17/09/2024
በዝምታ የሚናገሩት የሥነ-ሕይወቱ ሊቅ፤
ፖለቲከኛው ታጋይ፣ ባለውለታችን ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ።
***
(ሄኖክ ስዩም - ለድሬ ቲዩብ)
ቤተሰቦቻቸው ለኢትዮጵያ የጠቀሙ ኢትዮጵያውያንን አበርክተዋል። የጴጥሮስ ልጆች የኢትዮጵያ ልጆች ናቸው። ለኢትዮጵያ የኖሩ፣ ባለውለታዎቻችን።
ዝምተኛው ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ በፀጥታቸው የሚጮሁ፣ በዝምታቸው የሚደመጡ፤ ሹመት ሳይኾን እምነት በቦታቸው ያፀናቸው። ላመኑበት የኖሩ ድንቅ ሰው።
ለሃድያ ህዝብ ክብር አለኝ። በተለይ በተደጋጋሚ የሚደርስበትን ጫና ተቋቁሞ እንደ ሀገር የመታገል ምሳሌ ጭምር የሚባሉትን ፕሮፌሰር በየነ ይወክሉኛል ብሎ መርጦ ሌላ መወከል በሚያስፈራበት ሰዓት ካከበርነው ፓለቲከኛ ጋር አስተዋውቀውናል።
ሰውዬው በፓለቲካው መድረክ አደባባይ ወጥተው ሲታዩ ላብራቶሪው ውስጥ የሙያቸውን አበርክተው ነበር። የ Tropical Diseases ተመራማሪው በየነ ወደ ፓለቲካል ኢኮኖሚው አደባባይ ሲመጡ ኤችአይቪ/ኤድስ እና ሳምባ ነቀርሳ ላይ የሚያደርጉትን ጥናት ሜዳ ሳይበትኑ ነበር። እንደ ፌዴራሊዝሙ የወባ በሽታን ያጠኑ፣ ለሰው ብቻ ሳይሆን ለሰው ህዋስ ጭምር ቅርብ የነበሩ የሳይንስ ሰው።
ፓርላማ ገብተው ለሀገራቸው ይበጃል ያሉትን የሚናገሩት እና የሚፅፉት ፕሮፌሰር በየነ የተማርንበትን Introductory to Basic Biology አዘጋጅተው ለህትመት ያበቁ መምህር ናቸው።
ስራቸውን አክባሪ፤ ተማሪዎቻቸው ጥንቅቅ ብለው የሚመጡ በሚል ከዝግጅታቸው የተነሳ የሚያደንቋቸው መምህር፣ ቀዳሚው የሥነ ሕይወት ትምህርት ክፍል ባልደረባ፣ ረዥም ዘመን በትምህርት ክፍሉ የጀርባ አጥንት የነበሩ ባለውለታ።
የዛሬ 75 ዓመት በገራዶቹ ምድር ሾኔ ጉያ ባለችው ገጠር የተወለዱት ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ የሥነ ሕይወት ሰው ናቸው። የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በባዮሎጂ ከወሰዱ በኋላ በሳይንሱ ተወስደው ቀጠሉ። ሁለተኛ ዲግሪያቸውን አሜሪካን ሀገር ከሚገኘው ዊስኮንሰን ዩኒቨርሲቲም የወሰዱት ሁለተኛ ዲግሪ በዚሁ የጥናት መስክ ነበር። ከዚያም በህዝብ ጤና አጠባበቅ እና በተላላፊ በሽታዎች የዶክትሬት ዲግሪያቸውን በሀገረ አሜሪካ ከቱለን ዩኒቨርሲቲ ተቀበሉ፡፡
በፓለቲካው መድረክ ያለ ድካም የምናያቸው ፕሮፌሰር በየነ አርባ አምስት ዓመታት ለሚጠጋ ዕድሜ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የባዮሎጂ መምህር ኾነው ያለ መጉደል በመኖር ነው።
የፓለቲካ ሰዎች የሰላማዊ ትግል ተምሳሌት ሲሉ ይገልጿቸዋል። ያነሱት የላብራቶሪ መሳሪያ ነው። ከዚያ ሌላ ደግሞ ለሀገሬ ይበጃል ያሉትን ሀሳብ።
ዝምታቸው የሚናገር ድፍረታቸው የሚያስገርም ትጋታቸው የሚያስቀናው ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ ሀገር ካስተማረቻቸው ሙያ ለሀገር በሚል ሳይነጠሉ ማስተማር ከመብት ትግል ሳይጣላባቸው ኖረዋል። ፓለቲካ ጠብ በኾነበት ባህላችን ሀሳብ እንጂ ጠላትነት መርሃቸው ሳይኾን ሰክነው አስክነዋል።
ከብዙ ጠንካራ ተመራማሪዎች ጀርባ የእሳቸው አብሮነት አለ። ጥናትና ምርምሮችን በመምራት እና በማስተባበር ለውጤት ያበቋቸው ምርምሮች ብዙ ናቸው። በሀገር ውስጥ እና በዓለም አቀፍ ጆርናሎች የሥነ ህይወት ሳይንስ ዘርፍ ላይ ላወጧቸው የምርምር ህትመቶችና የማስተማር አበርክቷቸው። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሙሉ ፕሮፌሰርነት ማዕረግ ሰጥቷቸዋል።
በእርግጥም ሀገራቸውን ይወዱ ነበር። ለሀገራቸውም ኖረዋል። በሙያቸው ሀገር አኑረዋል። ለተበደለ ድምፅ ሆነዋል።
የሚበድል ሥርዓትን በሰለጠነ ፓለቲካ ታግለዋል። ሞኝ ወይም ፈሪ አልነበሩም፤ ፍርሃትን አሽቀንጥረው የአደባባይ ፓለቲከኛ፣ የክፍል ውስጥ መምህር፣ የላብራቶሪ ሳይንቲስት በመሆን ለአመኑበት ኖረዋል። በኢትዮጵያ ጉዳይ ተስፋ የማይቆርጡት ምሁር ስለ ኢትዮጵያ ደክመው አሁን ከዚህ ዓለም ድካም አርፈዋል። ለቤተሰቦቻቸው፣ ለተማሪዎቻቸው፣ ለወዳጆቻቸው፣ ለሀገራቸው መጽናናት ይሁን።