27/02/2020
የፌዴሬሽን ምክር ቤት እና የህገ መንግስት አጣሪ ኮሚሽን ስልጣንና የአሰራር ስርዐት፡
ሰሞኑን በፋና ቴሌቪዥን የዜና ዕወጃ በመደበኛ ፍርድ ቤቶች ክርክር የተደረገበት የሪል ስቴት ህንጻ ሽያጭ ዉል አፈጻጸም የመጨረሻ ዉሳኔ በፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከተሰጠና ለክርክሩ መንስኤ የሆነዉ የሽያጭ ዉል ፈርሶ ሻጭ ንብረቱን በመያዝ የወሰደችዉን ክፍያ ለገዥ እንድትመልስ በተሰጠዉ ዉሳኔ ሻጭ/መልስ ሰጭ ቅር በመሰኘት የሰበር ዉሳኔዉ በህገ መንግስቱ ጥበቃ የሚደረግለትን ንብረት የማፍራት መብቴን የሚጥስ ስለሆነ ዉሳኔዉ ህገ መንግስታዊ ትርጉም ያሻዋል የሚል አቤቱታ ለህገ መንግስት አጣሪ ኮሚሽን ካቀረበች በኻላ ኮሚሽኑ ጉዳዩን መርምሮ ቅሬታዉን ዉድቅ በማድረግ የህገ መንግስት ትርጉም የማያስፈልገዉ ስለሆነ ጉዳዩ በመደበኛ ፍ/ቤት ታይቶ ዉሳኔ የሚሰጥበት የፍ/ር ጉዳይ ነዉ የሚል ዉሳኔ አሳልፏል፡፡ ይሁን እንጂ ሻጭ አሁንም በኮሚሽኑ ዉሳኔ ቅር በመሠኘት ቅሬታቸዉን ለፌዴሬሽን ም/ቤት ያቀረቡና የምክር ቤቱ ሰብሳቢ ወ/ሮ ኬርያትም አቤቱታዉን በመቀበል ተመርምሮ ዉሳኔ እስኪሰጥ ድረስ በፍ/ቤት የተጀመረዉን አፈጻጸም አግደዋል፡፡ ታድያ አነጋጋሪ የሆነዉ ይህ የምክር ቤቱ ስልጣን ከጉዳዩ ጋር አግባብነት ካለዉ ህግ አንፃር በመመርመር ይህን ፅሁፍ ለማዘጋጀት ወደድን፡፡
1.ከህገ መንግስት አንጻር፡-አንቀፅ 62 የፌደረሽን ም/ቤትን ስልጣን የሚደነግግ
አንቀፅ 82, የህገ መንግስት አጣሪ ኮሚሽን አወቃቀር ተደንግጓል፡፡
84 የኮሚሽኑን ስልጣንና ተግባር በዝርዝር ተጠቅሷል፡፡
2.የፌደረሽን ምክር ቤት አዋጅ ቁ 251/2001 ላይ አንቀፅ 5 መሠረት የፌደሬሽን ም/ቤት በኮሚሽኑ ተዘጋጅቶ በቀረበለት የህገ መንግስት ትርጉም ላይ የመጨረሻ ዉሳኔ የመስጠት ስልጣን እንዳለዉና በን/ቁ 2 መሠረት ደግሞ ለኮሚሽኑ ቀርቦ የህገ መንግስት ትርጉም አያስፈልገዉም ተብሎ የተሰጠን ዉሳኔ ላይ ቅር የተሰኘ ወገን በኮሚሽኑ ዉሳኔ ላይ ለምክር ቤቱ የይግባኝ ቅሬታ የማቅረብ መብት እንዳለዉ ይደነግጋል፡፡ በዚህ ድንጋጌ መሠረት የኮሚሽኑ ዉሳኔ የመጨረሻ እንዳልሆነና ምክር ቤቱ በይግባኝ የሚመለከተዉ እንደሆነ ነዉ፡፡
3.የህገ መንግስት አጣሪ ኮሚሽን አዋጅ ቁጥር 798/2005 መሠረት ኮሚሽኑ በፍርድ ቤት ወይም አስተዳደር አካል በተሰጠ የመጨረሻ ዉሳኔ ላይ የህገ መንግስት ትርጉም አለበት በሚል የሚቀርብለትን አቤቱታ መርምሮ ዉሳኔ የሚሰጥ አካል ሲሆን አቤቱታዉን መርምሮ ጉዳዩ የህገ መንግስት ትርጉም አያስፈልገዉም በማለት ሊወስን ወይም የህገ መንግስት ትርጉም ያሻዋል በሚል ከዉሳኔ ሀሳብ ጋር ጉዳዩን ለምክር ቤቱ ለዉሳኔ ሊያቀርብ እንደሚችልና በዚህ ሂደት በፍርድ ቤት ላይ ያሉ ክርክሮችን ሊያግድ ይችላል፡፡
በዚህ የህግ አግባብ መሠረት ሰሞኑን በፋና ብሮድካስት ዜና የተሰራጨዉ የኮሚሽኑ ዉሳኔና የምክር ቤቱ እርምጃ የህግ መሠረት ያለዉ በመሆኑ ከህግ አንፃር ሚድያዎች የሚሠሩት ዘገባ ሀላፊነት የጎደለዉ ህጉን ሳይመረምሩና በባለሙያ አስተያየት ሳያሰጡ መሆኑን አስተዉለናል፡፡
እርስዎስ ምን አስተያየት አለዎት..?
ተጻፈ 19/06/2012
በስራ ሂደቱ
ጂንካ፡