25/05/2026
⚖️ የኮምቦልቻ ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት ለባህላዊ ፍርድ ቤት ዳኞችና ፀሐፊዎች የአቅም ግንባታ ሥልጠና እና የሥራ ማስጀመሪያ መድረክ አደረገ
ግንቦት 17 ቀን 2018 ዓ.ም ኮምቦልቻ ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት
፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤ //// //// ፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤፤
የኮምቦልቻ ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት ከከተማ አስተዳደሩ ባገኘው የገንዘብ ድጋፍ፣ በከተማዋ በሚገኙ 20 ቀበሌዎች ለተዋቀሩ የባህል ፍርድ ቤት ዳኞች እና ፀሐፊዎች ያዘጋጀው የአቅም ግንባታ ሥልጠና እና የሥራ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር በደማቅ ሁኔታ አካሂዷል፡፡
ከግንቦት 13 እስከ 14 ዓ.ም ለሁለት ቀናት በቆየው በዚህ ሥልጠና ላይ 100 የባህል ፍርድ ቤት ዳኞች፣ 20 ጸሐፊዎች እና 5 አበጋሮች ተሳትፈዋል፡፡
📌 የመድረኩ ክብር እንግዳ የነበሩት የአማራ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ ክብርት ወ/ሮ ፋንቱ ተስፋዬ በመክፈቻ ንግግራቸው፤ አማራጭ የሙግት መፍቻ ሥርዓቶችን ማጠናከር በክልሉ መንግሥት ከፍተኛ ትኩረት የተሰጠው መሆኑን ገልጸዋል። አፈ-ጉባኤዋ አክለውም፣ የባህል ፍርድ ቤቶች በማቋቋሚያ አዋጁ በተቀመጠው አቅጣጫ መሠረት የሴቶች እና የሕፃናትን መብት ማስከበር ላይ ልዩ ትኩረት አድርገው መሥራት እንዳለባቸው በአጽንዖት አሳስበዋል።
📌የደቡብ ወሎ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ክብርት ወ/ሮ ትዕግስት ዳኛቸው በመድረኩ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት የባህል ፍርድ ቤቶች ከመደበኛው የሕግ ሥርዓት ጎን ለጎን ፍትሕን ተደራሽ በማድረግ ረገድ ያላቸውን የማይተካ ሚና አብራርተዋል።
📌የደቡብ ወሎ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት የተከበሩ አቶ ምትኬ ወርቁ በበኩላቸው፣ የሃይማኖት እና የባህል ፍርድ ቤቶች በሕገ-መንግሥቱ ዕውቅና የተሰጣቸው መሆኑን ጠቅሰው፣ የክልሉ መንግሥት ከሕግ ማዕቀፍ ማውጣት ጀምሮ ተቋማቱን በማደራጀት ረገድ አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
📌 የኮምቦልቻ ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት የተከበሩ አቶ ተሾመ በላይ እንደገለጹት፤ ባህላዊ ፍርድ ቤቶች ከመደበኛው የሕግ ሥርዓት ጎን ለጎን የፍትሕ ተደራሽነትን በማረጋገጥ ረገድ የማይተካ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ። እነዚህ ተቋማት ማኅበረሰባዊ አለመግባባቶችን በውይይትና በዕርቅ በመፍታት፣ ሕዝባዊ ትስስርና አንድነት እንዳይላላ በማድረግ ረገድ ግንባር ቀደም መሆናቸውን አብራርተዋል። በተጨማሪም የከተማ አስተዳደሩ ይህ ፕሮግራም እንዲሳካ ላደረገልን የገንዘብ ድጋፍ ፍርድ ቤቱ ልባዊ ምስጋናዬን አቀርባለሁ ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
ፕሬዝዳንቱ አክለውም የተዘጋጀው ሥልጠና ዋና ዋና ዓላማዎች ጠቁመዋል፦
⚖️ የሕግ ግንዛቤን ማሳደግ፦ በቀበሌ ደረጃ የተዋቀሩ የባህል ዳኞች ያላቸውን የሕግ እውቀት ይበልጥ ማበልጸግ፤
⚖️ አሠራርን ማዘመን፦ የሰነድ አያያዝ እና የፀሐፊነት ተግባራትን በዘመናዊና ስልታዊ መልኩ እንዲመሩ ማስቻል፤
⚖️ ቅንጅታዊ አሠራርን መፍጠር፦ ከመደበኛው የፍትሕ አካላት ጋር የተናበበና የተቀናጀ የሥራ ግንኙነት መመሥረት።
ይህ በቀበሌ ደረጃ የሚከናወን የዳኝነት ሥርዓት የማኅበረሰቡን እንግልት፣ ጊዜና ወጪ ከመቀነሱም በላይ፣ ጉዳዮች በአጭር ጊዜና በሰላማዊ መንገድ ተቋጭተው ለከተማዋ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ተገልጿል።
የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ አቶ ሁሴን አህመድ በበኩላቸው፣ ምክር ቤቱ የባህል ፍርድ ቤቶችን ወሳኝ ምሰሶነት በመረዳት የበጀትና መሰል ድጋፎችን እያደረገ እንደሚገኝና ወደፊትም ድጋፉ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።
ስልጠናውን የሰጡት የኮምቦልቻ ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት ዳኛ በሆኑት አቶ መንገሻ እያሴ ሲሆኑ
⚖️ የባህል ዳኞች የሕግ ግንዛቤያቸውን እንዲያሳድጉ፣
⚖️ የሰነድ አያያዝ እና የፀሐፊነት ተግባራትን በዘመናዊ መልኩ እንዲመሩ፣
⚖️ ከመደበኛው የፍትሕ አካላት ጋር ተቀናጅተውና ተናበው መሥራት እንዲችሉ ለማስቻል እንደሆነ አስገንዝበዋል።
የሥልጠናው ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት፣ የተሰጠው ሥልጠና የሕግ ግንዛቤያቸውን እንደሚያሳድግላቸው እና ህብረተሰቡን ያለአስፈላጊ እንግልት እና ወጭ እንደሚያስቀሩ ገልጸው፤ በቀጣይ አገልግሎታቸው በገለልተኝነት፣ ያለአድልዎ፣ ዕርቅን በማስቀደም ማኅበረሰባቸውን በቅንነት ለማገልገል ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።© #ኮምቦልቻ
ይህ የቴሌግራም ቻናል የኮምቦልቻ ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት ነው፡፡ በዚህ ቻናል ፡- ✅ ፍርድ ቤቱ የሚያከናውናቸውን አስተማሪ ፣ የሚሰሩ ስራዎች አስቼኳይና አስፈላጊ መረጃዎችን የሚጋሩበት...