04/09/2025
የመኖሪያ ቤት ኪራይ ቁጥጥር እና አስተዳደር አዋጅ ቁጥር 1320/2016 በአከራይ እና በተከራይ መካከል የኪራይ ውሎች የሚፈጸሙት በተቆጣጣሪ አካል በተያዘው ጉዳይ በቤቶች አስተዳደር ጽ/ቤት ፊት መሆኑን፤አለመግባባቶች መነሻ ያደረገ አቤቱታ በአከራይም ሆነ በተከራይ በመጀመሪያ ደረጃ ለተቆጣጣሪ አካል እንደሚቀርብ፣በ2ኛ ደረጃ ለቅሬታ ሰሚ ኮሚቴ እንዲሁም በመጨረሻም በይግባኝ ደረጃ ለፍ/ቤት መሆኑን የአዋጁ ደንጋጌዎች ያስረዳሉ፡፡ሆኖም ውሳኔው በምን አግባብ ሊፈጸም እንደሚችል በአዋጁም ሆነ በመመሪያው ላይ ተገቢ ድንጋጌ የለም፡፡
ይህ ደግሞ በአከራይ እና ተከራይ መካከል የሚነሱ አለመግባባቶች ከዚህ ቀደም ዜጎች ለፍ/ቤት የሚያቀርቡትን አቤቱታ ያስቀረ ነው፡፡
በዚህ ረገድ የቤት ኪራይ ውሎች በተቆጣጣሪ አካል ዘንድ እየተደረጉ መሆኑ አገልግሎት በወቅቱ እስከተሰጠ ጊዜ ድረስ እና አከራይ እና ተከራይ ላይ መጉላላት እስካላስከተለ ድረስ ችግር ያለው አይደለም፡፡በተግባር ግን በአከራይ እና በተከራይ በዚህ ረገድ መጉላላት እየደረሰ መሆኑ በየቤቶች አስተዳደር ጽ/ቤቶች ያለው ሰልፍ ገላጭ ነው፡፡በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በወረዳ ደረጃ ያለው ቤቶች አስተዳደር ጽ/ቤት ቀሪ በመደረጉ ይህ አገልግሎት እየተሰጠ ያለው በክ/ከተማ ደረጃ በመሆኑ በክ/ከተማ ደረጃ ያለው የቤቶች አስተዳደር ጽ/ቤት ከዚህ ቀደም በስሩ ባሉ ከ10 ያላነሱ ወረዳዎች ሲሰጥ የነበረው አገልግሎት በክ/ከተማ መወሰኑ አከራይም ሆነ ተከራይ አገልግሎቱን ለማግኘት የሚኖርበትን ውጣ ውረድ መገመት አያዳግትም፡፡
እንዲሁም ውሉ በተቆጣጣሪ አካል ብቻ ተዘጋጅቶ መቅረቡ መካተት ያለባቸውን የአከራይን እና የተከራይን ሀሣብ እንዳይኖረው የሚያደርግ በመሆኑ በፍ/ብ/ህጉ በጠቅላላ የውል ህግ የተቀመጠውን የተዋዋይ ወገኖች የመዋዋል ነፃነት ላይ ገደብ የጣለ ነው።
ሌላው ከዚህን ቀደም በአከራይ እና በተከራይ መካከል የሚኖር አለመግባት ለፍ/ቤቶች እየቀረቡ ሲታዩ የመጨረሻ ውሳኔ ለመሰጠት ጊዜ የሚፈጅ መሆኑ አከራካሪ አይደለም፡፡ሆኖም ግን ዜጎች ፍትህ አገኛለው ብሎ ከማመን አንጻር ከአስተዳደር አካላት ይልቅ ፍ/ቤትን የሚመርጡበት ሁኔታ መኖሩን ለማወቅ አደጋች አይደለም፡፡ፍ/ቤቶች ለሚሰጡት ዳኝነት የግራቀኙን ክርክር እና ማስረጃ ከህግ አንጻር ለመመዘን የሚያስችል ተቋማዊ አሰራር፣የህግ ስነ ስርዓት፣እንዲሁም ህግን ለመተርጎም የሚያስችል ለጉዳዩ አግባብነት ያለው ልምድ እና የትምህርት ደረጃ የሚያሟላ ባለሙያ አላቸው፡፡በአስተዳደር አካል የሚሰጥ ዳኝነት ከሚኖረው ፍጥነት ውጪ አንድ ፍትኃዊ ውሳኔ ለመስጠት በፍ/ቤቶች ተሟልቶ የሚገኘውን ሂደት ያሟላ ነው ተብሎ አይገመትም፡፡ከዚህ አንጻር በዚህ አዋጅ አለመግባባት የሚፈታበት መንገድ በቅድሚያ ለአስተዳደር አካላት እና በእነሱ ስር ለተቋቋመ ቅሬታ ሰሚ ኮሚቴ መሰጠቱ እንዲሁም የተሠጠውን ውሳኔ ማነው የሚያስፈፅመው የሚለው ጉዳይ በአዋጁ አለመካተቱ በአከራይም ሆነ በተከራይ ላይ እያስከተለ ያለው ችግር መፈተሸ አለበት።