጠል ስልጣን ለአቃቤ ህግ ብቻ የተሰጠ ልዩ ስልጣን እንደሆነ መደንገጉ፣ አዋጁ በምን አይነት ቅድመ ሁኔታዎች አቃቤ ህግ የተቋረጠውን ክስ እንደሚቀጥል እና የተቋረጠው ክስ ሊቀጥል የሚችልበት የተቀመጠ የጊዜ ገደብ አለመኖሩ በአዋጁ ውስጥ የሚታዩ የህግ ክፍተቶች ናቸው፡፡
3.2 የወነጀል ስነ ስርዓት ህግ
አንቀጽ 42 ክስ ስለማይቀርብባቸው ሁኔታዎች፣
የወ/ስ/ስ/ህግ/ቁጥር 42(1(መ)- መሰረት አቃቤ ህግ ክስ መዝጋት እንደሚችልና“ ክስ ማቅረብ የማይቻለው የፍርድ ሚኒስትሩ በፈረመበት ማዘዣ ለህዝብ ጥቅም ሲል ክስ እንዳይቀርብ አቃቤ ህጉን ያዘዘው እንደሆነ ነው” በማለት የሚደነግግ ሲሆን ይህም ከክስ ማንሳት በመጠኑ የሚለይና ከውጤት አንጻር ከክስ ማንሳት ጋር ተመሳሳይ ውጤት ያለው ለጊዜው ተከሳሹን ክስ እንዳይቀርብበት የሚያደርግና ወደፊት ግን አዲስ ክስ ከማቅረብ የሚያግደው ነገር የሌለ በመሆኑ በዚህ ድንጋጌ መሰረት ክሱ የተዘጋ ተከሳሽ ወደፊት ክሱ ሊቀጥል እንደሚችል እንረዳለን፡፡ ይሁን እንጂ ከክስ ማንሳት የሚለየው ነጥብ ክሱ ለፍርድ ቤት ከመቅረቡ በፊት ዐቃቤ ህግ የምርመራ መዝገቡ እንደደረሰው በራሱ የሚወስነው ውሳኔ መሆኑ ነው፡፡
አንቀጽ 122 ክስ ስለማንሳት፣
1.ከከባድ የግፍ ግድያ እና ከከባድ ወንበዴነት ክስ በስተቀር አቃቤ ህግ በተከሳሽ ላይ ለፍርድ ቤት ያቀረበውን ማንኛውም ክስ በፍርድ ቤቱ ፈቃድ ከፍርድ በፊት ክሱ በሚሰማበት በማንኛውም ጊዜ ክሱን ለማንሳት ይችላል በማለት ይደነግጋል፡፡ ምንም እንኳን አቃቤ ህግ በምን ምክንያት ክስ ለማንሳት እንደሚችል ይህ ድንጋጌ በግልጽ ባይደነግግም ከጠቅላይ አቃቤ ህግ መቋቋሚያ አዋጅ መሰረት አቃቤ ህግ ክስ ማንሳት የሚችለው የክሱ መነሳት ለህዝብ ጥቅም አሰፈላጊ ሆኖ መገኘቱ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ ክስ ማንሳት ለአቃቤ ህግ የተሰጠ ፍጹም የሆነ መብት ሳይሆን በፍር ድቤቱ ፈቃድ መሰረት የሚፈጸም መሆኑንና ይህም ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ ክሱን ለማንሳት የሚያቀርበውን ምክንያት መርምሮ አሳማኝ ሆኖ ሲያገኘው ብቻ የክሱን መነሳት እንደሚፈቅድ መረዳት ይቻላል ይሁን እንጂ የክሱ መነሳት በመንግሰት ትዕዛዝ መሰረት ከሆነ በዚህ ንዑስ አንቀጽ ለፍርድ ቤቱ የተሰጠው ፍቅድ ስልጣን የመንግስት ትዕዛዝ መኖሩን ማረጋገጥ ብቻ ነው፡፡ ስለሆነም ክስ ለማንሳት አቃቤ ህግ ከሚያቀርባቸው ምክንያቶች ውስጥ በዚህ ድንጋጌ የተገለጸው የመንግስት ትዕዛዝ ብቻ ነው፡፡

2.ክሱን እንዳነሳ በመንግስት ታዝዣለሁ ብሎ አቃቤ ህግ ለፍርድ ቤቱ ሲያመለክት ዐቃቤ ህጉ ክሱን እንዲያነሳ ከመንግስት የታዘዘ መሆኑን ፍርድ ቤቱ ከተረዳ ፍርድ ቤቱ የክሱን መነሳት መፍቀድ እንዳለበት ይደነግጋል፡፡ ይህ ድንጋጌ በንዑስ ቁጥር (1) ላይ ለፍርድ ቤቱ የተሰጠው ክስ እንዲነሳ የመፍቀድ ፍቅድ ስልጣን ቀሪ የሚሆንና የመንግሰት ትዕዛዝ መኖሩን ፍርድ ቤቱ ካረጋገጠ የክሱን መነሳት የመፍቀድ ግዴታን ይጥልበታል፡፡
3.ክሱ እንዲነሳ ፍርድ ቤቱ ሲፈቅድ በተከሳሹ ላይ በቁጥር 119 መሰረት አዲስ ክስ ያልተዘጋጀ እንደሆነ ተከሳሹ ለጊዜው ይለቀቃል በማለት ይደነግጋል፡፡ የክስ መነሳት ውጤት አንዱ ተከሳሹ ለጊዜው መለቀቅ እንጂ ከቀረበበት ክስ ነጻ እንደማይሆንና ክስ ከተነሳ በኃላ የተሸሻለ ወይም የተለወጠ ክስ በአንቀጽ 119 መሰረት ሊቀርብበት እንደሚችልና ይህም ክስ ማንሳት በክስ አመሰራረት ሂደት በሚጠሩ ስህተቶችን ለማረም አቃቤ ህግ የሚጠቀምባቸው አንዱ ስነስርዓታዊ ሂደት እንደሆነ መረዳት እንችላለን፡፡ ስለሆነም በዚህ ንዑስ ድንጋጌ መሰረት ክስ ከሚነሳባቸው ምክንያቶች ውስጥ አንዱ በክስ አመሰራረት ሂደት አቃቤ ህግ የፈጸመውን ስህተት ለማረም እንደሆነ በትርጉም መረዳት ይቻላል፡፡
4.ፍርድ ቤቱ ክሱን ለማንሳት ወይም ላለማንሳት ለሚሰጠው ውሳኔ ምክንያቱን መግለጽ እንዳለበት እና በዚህ ቁጥር መሰረት ክሱ የተነሳ እንደሆነ ክሱን ለወደፊት ለመቀጠል የሚከለክል አይሆንም በማለት የክስ ማንሳት ውጤትን ይደነግጋል፡፡
በጥቅሉም ከነዚህ ሁለት የስነ ስርዓት ድንጋጌዎች መረዳት የምንችለው፡-
ህጉ የህዝብ ጥቅም ለሚለው በግልጽ የሰጠው ትርጉም ወይም ያስቀመጠው መስፈርት አለመኖሩ
#ህጉ 42 ላይ ክስ ላለመመስረት የህዝብ ጥቅምን ምክንያት አድርጎ ከመደንገግ ውጪ በአንቀጽ 122 ላይ የተጀመረ የወንጀል ክስ ሊቋረጥ ወይም ሊነሳ የሚችልበትን ምክንያት አይደነግግም
ፍርድ ቤት ክስ እንዲነሳ የቀረበው ጥያቄ አቃቤ ህጉ በመንግስት የታዘዘ መሆኑን ካረጋገጠለት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ፍርድ ቤቱ ክሱ እንዲነሳ የመፍቀድ ግዴታ እንዳለበት
ክስ እልመሰርትም ተብሎ በአቃቤ ህግ የተሰጠ ውሳኔ ወይም የተጀመረ ክስ እንዲነሳ ወይም እንዳይነሳ የተሰጠ ውሳኔ ይግባኝ የማይባልበት መሆኑ
ክስ ላለመመስረት ወይም ክስ ለማንሳት ለአቃቤ ህግ የተሰጠው ብቸኛ ስልጣን መሆኑና የአቃቤ ህግ ተቋም ተጠሪነቱ ለአስፈጻሚው እስከሆነ ድረስ አስፈጻሚው ጣልቃ እንዲገባ ሰፊ በር የሚከፍት መሆኑ ሲሆን
4.የወንጀል ክስ ማንሳት ከህገ መንግስት አንጻር
በኢፌድሪ ህገ መንግሰት እውቅናና ጥበቃ ከሚደረግላቸው መብቶች ውስጥ አንዱ በአንቀጽ 20 (2) መሰረት የተከሰሱ ሰዎች በቀረበባቸው ክስ ላይ ውሳኔ የማግኘት ወይም የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብት እንዳላቸውና በአንቀጽ 37 መሰረት ደግሞ ማንኛውም ሰው ፍትህ የማግኘት መብት እንዳለው ይነግጋል፡፡ በአንጻሩ በወንጀል የተከሰሰ ሰው ክሱ ሲነሳለት ከቀረበበት ክስ ሙሉ በሙሉ ነጻ የማይሆንና ወዲያውኑ ሌላ ክስ ሊቀርብበት ወይም የተቋረጠው ክስ ወደፊት ሊቀጥል የሚችል ውጤት ያለው በመሆኑ ይህ ተከሳሽ በቀረበበት ክስ መሰረት ነጻ መሆኑ ወይም ጥፋተኛ መሆኑ ተረጋግጦ አንድ ውሳኔ ሳያገኝ ጉዳዩን በእንጥልጥል የማስቀረት ውጤት ያለውና በተከሳሹም ላይ የተቋረጠው ክስ ከዛሬ ነገ ለቀጥል ይችልላል በሚል ፍርሀትና ሰቀቀን ውስጥ ህይወቱን እንዲመራ የሚያደርገው በመሆኑ ህገ መንግስታዊ ከሆነው ፍትህ የማግኘት መብት እና የተከሰሱ ሰዎች የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብት ጋር የሚቃረን ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡
አንቀጽ 78 እና 79 ነጻ የሆነ የዳኝነት አካል ስለመቋቋሙና ከማንኛውም ጣልቃ ገብነት ነጻ ስለመሆናቸው ይደነግጋል፡፡ ይሁን እንጂ በተያዘው ጉዳይ በተለይም አቃቤ ህግ የተጀመረውን ክስ እንዲያነሳ በመንግስት መታዘዙን ካረጋገጠ ፍርድ ቤት የቀረበውን ምክንያት ሳይመረምር ክሱ እንዲነሳ የመፍቀድ ግዴታን የሚጥል በመሆኑ የዳኝነት ነጻነትን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ እና ህብረተሰቡ በፍትህ ላይ ያለውን አመኔታ የሚሸረሽር ይሆናል፡፡
በአንቀጽ ይግባኝ የማቅረብ መብት እንዳለው ይደነግጋል ነገር ግን በተያዘው ጉዳይ አንድ የተመሰረተ ክስ አንዲነሳ ወይም እንዳይነሳ ፍርድ ቤት በሚሰጠው ውሳኔ ላይ ይግባኝ የማይቀርብበት መሆኑ የዜጎችን ይግባኝ መብት የሚጋፋ በመሆኑ እና በጥቅሉ በህገ መንግስቱ እውቅናና ጥበቃ የሚደረግለትን የግለሰብ መብት የሚጥስ በመሆኑ የወንጀል ክስን ማቋረጥ ህገ መንግስታዊነት በሚመለከተው አካል ትርጉም የሚያሻው ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡
5. የሚታዩ ችግሮች፡- ከሞላ ጎደል ስለ ክስ መዝጋት ወይም ክስ ማንሳት አስመልክቶ በሁለቱ አዋጆች ላይ የተደነገጉ ቢሆንም ህጎቹ በራሳቸው በርካታ ክፍተቶችና ውስንነቶች ያሉባቸው በመሆኑ የሚከተሉት ችግሮችን ተለይተዋል፡፡
5.1 አስፈጻሚ አካሉ በፍትህ አስተዳደሩ ላይ ጣልቃ እንዲገባ ምቹ ሁኔታን መፍጠሩ፡- ከላይ እንዳየነው በህጎቹ ላይ ክስ ለማንሳት ምክንያት የሆኑ መስፈርቶች በግልጽ ካለመቀመጣቸው ባለፈ የህዝብ ጥቅም ለሚለው ሁኔታ ግልጽ ትርጉም አለመሰጠቱና ዝርዝር መስፈርቶች ወይም ቅድመ ሁኔታዎች አለመኖራቸው የህዝብ ጥቅምን የመወሰን ስልጣን በአስፈጻሚው ስር ለሚገኘው የዐቃቤ ህግ ተቋም ልዩና ብቸኛ ስልጣን የሚሰጥ በመሆኑ ይህም ማለት በህገ መንግስቱ እና ሌሎች ህጎች ለዜጎች የተሰጡ መሰራዊ መብቶችን ጠቅላይ አቃቤ ህግ እንዳሻው እንዲጥሳቸው ከመፍቀድ የማይተናነስ ስልጣን መሆኑና ይህም አስፈጻሚ አካሉ በወንጀል ፍትህ አስተዳደር ውስጥ ጣልቃ በመግባት የፍትህ አስተዳደሩ ላይ ሳንካ የመፍጠር ሰፊ እድልን ፈጽሯል፡፡
5.2 ክስ ለማንሳት በሚቀርብ አቤቱታ ላይ የፍርድ ቤቶች ፍቅድ ስልጣን የተገደበ መሆኑ፡- አቃቤ ህግ ክሱ እንዲነሳ በመንግስት ታዝዣለሁ የሚል ምክንያት ካቀረበ ፍርድ ቤቶች መንግስት ክሱ እንዲነሳ የፈለገበት ምክንያት አሳማኝና በቂ ስለመሆኑ የመመርመር ስልጣን የሌላቸውና የመንግስት ትዕዛዝ መኖሩን ብቻ ካረጋገጡ የክሱን መነሳት የመፍቀድ ግዴታ የሚጥልባቸው መሆኑ ለፍርድ ቤቶች በህግ የተሰጣቸውን ስልጣን የሚገድብና በህገ መንግስቱ እውቅናና ጥበቃ የሚደረግለትን የፍርድ ቤቶችን ነጻነትና ገለልተኛነት የሚጥስ እና በፍርድ ቤቶች ስራ አስፈጻሚውን አካል ጣልቃ የሚያስገባ የአሰራር ስርዓትን ፈጥሯል፡፡
5.3 የይግባኝ መብት አለመኖር፡- ዐቃቤ ህግ በቁጥር 42 መሰረት ክስ ሲዘጋ ወይም በቁጥር 122 መሰረት ክስ ሲያነሳ ወይም ፍርድ ቤት ክስ እንዲነሳ ወይም እንዳይነሳ በሚሰጠው ውሳኔ ላይ ቅር የተሰኘ ወገን ቅሬታውን ወይም ይግባኝ በውስጥ አሰራር ወይም በመደበኛ ፍርድ ቤቶች የሚያቀርብበት ስርዓት አለመኖሩ ህገ መንግስታዊ የሆነውን የዜጎችን የይግባኝ መብት የሚቃረንና የዜጎች መሰረታዊ መብቶች እንዲጣሱ ዕድልን ፈጥሯል፡፡
5.4 ህገ መንግስታዊ ጥያቄን ማስነሳቱ፡- በተለይም ከይግባኝ መብት አንጻር በየትኛውም የአስተዳደር እርከን ወይም ፍርድ ቤቶች በሚሰጡ ውሳኔዎች ላይ ጥቅም ወይም መብት ያለው ሰው ቀሬታውን ለሚመለከተው አካል የማቅረብ መብት በህገ መንግስቱ ዕውቅናና ጥበቃ የሚደረግለት መብት ቢሆንም በክስ መዘጋት ወይም መነሳት ሂደት ግን አቃቤ ህጉ ወይም ፍርድ ቤቱ በሚሰጠው ውሳኔ ላይ ይግባይ ወይም ቅሬታ የሚቀርብበት ስርዓት አለመኖሩ፣ የተፋጠነ ፍትህ ከማግኘት መብት አንጻር የተከሰሰ ሰው በቀረበበት ክስ መሰረት የጥፋተኝነት ውሳኔ ወይም ጥፋተኛ ባለመሆኑ ነጻ መሆኑ የሚረጋገጠው የክስ መሰማት ሂደቱ ተጠናቆ ፍርድ ቤቱ በሚሰጠው ውሳኔ ሲሆን በክስ ማንሳት ሂደት ግን ክስ የቀረበበት ሰው በቀረበበት ክስ ላይ የመጨረሻ ውሳኔ ሳያገኝ ለጊዜው የሚለቀቅ በመሆኑ ተከሳሽ በቀረበበት ክስ ላይ የመጨረሻ ውሳኔ የማግኘት መብቱንና የወንጀል ተጎጂዎችና ቤተሰቦችም ተከሳሹ በፈጸመው ወንጀል ለፍትህ ቀርቦ የመጨረሻ ውሳኔ ሳያገኝ ክሱ በመነሳቱ ፍትህ የማግኘት ህገ መንግስታዊ መብታቸውን የሚገድብ ስርዓት መሆኑ፣ ነጻና ገለልተኛ ፍርድ ቤቶች ከማቋቋም እና ከዳኝነት ነጻነት አንጻር የተደነገጉ መርሆች ጋር የሚጣረሱ አፈጻጸሞችን በመፍጠር በፍትህ አስተዳደር ስርዓቱ ውስጥ አስፈጻሚውን አካል ጣልቃ የሚገባበትን ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር አሰራር መሆኑ ሲታይ ይህ ስነ ስርዓታዊ ሂደት ህገ መንግስታዊ ትርጉም የሚያስፈልገው ጉዳይ ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡
5.5 የህዝብ ጥቅም የሚለው መስፈርት ለሚዛን አዳጋች መሆን፡- በወንጀል ህግ በግል አቤቱታ አቅራቢነት ከሚያስቀጡ ወንጀሎች በስተቀር በክስ አቅራቢነት የሚያስቀጡ ወንጀሎች ከባድ ወንጀሎች መሆናቸውና ጉዳት የሚያደርሱትም በመላው ህዝብ ላይ በመሆኑ በተፈጸመው ወንጀል መብቱና ጥቅሙ የተጎዳበት ህዝብ በአንድ በኩል ሲኖር በክሱ መነሳት ደግሞ ተጠቃሚ የሚሆን ሌላ ህዝብ እንዴት ሊኖር ይችላል ቢኖር እንኳን የየትኛው ጎራ ጥቅም እንደሚበልጥ መለክያው ምንድን ነው በቁጥር ካልን የወንጀሉ መፈጸም ጉዳት የሚያደርሰው በሀገሪቱ ውስጥ ባሉ መላው ህዝብ ላይ ሲሆን በክሱ መነሳት ግን ሊጠቀሙ የሚችሉት ተከሳሽና የተከሳሽ ቤተሰቦች ወይም የተወሰነ የህብረተሰብ ክፍል በመሆኑ ይህ መስፈርት በራሱ ለአፈጻጸምና ለመለካት አስቸጋሪ ይሆናል፡፡ ስለሆነም የህዝብ ጥቅም መለካት ያለበት ከሀገራዊ ፋዳና ጥቅም አንጻር ብቻ ስለሆነ በጠቅላይ አቃቤ ህግ ማቋቋሚያ አዋጅ መሰረት ደግሞ የሀገሪቱን ጥቅም በሚመለከቱ ጉዳዮች ሲሆኑ ጠቅላይ አቃቤ ህግ የክስ ማንሳት ሂደቱ የሚፈጸምበትን መመርያ በጠቅላይ ሚንስትሩ አማካሪነት እንደሚያዘጋጅ የተደነገገ በመሆኑ በተለይም በቅረቡ በሀገራችን ክሳቸው እየተነሳ ከእስር የሚለቀቁ ተከሳሾች ክስ ፖለቲካዊና ሀገራዊ ጭብጥ ያላቸው በመሆኑ ይህ የአፈጻጸም መመርያ በሌለበት ክሳቸውን ማንሳት ከአዋጁ ጋር የሚቃረን ተግባር ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡
6. መውጫ፡- ሲጠቃለል እነዚህ በህግ ማዕቀፎቹ ላይ የሚታዩ ክፍተቶች ሳይስተካከሉና የህግ ማዕቀፍ ማሻሻያ ሳይኖር በሀገራችን እየተፈጸመው የሚገኘው የክስ ማንሳት ሂደት በተጓዳኝ የሚያስከትላቸውን ሁለንተናዊ ችግር ከግምት በማስገባት የሀገሪቱ ህግ አውጪ አካልና መንግሰት ግልጽነት ያለው ወጥ የሆነ ጠንካራ የህግ ማዕቀፍ በማዘጋጀት ከህገ መንግስቱ ጋር በተጣጣመ መልኩ ተፈጻሚ የሚሆን ህግ እንዲዘጋጅ መልዕክታችንን እናስተላልፋለን፡፡
ተጻፈ 22/06/2012 ዓ.ም
ጂ ን ካ፣
በስራ ሂደቱ፣

27/02/2020

የፌዴሬሽን ምክር ቤት እና የህገ መንግስት አጣሪ ኮሚሽን ስልጣንና የአሰራር ስርዐት፡
ሰሞኑን በፋና ቴሌቪዥን የዜና ዕወጃ በመደበኛ ፍርድ ቤቶች ክርክር የተደረገበት የሪል ስቴት ህንጻ ሽያጭ ዉል አፈጻጸም የመጨረሻ ዉሳኔ በፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከተሰጠና ለክርክሩ መንስኤ የሆነዉ የሽያጭ ዉል ፈርሶ ሻጭ ንብረቱን በመያዝ የወሰደችዉን ክፍያ ለገዥ እንድትመልስ በተሰጠዉ ዉሳኔ ሻጭ/መልስ ሰጭ ቅር በመሰኘት የሰበር ዉሳኔዉ በህገ መንግስቱ ጥበቃ የሚደረግለትን ንብረት የማፍራት መብቴን የሚጥስ ስለሆነ ዉሳኔዉ ህገ መንግስታዊ ትርጉም ያሻዋል የሚል አቤቱታ ለህገ መንግስት አጣሪ ኮሚሽን ካቀረበች በኻላ ኮሚሽኑ ጉዳዩን መርምሮ ቅሬታዉን ዉድቅ በማድረግ የህገ መንግስት ትርጉም የማያስፈልገዉ ስለሆነ ጉዳዩ በመደበኛ ፍ/ቤት ታይቶ ዉሳኔ የሚሰጥበት የፍ/ር ጉዳይ ነዉ የሚል ዉሳኔ አሳልፏል፡፡ ይሁን እንጂ ሻጭ አሁንም በኮሚሽኑ ዉሳኔ ቅር በመሠኘት ቅሬታቸዉን ለፌዴሬሽን ም/ቤት ያቀረቡና የምክር ቤቱ ሰብሳቢ ወ/ሮ ኬርያትም አቤቱታዉን በመቀበል ተመርምሮ ዉሳኔ እስኪሰጥ ድረስ በፍ/ቤት የተጀመረዉን አፈጻጸም አግደዋል፡፡ ታድያ አነጋጋሪ የሆነዉ ይህ የምክር ቤቱ ስልጣን ከጉዳዩ ጋር አግባብነት ካለዉ ህግ አንፃር በመመርመር ይህን ፅሁፍ ለማዘጋጀት ወደድን፡፡
1.ከህገ መንግስት አንጻር፡-አንቀፅ 62 የፌደረሽን ም/ቤትን ስልጣን የሚደነግግ
አንቀፅ 82, የህገ መንግስት አጣሪ ኮሚሽን አወቃቀር ተደንግጓል፡፡
84 የኮሚሽኑን ስልጣንና ተግባር በዝርዝር ተጠቅሷል፡፡
2.የፌደረሽን ምክር ቤት አዋጅ ቁ 251/2001 ላይ አንቀፅ 5 መሠረት የፌደሬሽን ም/ቤት በኮሚሽኑ ተዘጋጅቶ በቀረበለት የህገ መንግስት ትርጉም ላይ የመጨረሻ ዉሳኔ የመስጠት ስልጣን እንዳለዉና በን/ቁ 2 መሠረት ደግሞ ለኮሚሽኑ ቀርቦ የህገ መንግስት ትርጉም አያስፈልገዉም ተብሎ የተሰጠን ዉሳኔ ላይ ቅር የተሰኘ ወገን በኮሚሽኑ ዉሳኔ ላይ ለምክር ቤቱ የይግባኝ ቅሬታ የማቅረብ መብት እንዳለዉ ይደነግጋል፡፡ በዚህ ድንጋጌ መሠረት የኮሚሽኑ ዉሳኔ የመጨረሻ እንዳልሆነና ምክር ቤቱ በይግባኝ የሚመለከተዉ እንደሆነ ነዉ፡፡
3.የህገ መንግስት አጣሪ ኮሚሽን አዋጅ ቁጥር 798/2005 መሠረት ኮሚሽኑ በፍርድ ቤት ወይም አስተዳደር አካል በተሰጠ የመጨረሻ ዉሳኔ ላይ የህገ መንግስት ትርጉም አለበት በሚል የሚቀርብለትን አቤቱታ መርምሮ ዉሳኔ የሚሰጥ አካል ሲሆን አቤቱታዉን መርምሮ ጉዳዩ የህገ መንግስት ትርጉም አያስፈልገዉም በማለት ሊወስን ወይም የህገ መንግስት ትርጉም ያሻዋል በሚል ከዉሳኔ ሀሳብ ጋር ጉዳዩን ለምክር ቤቱ ለዉሳኔ ሊያቀርብ እንደሚችልና በዚህ ሂደት በፍርድ ቤት ላይ ያሉ ክርክሮችን ሊያግድ ይችላል፡፡
በዚህ የህግ አግባብ መሠረት ሰሞኑን በፋና ብሮድካስት ዜና የተሰራጨዉ የኮሚሽኑ ዉሳኔና የምክር ቤቱ እርምጃ የህግ መሠረት ያለዉ በመሆኑ ከህግ አንፃር ሚድያዎች የሚሠሩት ዘገባ ሀላፊነት የጎደለዉ ህጉን ሳይመረምሩና በባለሙያ አስተያየት ሳያሰጡ መሆኑን አስተዉለናል፡፡
እርስዎስ ምን አስተያየት አለዎት..?
ተጻፈ 19/06/2012
በስራ ሂደቱ
ጂንካ፡

26/02/2020

❖❖❖የመገናኛ ብዙሐን እና የመረጃ ነፃነት አዋጅ ቁጥር 590/2000❖❖❖
መግቢያ
በእዚህ በመገናኛ ብዙሃን እና የመረጃ ነፃነት አዋጅ ቁጥር 590/2000 ውስጥ ዜጎች መረጃ የማግኘት ሕገ መንግስታዊ መብት እንዳላቸው እና የመረጃ ባለቤቶችም እንደሆኑ በግልጽ የሚያመላክቱ አንቀጾችና ተዛማጅ ድንጋጌዎች ሰፍረዋል፡፡ ይኸው የመረጃ ነፃነትን ሕግ የያዘው ክፍል ሦስት በአዋጁ ከአንቀፅ 11 እስከ አንቀፅ 39 ባሉ 29 አንቀፆች እና ፣ 90 ንዑሳን አንቀፆች የተከፋፈለ ነው፡፡
ይህ የመረጃ ነጻነት አዋጅ ህገ መንግስታዊ ዋስትና ያለውን የዜጎች መረጃ የማግኘት መብትን ተግባራዊ ማድረግ ዋና ዓላማ አድርጎ የተደነገገ ነው፡፡ እኛም በዛሬ ዝግጅታችን መረጃ የማግኘት፡ የመጠየቅ፡ መብትና የመስጠት ግዴታን አስመልክቶ ከአዋጁ አንፃር አንዳንድ ነጥቦችን ለማንሳት ወደድን፡፡
መረጃ ምንድ ነው ?
መረጃ ለሚለዉ የተለያየ ትርጉም ቢኖረዉም ከአዋጁ አንጻር ማንኛውም አካል እና በማንኛውም ጊዜ የተፈጠረ ወይም የተዘጋጀ ቢሆንም በመንግስት አካል ይዞታና ቁጥጥር ሥር የሚገኝ ሆኖ፡-
♠ማንኛውንም መዝገብ፣ ፋይል፣ በእጅ ወይም በማሽን የተጻፈ ረቂቅ፤
♠ማንኛውንም ማይክሮ ፊልም ማይክሮፊሽና በኤሌክትሮኒክ መልክ የወጣ መዝገብ ግልባጭ፤
♠ማንኛውም በነዚህ ማይክሮ ፊልሞች ላይ ያሉ ምስሎች ቅጂ፤
♠በኮምፒውተር ወይም በሌላ በማንኛውም መሳሪያ በመታገዝ የሚታዩ ፤የሚነበቡ ፤ የሚደመጡ ወይም የሚታወቁ፤በአጠቃላይ በማንኛውም ዓይነት ቅርጽ ወይም የማስተላለፊያ ዘዴ የሚገኝ ማንኛውንም መረጃ ያካትታል፡፡(እዚህ ላይ አዋጁ መረጃን መረጃ ለማለት በማስረጃ መደገፍ እንዳለበትና ወደሆነ ዐይነት ቅርፅ መለወጥ እንዳለበት የፅሁፉ አዘጋጅ ይረዳል)::
የመረጃ ነፃነት ከዐለም ዐቀፍ ህጎች አንፃር
በዓለም ላይ ከ 90 ሀገሮች በላይ የመረጃ ነፃነት ህግ አላቸው በ1766 የወጣው የስዊድን የፕሬስ ነፃነት ህግ የመጀመሪያው ነው፡፡ የመረጃ ነጻነት ተግባራዊነት ለዜጎች መሰረታዊ የዴሞክራሲያዊ መብቶች አከባበርና ለሰብአዊ መብቶች መረጋገጥ መሰረት እንደሆነ ይህ አለም አቀፍ ሰነድ ይጠቀሳል፡፡
የመረጃ ነጻነት ፡- የሰዎች የመናገርና ሃሳብን በነፃ የመግለጽ መብት የሰዎችን መረጃ የመፈለግ፣ የማግኘትና የማስተላለፍ መብትን ያካተተ ነው፡፡የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ እ.ኤ.አ በ1946 ዓ.ም በውሳኔ ቁጥር 59/I እንዳመለከተው የመረጃ ነጻነት ሰብአዊ መብትን ጨምሮ ለሁሉም መብቶች መከበር መሰረት እንደሆነ አረጋግጧል፡፡“Freedom of Information is a Fundamental Human Right and the Touchstone or all Freedoms to which the United Natioins is Consecrated”
በኢትዮጵያ ህገ መንግስት አንቀፅ 29 ላይ እንደተቀመጠው ማንኛውም ሰው መረጃ የማግኘት መብት እንዳለዉ በመደንገግ ይህ መብት በህገ መንግስቱ እዉቅናና ጥበቃ የሚደረግለት መብት መሆኑን እንረዳለን፡፡
የመረጃ ነፃነት ህግ (አዋጅ ቁጥር 590/2000 ) መሠረታዊ መርሆዎች ❖የመረጃ ነጻነት ህግ በሰፊ ግልፅነትና በውስን ክልከላ ላይ የተመሰረተ ነው፤
♠የመንግስት አካላት ቁልፍና ተገቢ የሆኑ መረጃዎችን አትሞ የማውጣት ግዴታ አለባቸው፤
♣የመንግስት አካላት በግልጽነትና ተጠያቂነት መንፈስ ሊሰሩ ይገባል፤
♦የተከለከሉ መረጃዎች በግልጽና በጠባቡ ሊተረጎሙ ይገባል፤
♣የመረጃ ጥያቄ በፍጥነትና ፍትሐዊ በሆነ መንገድ መስተናገድ አለበት፤
♠የመረጃ ጥያቄዎች ቅሬታ አሰማም ሥርዓት ሊዘረጋ ይገባል፤
❖የመንግስት አካላት ስብሰባዎች ለሕዝብ ክፍት ሊሆኑ ይገባል፤
♣ከመረጃ ነፃነት ህግ ጋር የሚቃረኑ ነባር ህጎች መናበብና መከለስ አለባቸው
♥በቅን ልቦና መረጃ አፈትላኪዎች ተገቢ የሆነ ህጋዊ ከለላ ሊያገኙ ይገባል የሚሉት መሠረታዊ መርሆዎቹ ናቸው፡፡
መረጃን የማግኘት መብት የዜጎች መረጃ የማግኘት መብት በህገ መንግሥቱ አንቀፅ 29 ላይ እንደተቀመጠው ማንኛውም ሰው መረጃ የማግኘት መብት አለው በሚለው መሰረት ማንኛውም ሰው ተነፃፃሪ ጥቅሞችን ለማስጠበቅ ሲባል ከማይገለፅ ውስን መረጃ በስተቀር ከማንኛውም መንግስታዊ አካል መረጃን የመጠየቅና የማግኘት መብት እንዳለው በአዋጁ አንቀፅ 12 ተደንግጎ ይገኛል፡፡ በዚህ አንቀፅ “ማንኛውም ሰው“ የሚለው አባባል መረጃ የመጠየቅ መብት ያላቸው ኢትዮጵያውያን ዜጎች ብቻ ሳይሆኑ የውጭ አገር ዜጎችም ጭምር እንደሚሆኑ መረዳት ይቻላል፡፡ በዚህ መሠረት ማንኛዉም ሰዉ ከመንግስት ተቋማት በህግ ከተገደቡ ጉዳዮች በስተቀር በመንግስት አካል ዘንድ የሚገኝ መረጃን፡ የመረጃ ምንጭን የመጠየቅ፡ የማወቅና የማግኘት መብት ሲኖረዉ በአንጻሩ የመንግስት ተቋማት መረጃዎችን የማሳወቅ፡ የመስጠት ግዴታ እንዳለባቸዉ መረዳት ይቻላል፡፡ ይህም የመንግስት አሰራርን ግልፀኝነት በማረጋገጥ ተጠያቂነትንና በተቋማቱ የተግባር አፈጻጸም የህብረተሰቡን ተሳታፊነት እና ባለቤትነት ለማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ሌላው በአንቀፁ የተሰጠው መረጃ የማግኘት መብት ሶስት አላባውያንን (Elements) ይዞ ይገኛል ይህ ማለት ደግሞ መረጃ ጠያቂው ያሉትን መብቶች የሚያሳይ ሲሆን እነሱም፡-1ኛ / መረጃን የመጠየቅ፣ 2ኛ / መረጃን የማግኘትና 3ኛ / መረጃን የማስተላለፍ መብቶች ሲሆኑ መረጃ ተደራሽ የሚሆኑባቸዉ መንገዶች ደግሞ መረጃ ለማግኘት በሚቀርብ ጥያቄና በተቋሙ ግዴታ መሠረት መረጃ ጠያቂዎች ማግኘት የሚፈልጉትን መረጃ ከሚከተሉት አማራጮች በአንዱ ወይም በሌላ እንዲሰጣቸው ወይም እንዲላክላቸው ሊጠይቁ ይችላሉ፡፡ እነዚህ ዋና ዋና ዘዴዎች ወይም ፎርሞች ተብለው የተለዩትም ቀጥሎ የተመለከቱት ናቸው፡-
☞በወረቀት ሕትመትና ፎቶግራፍ ;
☞በተለያዩ የኤሌክትሮኒክስ ዘዴዎች በድምጽና በምስል የተያዙ መረጃዎች( በሲዲ/ዲቪዲ፣ በፍላሽ ዲስክ፣…)
☞በኢሜይል ወይም በፋክስ
☞በማይክሮ ፊልም
☞በብሬይል ሊሆን ይችላል፡፡
መረጃዎች ይገለፃሉ፡፡

ማንኛውም ሰው እነዚህን መብቶች ለመተግበር የሚችልባቸው መንገዶች፡- የሚፈለገውን መረጃ መኖሩንና ያለመኖሩን በመጠየቅ፤ በመመልከት፤ ማስታወሻዎችን በመውሰድ ወይም ጥቅሶችን በመገልበጥ፤ የመረጃውን ትክክለኛ ግልባጭ በመውሰድ፤
በኤሌክትሮኒክስ ዘዴዎች ሁሉ እንዲሁም ከኮምፒዩተር ወይም ሌሎች መሳሪያዎች ላይ ታትመው የወጡ ቅጂዎችን በመውሰድ ነው፡፡ መረጃ የማግኘት መብት ሶስት ዋና ዋና ባላድርሻ አካላትን ያገናኛል፡፡ እነሱም:-
ሀ/ መረጃ ጠያቂ:- የምንለው አንድ መረጃን ፈልጎ ጥያቄ የሚያቀርብ ማንኛውም ግለሰብ ወይም ተቋም ሲሆን፡
ለ/መረጃ ሰጭ፡- የምንለው በእጁ መረጃው የሚገኝ የመንግስት አካል ማለት ነው፡፡
ሐ/ ቅሬታ ሰሚ ፡-የምንለው ደግሞ መረጃ ጠያቂው መረጃውን ጠይቆ ሊያገኝ ካልቻለ በአዋጁ አንቀፅ 31 ላይ በተቀመጠው የቅሬታ አቀራረብ ሥርዓት መሰረት ቅሬታ የሚሰማ ነው ፡፡
መረጃ ስለሚሠጥበት ቋንቋ:-አንቀፅ 30 ድንጋጌ መሰረት ለመንግስት አካል የቀረበው መረጃ ጥያቄ የተፈቀደለት አመልካች የጠየቀው መረጃ ፡-በመረጠው ቋንቋ የተዘጋጀ ከሆነ መረጃው አመልካቹ በመረጠው ቋንቋ ይሰጠዋል፡፡መረጃው አመልካቹ በመረጠው ቋንቋ ያልተዘጋጀ ከሆነ መረጃው በተዘጋጀበት ቋንቋ ለአመልካቹ መሰጠት አለበት፡፡
መረጃን አትሞ የማውጣት ግዴታ
መረጃን ሳይጠየቁ የማቅረብ ግዴታ በመንግስት አካላት ላይ የሚጥለው የአዋጁ አንቀጽ 13 ንዑስ ቁጥር 3 ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው በርካታ ዜጎች ለመረጃ ጥያቄ ወጪ መሸፈን የሚያዳግታቸው ሰዎች በቀላሉ መረጃ የሚያገኙበትን ሁኔታ ለማመቻቸት ታስቦ የተቀረጸ ነው፡፡
መረጃን ለሕዝብ ግልፅ በማድረግ መንግስት በሚያቅዳቸው የልማት ስራዎች በባለቤትነት እንዲሳተፉ ስለሚያግዝ ነው፡፡ ይህ ድንጋጌ የመንግስት አካላት በየድርጅታቸው ስላለው የመረጃ ጥያቄ አቀራረብ ስነ ስርዓት ዝርዝር ማብራሪያዎችን ተደጋግመው የሚቀርቡ ጥያቄዎችንና ምላሻቸውን የመ/ቤቱን አደረጃጀት መዋቅር ተግባርና ሃላፊነት የድርጅቱን ሃላፊዎችና የስራ ግዴታ እና መስሪያ ቤቱ ለህዝብ የሚሰጣቸው አገልግሎቶች ዝርዝር አትመው እንዲያወጡ ያስገድዳቸዋል፡፡
ማንኛውም የመንግስት አካል አስፈላጊ የሆነ ለውጥ ሲኖር የተለወጡ ነገሮች የታከሉበትን እና በዚህ አንቀጽ በንዑስ አንቀጽ /አንድ/ የተመለከተው ህትመት ቢያንስ በዓመት አንድ ጊዜ በማውጣት ለማንኛውም ጠያቂ ወዲያውኑ የህትመቱን ቅጂ መስጠት ወይም እንዲመለከት ማድረግ አለበት፡፡ ሆኖም እያንዳንዱ የመንግስት አካል በነዚህ ህትመቶች ውስጥ በዚህ አዋጅ ክፍል ሶስት የማይገለጹ መረጃዎችን በሚመለከቱ ድንጋጌዎች መሰረት መገለጽ የሌለባቸውን መረጃዎች አያካትትም፡፡
ማንኛውም የመንግስት አካል፡-
ሀ./ የህዝብ ጥቅም የሚመለከቱ ጠቃሚ ፖሊሲዎችና ውሳኔዎችን ይፋ በሚያደደርግበት ጊዜ ከውሳኔዎቹ ጋር የተያያዙ መረጃዎችን በሙሉ አትሞ ማውጣት አለበት፡፡
ለ./ የአስተዳደራዊ ፤ የዳኝነትም ሆነ የዳኝነት ነክ ውሳኔዎች ሲሰጥ የሃሳብ ልዩነት ካለም ከነልዩነቱ ለማንኛውም መረጃ ጠያቂ የህትመቱን ቅጂ መስጠት ወይም እንዲመለከተው ማድረግ አለበት፡፡
ሐ./ በግልጽነትና ተጠያቂነት መርሆዎች መሰረት ማንኛውም አይነት ፕሮጀክት ተግባራዊ ከማድረጉ በፊት ለጠቅላላው ህዝብ ወይም ጥቅማቸው ለተነካባቸው ወይም ሊነካባቸው ለሚችሉ ወገኖች ከፕሮጀክቱ ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን አትሞ ማውጣት ወይም ማሳወቅ ይኖርበታል፡፡
የህዝብን ጥቅም የሚያመለክቱ ፖሊሲዎችና ውሳኔዎችን ስለማሳታም
የሕዝብ ጥቅምን የሚመለከቱ ፖሊሲዎች ከሕዝብ ሕይወት ጋር የተያያዘ ወይም በሕዝብ ሕይወት ላይ ለውጥ የሚያስከትል ውጤት ያለው እያንዳንዱን ጉዳይን አቅፈው ይይዛሉ፡፡ፖሊሲዎቹ ሊያካትቱ የሚችሏቸው የሕዝብ ጥቅሞች ከብዙ በጥቂቱ የሚከተሉት ናቸው፡፡
♠ንፁህ የመጠጥ ውኃ ፤ ንፁህ አየር .፤ መልካም ጤና ፤ ከፍተኛ የሥራ ዕድል ፤ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያለው አዲስ ግኝት ፤
♠በሥራ ላይ ያሉትን ለሕዝብ ጥቅም ተብለው የሚታቀዱ የአጭርና የረጅም ጊዜ ዕቅዶችን /ስትራቴጂ/ የሚወጡ ፖሊሲዎችን፤
♠ለወደፊት የታቀዱ ፖሊሲዎች ከሆኑም አፋጣኝ ምላሽ ለሚሹ ጉዳዮች የሚወጡ ፖሊሲዎች በሚመለከት ለምሳሌ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን ለመቋቋም የሚወጡ ፖሊሲዎች፣ የሕዝብ ጥቅምን የሚመለከቱ ውሳኔዎችንም አትሞ ማውጣት ይገባል ፡፡
ቅሬታ አቀራረብ ፡-በአንቀጽ 31 እና 34 መሠረት መረጃ ጠይቆ የተከለከለ ወይም በተሰጠዉ አገ/ት ያልረካ ሰዉ ቅሬታዉን ማቅረብ የሚችል ሲሆን የቅሬታ አቀራረብ ሥርዓቱ የሚከተሉት ደረጃዎች ይኖሩታል፡፡
1.አገልግሎቱን ለሰጠው ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ፡- የመረጃ ጥያቄ አቅርቦ ውድቅ የተደረገበት ወይም ተገቢ አገልግሎት አላገኘሁም የሚል ቅሬታ ያለው መረጃ ጠያቂ መጀመሪያ እዚያው አገልግሎቱን ለሰጠው ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ቅሬታውን ማቅረብ ይችላል፡፡
2.ለመሥሪያ ቤቱ የበላይ ኃላፊ:- የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው ያቀረበውን ቅሬታ ካልፈታለት ውሳኔውን በመቃወም ለመሥሪያ ቤቱ የበላይ ኃላፊ አቤቱታ አቅርቦ ይስተናገዳል፡፡
3.ለሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም፡-በመሥሪያ ቤቱ የበላይ ኃላፊ ውሳኔ ቅር የተሰኘ ወይም በአግባቡ አልስተናገድኩም የሚል የመረጃ ጠያቂ ለሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም ይግባኝ ማቅረብ ይችላል፡፡ 4.ለፍርድ ቤት፡- ለህዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም የቀረበው የይግባኝ አቤቱታ ውድቅ የተደረገበት መረጃ ጠያቂ አቤቱታውን ለፍርድ ቤት ሊያቀርብ ይችላል ሆኖም ፍርድ ቤት የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ ይሆናል፡፡
የማይገለፁ መረጃዎ
በአዋጁ አንቀጽ12 የተመለከተው መረጃ የማግኘት መብት በዚህ ክፍል ስር ከተደነገጉ ገደቦች በስተቀር መረጃ እንዳይገለጽ በሚከለክሉ ማንኛውም የህግ ክልከላዎች ሊገደብ አይችልም፡፡ መረጃ የማግኘት መብት የተገደበባቸዉ ጉዳዮች የሚከተሉትን ያካትታል፡፡
♠ሶስተኛ ወገንን የሚመለከቱ የግል መረጃዎች:
♠ሶስተኛ ወገንን የሚመለከቱ የንግድ መረጃዎች
♠የግለሰቦች የንብረት ደህንነት ሰለመጠበቅ
♣የህግ አስከባሪ የፍርድ ምርመራ ስራዎች ጥበቃ
♥በፍርድ ምርመር ሂደት እንዳይገለፁ ጥበቃ ስለሚደረግላቸው መረጃዎች
♦ስለመከላከያ ደህንነትና ዓለም አቀፍ ግንኙነት
♥የካቢኔ ሰነዶች
♥የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ጥቅሞችና የፋይናንስ ደህንነትን እንዲሁም የመንግስት ድርጅቶችን የንግድ እንቅስቃሴ ስለሚመለከቱ መረጃዎች
♥የመንግስት የስራ ሰነዶች መረጃ የተከለከሉ ናቸዉ፡፡
መዉጫ፡- ሲጠቃለል ማንኛዉም የመንግስት ተቋም የሚከዉናቸዉ ተግባራት ያለህብረተሰቡ ተሳትፎ ማሳካት አዳጋች ስለሆነ የመንግስት ተቋማት በአዋጁ መሠረት መረጃዎችን ከመጠየቃችን በፊትም ሆነ ስንጠየቅ መረጃዉን የማሳወቅና የመረጃ ምንጩን የመስጠት ግዴታችንን ልንወጣ ይገባል፡፡ ዜጎችም እንዲሁ.......!! የዕለቱ መልዕክታችን ነዉ.........አጠቃለልን፡፡
ተጻፈ 18/06/2012
ጂንካ፡
በስራ ሂደቱ፡

Address

Jinka

Telephone

+251916452747

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when በደቡብ ኦሞ ዞን ፍትህ መምሪያ የፍትሀብሄር ፍትህ አስተዳደር ዋና የስራ ሂደት posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to በደቡብ ኦሞ ዞን ፍትህ መምሪያ የፍትሀብሄር ፍትህ አስተዳደር ዋና የስራ ሂደት:

Share

Category