01/09/2015
#ችሎት - እውነተኛ ገጠመኞች
(1)
ልጁ በሸንኮራ አገዳ የመኪና የጎን መብራት በመስበር ይከሰስና ፍርድ ቤት ይቀርባል። ኋላ ላይ ዳኛዋ ሲጠይቁት «ኧረ እኔ ሸንኮራ የሚባል አልያዝኩም - ገና ሸንኮራ ልገዛ እየሄድኩ ነበር . . .» ሲል ይመልሳል።
ዳኛዋ ወደ ምስክሩ ዞረው «አንተ ያየኸው ምንድነው?» ሲሉ ይጠይቁታል።
ምስክሩም « የተከበሩ ዳኛ ሸንኮራ ይዞ ነበር። ከዚያ በሸንኮራው የመኪናውን የጎን መብራት ሰብሮ አለፈ። ፖሊስ ጣቢያ ከደረሰ በኋላ ነው እንደውም ሸንኮራውን የበላው» በማለት ይመልሳል።
ዳኛዋም ወደ ተከሳሹ ዞረው «ኤግዚቢቱን በላኸው ማለት ነው?»
- - - - - -
(2)
ለምስክርነት የቀረቡት ሴት እድሜያቸው የገፋ አሮጊት ናቸው። ምስኪንነታቸው ከፊታቸው የሚነበብና በጣም የሚያሳዝን ገጽታ ያላቸው ሴትዮ ነበሩ። ከምስክር ወንበር ላይ ተቀምጠው ሌሎች ሃተታዎች ከተነገራቸው በኋላ ጥያቄ ይጠየቁ ጀመር፦
ዳኛዋ ፦ እድሜዎት?
እሳቸው፦ 25
በችሎት የታደመው ሰው ሁሉ ሳቀ። ዳኛዋም የታፈነ ሳቃቸውን እንደምንም በፈገግታ ሸፍነው አሳለፉ ። እማማ ተሸማቀቁ። እኔን! አልኩ በልቤ። የሰዉን መሳቅ አይተው የተሸማቀቁት እማማ ያጠፉት አንድ ጥፋት እንዳለ ተሰምቷቸው እሷን ሊያስተካክሉ የተናገሯት ነገር ሌላ ሳቅ ፈጠረች። ከዚያ በኋላ ምን እንደተሰማኝ ማስታወስ አልቻልኩም። እማማ ያሉት እንዲህ ነበር ፥
«ካነሰ እጨምራለሁ»