Abrham Yohannes Law Corner

Abrham Yohannes Law Corner Topics on Ethiopian law and judicial trends Views and Opinions on current legal topics

06/09/2022

ይዞታ አስተዳደር ሰ/መ/ቁጥር 215098

በፕሮፖርሽን ካርታ ውስጥ ተካትተው የሚገኙ ይዞታዎች ውስጥ የሚገነቡ አጥርም ሆነ ሌላ ግንባታ ሊከናወን የሚችለው የግንባታ ፈቃድ ተጋሪ የሆኑ ግለሰቦች ለግንባታው ፈቃዳቸውን ሲሰጡ ነው።

በዚህ መዝገቡ የችሎቱ ሐተታ እንደሚከተለው ይነበባል።
በተለያዩ ምክንያቶች መሬቱ ተከፍሎ መስጠት ካልተቻለ የተነፃፃሪ የመሬት ድርሻ ይዞታ ካርታ የሚሰጥ መሆኑ በይዞታ አስተዳደር አግልግሎት አሰጣጥ መመሪያ ቁጥር 12/2004 አንቀፅ 13.1 የተመለከተ ሲሆን አሁን በተያዘው ጉዳይም ከላይ እንደተመለከተው ተጠሪዎችና አመልካቾች የመፀዳጃ ቤት የሚገነቡላቸው ግለሰቦች ለይዞታቸው ያላቸው የይዞታ ማረጋገጫ ሰነድ በተነፃፃሪ የተሰጠ ሲሆን በዚህ አግባብ የይዞታ ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ከተሰጠ ደግሞ በጋራ በግቢው ውስጥ የሚኖሩ ባለይዞታዎች በጋራ ተስማምተው ካልመጡ በተናጠል ለማልማት የማይፈቅድላቸው መሆኑን ከአንቀፅ 13.6 እና ከተነፃፃሪ ካርታ አሰጣጥ አጠቃላይ ግብና አላማ ለመረዳት የሚቻል ሲሆን አሁን በያዝነው ጉዳይም የአሁን ተጠሪዎች መፀዳጃ ቤቱ እንዲገነባ ፈቃዳቸውን የሰጡ ስለመሆኑ የሚያመለክት ግልጽ ማስረጃ ወይንም የፈቃድ መስጫ ሰነድ ሆኖ ተረጋግጦ የቀረበ ማስረጃ አለመኖሩ፤ ቃለጉባኤውም በዚህ አግባብ የሚያረጋግጥ አለመሆኑ በስር ፍርድ ቤት የተረጋገጠ ከመሆኑ አንፃር የስር ፍርድ ቤቶች የተነፃፃሪ ካርታው ተጋሪዎች ፍቃድ ሳይገኝ በአመልካቾች በኩል መፀዳጃ ቤቱን ለመገንባት መንቀሳቀሳቸውን የሁከት ተግባር ነው ማለታቸው የሚነቀፍ ሆኖ [አልተገኘም]።
የአዲስ አበባ አስተዳደር ይዞታ አስተዳደር አግልግሎት አሰጣጥ መመሪያ ቁጥር 12/2004 አንቀፅ 13.1

04/09/2022

የውርስ ሀብት ሰ/መ/ቁ.210911
Abrham Yohannes

ሟች በህይወት እያለ ኑዛዜ ስጦታ ካደረገ በኋላ ይህንኑ ንብረት በተወካዩ አማካይነት በሽያጭ ውል ካስተላለፈው በፍ/ብ/ሕ/ቁ. 900(1) መሰረት የኑዛዜ ስጦታውን ፈራሽ የሚያደርገው በመሆኑ በሽያጭ የተላለፈው ንብረት በፍ/ብ/ሕ/ቁ.826 (1) መሰረት የውርስ ሀብት አይደለም።
ፍ/ብ/ሕ/ቁ.826 (1)፤ 900 (1)

04/09/2022

የስራ ውል ማስጠንቀቂያ እንዲታገድ የሚቀርብ አቤቱታ

በህጉ አግባብ የተሰጠ ማስጠንቀቂያ ለሠራተኛው የማንቂያ ደወል ነው። የጊዜ ጉዳይ እንጂ ውሉ መቋረጡ እንደማይቀርለት ስለሚያውቅ ራሱን ከወዲሁ ያዘጋጃል። አማራጭ ሥራ ፍለጋ ይጀምራል። አሠሪውን የመሞገት ሀሳብ ካለው ሀሳቡን የሚተገብርበት መላ አስቀድሞ ይዘይዳል። እንበልና ሙግትን እንደ አማራጭ ከወሰደ ሠራተኛው ያሉት መፍትሔዎች ምንድናቸው? የመጀመሪያውና ግልጽ የሆነው መፍትሔ የማስጠንቀቂያ ጊዜው እስኪያልቅ ጠብቆ የሥራ ውሉ ከህግ ውጭ መቋረጡን ገልጾ ክስ ማቅረብ ነው። ሁለተኛውና ከአዋጁ አንጻር አከራካሪ ሊሆን የሚችለው ደግሞ የማስጠንቀቂያ ጊዜው ሳያልቅ ማስጠንቀቂያው እንዲታገድለት አቤቱታ ማቅረብ ነው።

የሥራ ውል ለማቋረጥ የተሰጠ ማስጠንቀቂያ እንዲታገድ በመጠየቅ የሚቀርብ ክስ ከመነሻው የክስ ምክንያት አለው ለማለት ያስቸግራል። በዚህ ነጥብ ላይ በሰበር ችሎት በግልጽ የተሰጠ የህግ ትርጉም ባይኖርም ማስጠንቀቂያ እንዲታገድ ክስ ከቀረበ በኋላ በክርክር ሂደት የማስጠንቀቂያው ጊዜ አልቆ የሥራ ውሉ መቋረጥ እርግጥ ከሆነ የመቋረጡ ህጋዊነት በይግባኝ ደረጃም ቢሆን ሊታይ ይችላል። በአመልካች የኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተክርስቲያን እና ተጠሪ አቶ ተስፋዬ ፀጋዬ (ጥር 28 ቀን 2001 ዓ.ም. ሰ/መ/ቁ 37940 ያልታተመ) መካከል በነበረው ክርክር ተጠሪ የሥራ ውላቸው እንደሚቋረጥ ተገልጾ በአመልካች የተሰጣቸው ማስጠንቀቂያ እንዲታገድ ክስ አቅርበው ክሱ የቀረበለት ፍ/ቤትም ‘ክሱ የማስጠንቀቂያው ውጤት ከታየ በኋላ የሚቀርብ እንጂ ገና ለገና ‘ከስራ ትወጣለህ ተዘጋጅ’ ተብያለው ብሎ ክስ ሊቀርብበት እንደማይገባ” በመጠቆም ውድቅ አድርጎታል። በውሳኔው ላይ ይግባኝ የቀረበለት ፍ/ቤት ግን አመልካች ተጠሪን አለአግባብ ስላሰናበተ ወደ ሥራ ይመልሳቸው በማለት ውሳኔ ሰጥቷል። ፍርድ ቤቱ በዚህ መልኩ ውሳኔ የሰጠው በይግባኝ ክርክር ወቅት የማስጠንቀቂያ ጊዜው አልቆ ስለነበር ነው።

ውሳኔው እንዲታረምለት አመልካች ባቀረበው የሰበር አቤቱታ መሰረታዊ የህግ ስህተት ተፈጽሟል በማለት ካቀረባቸው ክርክሮች መካከል አንዱ ከማስጠንቀቂያው እና ከተጠሪ የክስ ይዘት ጋር የተያያዘ ነበር። ምንም እንኳን አመልካች በዚህ ነጥብ ላይ ያቀረበው የክርክር ይዘት በችሎቱ ውሳኔ መግቢያ ላይ በግልጽ ባይዘገብም ተጠሪ መብት ሳይኖራት ባቀረበችው ክስ የይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት ውሳኔ መስጠቱ አግባብነት እንደሌለው ገልጾ እንደተከራከረ ከፍርዱ ሐተታ ለመገንዘብ ይቻላል። ይኼው የአመልካች ክርክር ተቀባይነት ያጣ ሲሆን ለዚህ የተሰጠው ምክንያት ክርክሩ በይግባኝ ደረጃ ሲካሄድ የማስጠንቀቂያ ጊዜው አብቅቶ ውሉ የሚቋረጥበት ደረጃ ደርሷል የሚል ነው።

ክሱ በቀረበበት የመ/ደ/ፍ/ቤት ላይ የሥራ ውሉ መቋረጥ ህጋዊነት በጭብጥነት ተይዞ በአመልካችና በተጠሪ ክርክር አልተካሄደበትም። ውሳኔም አላረፈበትም። በክሱ የተጠየቀው ዳኝነት የማስጠንቀቂያ መታገድ እንጂ የሥራ ውል መቋረጥ አይደለም። ጉዳዩ በይግባኝ እየታየ እያለ ውሉ የሚቋረጥበት ጊዜ ቢደርስም ፍርድ ቤቱ የሥራ ውሉ ከህግ ውጭ እንደተቋረጠ ውሳኔ የሰጠው እንደ መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት እንጂ እንደ ይግባኝ ሰሚ አይደለም። ምክንያቱም የሥራ ውሉ መቋረጥ ህጋዊነት ላይ በስር ፍ/ቤት የተሰጠ ውሳኔ የለም። ይህ የስነ-ስርዓት መፋለስ ግልጽ ሆኖ እየታየ ከምንም በላይ ደግሞ አመልካች የመሰማት መብቱ እንደተጣሰና እንደተጣበበ አከራካሪ ባልሆነበት ሁኔታ ችሎቱ የይግባኝ ሰሚውን ፍ/ቤት ውሳኔ ያለትችት አጽንቶታል።

03/09/2022

በፍ/ቤት ጸድቆ የነበረ የውርስ አጣሪ ሪፖርት ይሰረዝልን የሚል አቤቱታ በዛው ሪፖርቱ በጸደቀበት መዝገብ ላይ ሊቀርብ የሚገባው እንጂ ሪፖርቱ ከጸደቀበት መዝገብ ውጪ በሌላ የክስ መዝገብ ይስተናገድ የሚባልበት የህግ መሰረት የለም፡፡
ሰ.መ.ቁ 216299 ያልታተመ

የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በሰ.መ.ቁ 45905(ቅጽ 11) በፍ/ቤቱ የጸደቀ የውርስ አጣሪ ሪፖርት በማስረጃነት የሚያገለግል ሆኖ ይህን የውርስ አጣሪ ሪፖርቱን በማስረጃነት ተጠቅሞ የድርሻ ክፍፍል ዳኘነት ለመጠየቅ የሚያገለግል እንጂ በቀጥታ ውሳኔው ለአፈጻጸም ችሎት የሚቀርብ ባለመሆኑ በፍ/ብ/ስ/ስ/ህ/ቁ 358 መሰረት ተቃውሞ የሚቀርብበት አይደለም ሲል አስገዳጅ ትርጉም ሰጠቶበት ነበር፡፡

በዚህ መዝገብ በፌ/መ/ደ/ፍ/ቤት የጸደቀ የውርስ አጣሪ ሪፖርትን መሰረት በማድረግ በፌ/ከ/ፍ/ቤት የውርስ ሀብት ክፍፍል አቤቱታ ቀርቦ ፍርድ ቤቱ በሰጠው የክፍፍል ውሳኔን በመቃወም ለፌ/ከ/ፍ/ቤት በፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 358 መሰረት መቃወሚያ ቀርቦ የነበረ ሲሆን ፍርድ ቤቱ መቃወሚያው መቅረብ ያለበት የውርስ አጣሪ ሪፖርትን ላጸደቀው ፍርድ ቤት እንደሆነ የሰጠው ውሳኔ በሰበር ተሸሮ ለፌ/ከ/ፍ/ቤት ሊቀርብ ይገባል የሚል ትርጉም ተሰጥቶበታል፡፡
ችሎቱም በሰ.መ.ቁ 216299 እና በሰ.መ.ቁ 45905(ቅጽ 11) መካከል የተነሳው የህግ ጭብጥ በተመለከተ ልዩነት ሲያስቀምጥ እንዳለው

“በሰ.መ.ቁ 216299 አመልካቾች ያቀረቡት የክስ አቤቱታ በፍ/ቤቱ የጸደቀ የውርስ አጣሪ ሪፖርት እንዲሰረዝልን የሚል ሲሆን ይህ አቤቱታ በሰ.መ.ቁ 45905(ቅጽ 11) በፌ/ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የታየውን ከውርስ አጣሪ ሪፖርት መጽደቅ እና ይህንኑ ሪፖርት መሰረት አድርጎ የውርስ ሀብት ድርሻ ክፍፍል ክስ መቅረብ እና በዚሁ ላይም የውርስ ሀብት ድርሻ ክፍፍል ውሳኔን ሂደት ያለፈ ሳይሆን በፍ/ቤት ጸድቆ የነበረ የውርስ አጣሪ ሪፖርት ይሰረዝልን የሚል ይዘት ብቻ ያለው በመሆኑ በፌ/ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በሰ.መ.ቁ 45905 የተሰጠው ውሳኔ ለተያዘው ጉዳይ ተፈጻሚነት የለውም፡፡”

https://chilot.me/2022/07/23/c-f-no-216299-objection-liquidators-report/amp/

02/09/2022

FDRE Ministry of Justice/ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ፍትሕ ሚኒስቴር
የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች በኢትዮጵያ የንግድ ህግ

መግቢያ

በሀገራችን የንግድ እንቅስቃሴ ውስጥ ንግድን ከማፋጠን እና የፋይናንስ ግብይትን ከማሳለጥ አንጻር የገንዘብነት ዋጋ ያላቻው የሚተላለፉ ሰነዶች የሚጫወቱት ሚና እጅግ ከፍተኛ እንደሆነ ይታመናል፡፡ በዚህ አጭር ጽሁፍ እነዚህኑ የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች ምንነት እና የሀገራችን የሚተዳደሩበትን የህግ ማእቀፍ በአጭሩ እናያለን፡፡

የህግ ማእቀፍ

እስከቅርብ ጊዜ በስራ ላይ የነበረው የ1952ቱ የንግድ ህግ ስድስት መጽሐፍት የነበሩት ሲሆን የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶችና የባንክ ስራዎች በተመለከተ የደነገገው የህጉ ክፍል በመጽሀፍ አራት ስር የተደራጁ ናቸው፡፡ አዲሱ የንግድ ህግ አዋጅ ቁጥር 1243/2013 በይዘቱ በሶስት መጽሐፍት የተከፋፈለ ሲሆን የበፊቱ ንግድ ህግ መጽሐፍት 3 እና 4 የአዲሱ የንግድ ሕግ አካል ሳይሆኑ ራሳቸዉን ችለዉ የፋይናንስ አገልግሎት መድብል ወይም ኮድ ሆነው እንዲወጡ በመተው መጽሐፍ አንድ፣ሁለት እና አምስት የንግድ ሕግ ተብሎ እንዲሻሻል ተደርጎ በአዲሱ የንግድ ሕግ ተካተው ወጥተዋል፡፡ በዚህም አዲሱ የፋይናንስ አገልግሎት ህግ እስኪወጣ ድረስ የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች ወይም የንግድ ወረቀቶች በነባሩ የንግድ ህግ ምእራፍ አራት ድንጋጌዎች መሰረት የሚታዩ መሆናቸው ይቀጥላል፡፡

የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች ምንነት

በ1952ቱ የንግድ ህግ አንቀፅ 715 /1/ መሰረት የሚተላለፍ የገንዘብ ሰነድ ማለት መብቱ ከሰነዱ ተለይቶ ሊሰራበት ወይም ሊተላለፍ የማይችል የአገልግሎት መብት ያለበት ሰነድ ሁሉ ነው በማለት ይደነግጋል፡፡ ይህ ትርጉም የሚተላለፉ ሰነዶች የመብትና የግዴታ ማረጋገጫ ሰነዶች ናቸው ከማለት በተጨማሪ በሰነዶቹ ውስጥ የተመለከቱት መብቶች ከሰነዶች ተለይተው ሊተላለፉ /ሊሰራባቸው/ እንደማይችሉ የሚያመለክት ነው፡፡ ይህም አባባል ጠቅለል ባለ መልኩ ሲገለፅ የሚተላለፍ ሰነድ ማለት በሠነድ ላይ የተመለከተው መብት ከሰነድ ላይ ለይቶ ሊሰራበት እና ሊተላለፍ የማይችል የመብትና የዕዳ ማረጋገጫ ሰነድ መሆኑን የሚያስረዳ ነው፡፡

የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነድ አይነቶች

በ1952ቱ የንግድ ህግ አንቀፅ 732 መሰረት የንግድ ወረቀቶች ማለት በገንዘብ መክፈል የሚሆነውን ግዴታ የሚናገሩ የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች ናቸው፡፡ እነዚህ ሰነዶችም፡-
 የሀዋላ ወረቀት /Bill of Exchange/
 ለመክፈል ተስፋ ሰነድ /Promisory Note/፣
 ቼክ /Cheques/፣
 የመንገድ ቼክ/Travellers Cheques/፣
 የእቃ መጋዘን ለተቀመጡ እቃዎች ምስክር ወረቀቶች/ደረሰኞች /warehouse goods deposit certificates/ ናቸው፡፡

የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች ሊያሟሏቸው ስለሚገቡ መስፈርቶች እና የሚያስከትሉት ህጋዊ ውጤት

የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች የሚወጡት በህግ ችሎታ ባላቸው ሰዎች ብቻ ነው፡፡ በ1952 የንግድ ህግ አንቀጽ 733 መሰረት ማናቸውም በውል ለመገደድ ችሎታ ያለው ሰው በንግድ ወረቀትም መገደድ እንደሚችል ደንግጓል፡፡ ማንኛውም ሰው በውል የሚገደደው በህግ ችሎታውን ያላጣ ከሆነ ብቻ ነው፡፡ ህጋዊ ችሎታ የሌላቸው ሰዎች ማለት በፍትሐብሔር ህጉ መሰረት የጸና ህጋዊ ውጤት የሚያስከትሉ ክንውኖችን ለማካሄድ አቅም የሌላቸው ሰዎች ሲሆኑ እነሱም ለአቅመ አዳም ያልደረሱ ህጻናት፣ በህግ ወይም በፍርድ ቤት ውሳኔ ከህጋዊ ውጤት ካላቸው ድርጊቶች ውስጥ ከመሳተፍ የተከለከሉ ሰዎች (ለምሳሌ የአእምሮ ህመምተኛ፣ በእርጅና ምክንያት የሚያደርጉትን ድርጊት ህጋዊ ውጤት የማያውቁ ሰዎች እና በወንጀል ቅጣት ከመብት በመሻር ውሳኔ በወንጀል ህጉ አንቀጽ 123 መሰረት የተወሰነባቸው ሰዎች) ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶችን ወይም የንግድ ወረቀቶች ማውጣት አይችሉም፡፡ ካወጡም አይገደዱባቸውም ማለት ነው፡፡

ሌላኛው መስፈርት ፊርማ ነው፡፡ የሚተላለፉ ሰነዶች ሲወጡ የግድ በአውጪው መፈረም አለባቸው፡፡ ይኸውም በሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች ባወጧቸው ሰዎች ወይም መግለጫውን በሰጡ ሰዎች የእጅ ፣ጽሁፍ ፊርማ ሊፈረሙ ይገባል፡፡ መፈረም ለማይችሉ ሰዎች በእጅ ምልክት ወይም ማህተም ማድረግ አለባቸው፡፡ በሁሉም ሁኔታ በንግድ ወረቀቶች ላይ መፈረም የማይሉ ሰዎች ሰነዱን ስለማውጣታቸው እና ይዘቱ በባለስልጣን ፊት ቀርቦ መረጋገጠ አለበት፡፡

በንግድ ህጉ አንቀጽ 719 መሰረት የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች በሁለት መደቦች ሊወጡ የሚችሉ ሲሆን እነሱም ለአምጪው ወይም ስሙ ለተጠቀሰው ወይም ለታዘዘለት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ይህ ማለትም ላምጪው ተብለው የወጡ የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች ሰነዶቹን ለባለ ግዴታው ያቀረበ ማንም ሰው በሰነዶቹ የተገለጸው ገንዘብ ተከፋይ ባለመብት ይሆናል ማለት ነው፡፡ ባለእዳው የአምጪውን ማንነት ግምት ውስጥ ሳያስገባ ሰነዱን ያቀረበው ሰው በቀጥታ ባለመብት መሆኑን በመገንዘብ በሰነዱ ላይ የተጠቀሰውን ክፍያ መፈጸም ይኖርበታል ማለት ነው፡፡ እዚህ ላይ በህጉ አንቀጽ 721 እንደተገለጸው ሰነዱን ያቀረበው ሰው በሰነዱ የተገለጸው ግዴታ ባለመብት ለመሆኑ በቂ ማረጋገጫ ነው፡፡

ሁለተኛው የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች የሚወጣበት ፎርም ስሙ ለተጠቀሰው ወይም ለታዘዘለት ሰው ተብለው ሊወጣ ይችላሉ፡፡ ይህ ማለት የተከፋይነት ወይም የአገልግሎት ተጠቃሚነት ባለመብትን የመብቱን ተጠቀሚ ማንነት ቀድሞ በመለየት ይሄንኑም በተላላፊ የገንዘብ ሰነዶቹ ላይ በመግለጽ የወጡ ሰነዶች ናቸው፡፡ በሰነዱ የተገለጹ ገንዘብ ወይም ግደታዎች ባለ እዳ የሆነው ሰው ወይም ድርጅት አገልግሎቱን ወይም ክፍያውን ሰነዱን ላቀረበለት ሰው ሁሉ ቀጥታ የሚፈጽመው ሳይሆን በሰነዱ ስሙ ወይም ማንነቱ ለተገለጸው ሰው ብቻ መፈጸም አለባት፡፡ ስሙ የተገለጸው ሰው እና ሰነዱን ያቀረበው ሰው አንድ መሆናቸውን በመታወቂያና መሰል ሰነድ ማረጋገጫ መንገዶች አጣርቶ መክፈል አለበት፡፡

የአክስዮን ማህበር አክስዮንን በተመለከተ የቀድሞው የንግድ ህግ አክስዮኖች በሁለቱም መንገዶች ማለትም ለአምጪ ወይም ስሙ በአክስዮኑ ለተመዘገበው ሰው በማለት የሚወጡ እና የሚተላለፉ ሲሆን በአዲሱ የንግድ ህግ አዋጅ 1243/2013 አንቀጽ 267 መሰረት ግን አክስዮኖች በባለአክስዮኖች ስም በመመዝገብ መውጣት እንዳለባቸው ህጉ ደንግጓል፡፡ ቀደም ሲልም ለአምጪው ተብለው የወጡ አክስዮኖች በሶስት አመት ጊዜ ውስጥ ወደ ተመዝጋቢ ባለአክስዮንነት እንዲቀየሩ ተደንግጓል፡፡ ስለዚህ ለአምጪው ተብሎ የሚጠቀስ እና የሚወጣ አክስዮን በአዲሱ ንግድ ህግ መሰረት አዲሱ የንግድ ህግ ከወጣበት ቀን አንስቶ ከሶስት ዓመት በኋላ ህጋዊ ተቀባይነት የለውም ማለት ነው፡፡

በሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች ውስጥ የተገለጸ እዳ ባለእዳ የሆነ ሰው እዳውን መክፈል ያለበት ሰነዱን ከቀረበለት ብቻ ሲሆን ይህ ባለእዳ ክፍያውን ሲፈጽም ከባድ አታላይነት ወይም ቸልተኝነት ካልፈጸመ በስተቀር የገንዘብ ተከፋይ ትክክለኛው ሰው ባይሆን እንኳን ሰነዱ ባለገንዘብነት መብት ለሰጠው ሰው የክፍያ ጊዜው ሲደርስ ከከፈለ ከእዳው ነጻ መሆኑን ህጉ በአንቀጽ 716 ንኡስ አንቀጽ 3 ላይ ደንግጎ ይገኛል፡፡ ከዚህም የምንረዳው ይህ በሰነዶች የሚደረግ የገንዘብ ልውውጥ የፋየናንስ ግብይቱን እና አጠቃላይ የኢኮኖሚውን ፈጣን ግብይት ለማረጋገጥ ታስቦ የተቀረጸ ለግብይቱ የተደረገ የህግ ጥበቃ እና ዋስትና መሆኑን ነው፡፡

ነገር ግን እዳ ከፋዩ ሰነዱን ከያዘው ሰው ጋር ባሉ የግል ግንኙነቶች በመመስረት በሰነዱ አጻጻፍ፣ ፎርም፣ ቃላት፣ የማስመሰል ፊርማ፣ ሰነዱን የማውጣት ችሎታ ወይም የውክልና ስልጣን አለመኖር እና ሌሎች ክስ ለማቅረብ አስፈላጊ የሆኑ ቅድመ ሁኔታዎች አለመሟላታቸውን በማንሳት እዳ ከፋዩ ሰነዱን የያዘውን ሰው እዳውን ላለመክፈል ሊቃወም ይችላል፡፡ ሆኖም አንድ በቅን ልቦና የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶችን የያዘ ሰው መልስ ተብሎ ሊከሰስ አይችልም፡፡ በሌላ በኩል የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶችን የያዘ ሰው የሰነዶቹን ለአምጪው ከሚለው ወደ ስም የተጻፈበት ሰው እንዲቀይርለት ሰነዶቹን ላወጣው ሰው በራሱ ኪሳራ ሊጠይቅ እንደሚችል ህጉ ይፈቅዳል፡፡

ሌላው የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነድ በትእዛዝ በሚል የሚተላለፍ ሲሆን ይህም የሚፈጸመው በህጉ አንቀጽ 724 እና ቀጥሎ ባሉ ድንጋጌዎች መሰረት በሰነዱ ጀርባ በመፈረም እና ባለመብት ለሆነው ሰው በመስጠት ነው፡፡ በዚሁ ህግ መሰረት በሰነዱ ጀርባ ላይ በመፈረም በትእዛዝ በሚል የሚተላለፉ ሰነዶች በጀርባው መፈረሙ በሰነዱ ላይ መገለጽ ያለበት ሲሆን በጀርባውም በጻፈው ሰው በራሱ መፈረም አለበት፡፡ እዚህ ላይ በጀርባው የተፈረመ ሰነድ የተፈረመለት ሰው ስም ባይገለጽም ህጋዊ ዋጋ አለው፡፡ ለዚህ አላማ ሲባል ለአምጪው ተብሎ በጀርባ የተፈረመበት ገንዘብ አስተላላፊ ሰነድ ልክ ስም እንዳልተገለጸበት ይቆጠራል፡፡ በዚህም ሰነዱን ያቀረበው ሰው በሰነዱ የተገለጹ ግዴታዎች ባለመብት ይሆናል ማለት ነው፡፡ በተጨማሪም በሰነዱ ጀርባ ሀተታ ማስገባትን ህጉ አይፈቅድም መፈረሙ ብቻ በቂ ነው፡፡ የገቡ ሀተታዎች ካሉም እንዳልገቡ ይቆጠራሉ፡፡

ከህጋዊ ውጤት አኳያ በጀርባው የተፈረመ ገንዘብ ማስተላለፊያ ሰነድ በሰነዱ ውስጥ የተገለጹትን መብቶች ሁሉ ያስተላልፋል፡፡ በዚህ መልክ የሚወጣ የገንዘብ ማስተላለፊያ ሰነድ በጀርባው ጽሁፍ ወይም ስም ያልተሞላበት ከሆነ አምጪው ባዶውን ቦታ በራሱ ወይም በሌላ ሰው ስም መሙላት፣ ሰነዱን እንደገና ስም ሳይጽፍ ወይም የሌላ ሰው ስም በማስገባት ማስተላለፍ የችላል፡፡ በተጨማሪም ይህ ሰነዱን የያዘው ሰው የሰነዱን ባዶ ቦታ ሳይሞላ በጀርባውም ሳይፈርም ለሶስተኛ ወገን ሰነዱን ማስተላለፍ ይችላል፡፡ በዚህ ሁኔታ በሰነዱ ጀርባ የሚፈርም ሰው ሰነዱን ያወጣው ሰው ስላልፈጸመው ግዴታ ተጠያቂነት የለበትም፡፡ ይህ ማለት በሰነዱ ጀርባ የሚፈርም ሰው ሰነዱን ያወጣው ሰው በሰነዱ ይዘት ውስጥ የገባው ግዴታ ሀላፊነት አለበት ማለት ነው፡፡ በሰነዱ በተገለጸው ልክ ሰነዱ የሚያስከትለውን ግዴታ በሰነዱ ጀርባ የፈርመው ሰው ልክ እንደ ሰነዱ አውጪ በመሆን በተገለጸው ግዴታ ሀላፊነት አለበት ማለት ነው፡፡ ሰነድ የተላለፈለት ሰው ሰነዱን ሲቀበል እዳ ከፋዩን ለመጉዳት እያወቀ ካላደረገው በስተቀር ሰነድ አውጪ ከሰነድ ፈራሚው ጋር ባለው የግል ግንኘነት ላይ ከተመሰረቱት መከራከሪያዎች በቀር በዋስትና ስም ሰነዱ የተላለፈለትን ሰው ሊቃወምባቸው አይችልም፡፡

ማጠቃለያ
ገንዘብ ማስተላለፊያ ሰነዶች ወይም የንግድ ወረቀቶች አገራዊ ኢኮኖሚውን በተፋጠነ የግብይት ስርአት እንዲመራ ማድረግ ወስጥ ከፍተኛ ሚና ያላቸው ሲሆን የፋይናንስ ተቋማት የገንዘብ ፍሰት ፖሊሲንም ከማሳለጥ እና ለኢንቨስትመንት በብድር የሚሰጥ ወይም ለገንዘብ ጠያቂ ደንበኞቻቸው የሚከፈል የተከፋይ ገንዘብ እጥረት (liquidity problem) እንዳይገጠማቸው ያደርጋሉ፡፡ በዚህም አገራዊ እና ተቋማዊ እድገትን በከፍተኛ ሁኔታ ያግዛሉ፡፡ ከዚህ ባለፈ ያልተመዘገበ (የካሽ) የግብይት ስርአት እንደ አገር ከፋይናንስ ስርአቱ ውስጥ እንዲቀንስ ማድረግ ላይ ጉልህ ሚና አላቸው፡፡

02/09/2022

በሰበር ችሎት ክፍል አንድ
ቅን ልቦና ከውክልና እና አላግባብ መበልጸግ ጋር በተያያዘ በሰበር ችሎት የተሰጡ ትርጉሞች
አብርሃም ዮሐንስ
ውክልና
ሰ_መ_ቁ. 14974 ቅጽ 1

ተወካዩ የራሱን ጥቅም የሚመለከት ጉዳይ ሲያጋጥመው ሁኔታውን ለወካዩ ሳያሳውቅና ወካዩ ሳይስማማ ስራውን እንዳይፈጽም ይከላከላል፡፡ ስለወኪልነት የተደነገጉትን የፍ/ብሔር ድንጋጌዎች ስንመለከትም ተወካዩ ከወካዩ ጋር በሚኖረው ግንኙነት ጥብቅ የሆነ ቅን ልቦና ሊኖረው እንደሚገባ እና የውክልና ስልጣኑን የሚያስቀሩ ምክንያቶች እንዳለበት (የፍ/ብ/ህ/ቁ 2208)፣ ተወካዩ ስራውን የሚፈጽመው በተለይ ለወካዩ ጥቅም ሊሰጥ የሚችል መንገድ ብቻ መሆን እንዳለበት (ፍ/ብ/ህ/ቁ 2209(1))፣ እንዲሁም ተወካዩ በራሱ ስም ከወካዩ ጋር የሚያደርገው ውል ወካዩ ካላጸደቀው በቀር ሊፈርስ እንደሚችል (የፍ/ህ/ቁ 2188) መደንገጋቸው ተወካዩ ለወካዩ ፍጹም ታማኝ መሆን እንዳለበት እና ለወካዩ ጥቅም ብቻ መስራት እንዳለበት፣ የጥቅም ግጭት ባለበት ጊዜ ሁሉ ሁኔታውን ለወካዩ የማሳወቅ ግዴታ እንዳለበት የሚያስገነዝቡ ናቸው፡፡ በመሆኑም Aንድ ተወካይ የጥቅም ግጭት ባለበት ጊዜ ለወካዩ ሳያሳውቅ የሚየከናውነውን ስራ ወካዩ ሊቃወመው የሚችል መሆኑን እና በዚህ ሁኔታ የተከናወነው ስራም ወካዩ ካላፀደቀው በቀር ወካዩ ራሱ እንደፈጸመው ሊቆጠር እንደማይገባ ከውክልና ግንኙነት አጠቃላይ ዓላማ እና ከፍ/ብ/ህጉ ድንጋጌዎች መገንዘብ ይቻላል፡፡

ሰ_መ_ቁ. 26399 ቅጽ 5

ሿሚው በግልጽም ይሁን በዝምታ እንደራሴው ሥልጣኑ ቀሪ ከሆነ በኋላ የሠራውን ሥራ ያልተቀበለው መሆኑ ከተረጋገጠ የዚሁ ያለመቀበል ውጤት በቁጥር 2193 ተደንግጓል፡፡ የዚህን ድንጋጌ ይዘት ስንመለከት ሿሚው ይህንኑ የእንደራሴውን ሥራ ካልተቀበለው ምን ጊዜም ይኸው ውል ፈራሽ ነው የሚል አይደለም፡፡
ይልቁንም ከፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1808 እስከ 1818 ድረስ የተመለከቱትን ድንጋጌዎች ተከትሎ የውሉ መፍረስ ወይም መሰረዝ ሊወሰን የሚችል መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ይህም እነዚህኑ አግባብነት ያላቸውን ድንጋጌዎች በመከተል ውሉ ሊፈርስ የማይችልበት አጋጣሚ ያለ መሆኑን የሚያሳይና ነገር ግን ውሉ የሚፈርስ ሆኖ በተገኘ ጊዜ ውሉ በመፍረሱ ምክንያት በቅን ልቦና ከእንደራሴው ጋር በተዋዋሉት 3ኛ ወገኖች ላይ ለሚደርሰው ጉዳት ካሣ የሚጠየቅበት መንገድ የሚያመቻች ድንጋጌ ነው፡፡

ሰ_መ_ቁ. 77983 ቅጽ 15

ተወካዩ ከወካዩ ጋር የሚያሰተሳስረው ግንኙነት ውስጥ ጥብቅ የሆነ ቅን ልቦና ሊኖረው እንደሚገባ በፍትሐብሄር ሕግ ቁጥር 2208(1) ስር ተደንግጓል ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ተወካዩ የተወካይነት ሥራውን የሚፈጽመው በተለይ የወካዩን ጥቅም ሊሰጥ በሚችልበት መንገድ ብቻ መሆን እንዳለበት በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2209 (1) ድንጋጌ ያሳያል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ተወካዩ በውክልና ሥራው ላይ በሚገኝባቸው ጊዜዎች ሁሉ በውክልና በተሰጠው አደራ አንድ መልካም የቤተሰብ አባት ቤተሰቡን ለመጠበቅ እንደሚያደርገው ሁሉ በትጋትና በጥንቃቄ መጠበቅ ያለበት መሆኑን በፍትሐብሄር ሕግ ቁጥር 2211(1) ስር በግልጽ ተደንግጓል፡፡

አላግባብ መበልጸግ

ሰ_መ_ቁ. 81081 ቅጽ 14

የፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 2168 ድንጋጌ ይዘት ሲታይም አንድ ሰው ለተወሰነ ጊዜ በእጁ ያቆየውን እቃ እንዲመለስ የተገደደ እንደሆነ ለሕግ ወይም ለውል ተቃራኒ የሚሆን ድንጋጌ ከሌለ በቀር የተባለውን እቃ ከመለዋወጥ የተነሳ ያሉት መብቶችና ግዴታዎች ከድንጋጌው ቀጥለው ባሉት ደንቦች መሰረት የሚወሰን መሆኑን የሚያስገነዝብ ሲሆን በዚሁ ድንጋጌ ስር ከሰፈሩት ደንቦች መካከል አንዱ የሆነው በፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 2169 ስር የተቀመጠው ደግሞ የያዘውን እቃ እንዲመልስ የተገደደ ሰው በእቃው ላይ ያደረገው ወጪ ሊመለስለት የሚገባው ወጪው የግድ አስፈላጊ ሁኖ ሲገኝ ስለመሆኑና ወጪው አስፈላጊ ሳይሆን ከቀረ ወይም ወጪው እቃውን እንዲመለስ በተገደደው ሰው ወይም ተገዳጁ ኃላፊ በሚሆንበት ሰው ጥፋት ምክንያት ከሆነ ወጪው ሊመለስ የማይችል መሆኑን ያሳያል፡፡
ሕጉ በአንቀጽ 2171(1) ስርም ለእቃው የተደረገው ወጪ የእቃውን ዋጋ ግምት ከፍ አድርጎት እንደሆነም እቃውን ለመመለስ የተገደደው ሰው ስለዚሁ ጉዳይ ያወጣው ገንዘብ ሊመልስለት እንደሚገባ የደነገገ ሲሆን ይህ ወጪ በክፉ ልቦና ስለመደረጉ የተረጋገጠ ወይም ርትዕም የሚያስገድድ ከሆነ ደግሞ ዳኞች ወጪውን ለመቀነስ ወይም ጭራሹን ለማስቀረት የሚችሉበት አግባብ መኖሩንን የተጠቃሹ ድንጋጌ ቀጣይ የሆነው የፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 2172((1) ይዘት ያሳያል፡፡
ይህ ድንጋጌ አንድን ወጪ በክፉ ልቦና የተደረገ ነው ለማለት የሚቻልበት አግባብም ወጪው በተደረገበት ጊዜ ወጪውን የሚጠይቅ ሰው እቃውን ለመመለስ ግዴታ ያለበት መሆኑን ያውቅ እንደነበረ ወይም ማወቅ ይገባው የነበረና ርትዕም ሲያስገድድ መሆኑን በመለኪያነት አስቀምጧል፡፡
ስለሆነም እነዚህ ድንጋጌዎች ሲታዩ አንድ ሰው የሌላ ሰው ንብረት ይዞ ሲጠቀም ከቆየና ንብረቱን በሚጠቀምበት ጊዜ ንብረቱን ከጥፋት ወይም ከብልሽት ለማዳን ሲል ተገቢውን ወጪ ቢያወጣ ይኼው ወጪ በሕጋዊ ባለሃብቱ እንዲተካለት መጠየቅ የሚችልበት አግባብ የሚኖረው ወጪው የግድ አስፈላጊ ከሆነና በቅን ልቦና የተደረገ መሆኑ ሲረጋገጥ ስለመሆኑ የሚያስገነዝቡ ሲሆን በክፉ ልቦና የተደረገ ስለመሆኑ የተረጋገጠውን ወጪ ግን እቃውን እንዲመለስ የተደረገ ሰው ሊቀነስበት ወይም ጭራሹንም ዳኞች ሊያስቀሩት የሚችሉ ስለመሆኑ ሕግ ስልጣን የሰጣቸው መሆኑን ድንጋጌዎች ያስረዳሉ፡፡

ሰ/መ/ቁ. 181649በጋራ ንብረት ክፍፍል ወቅት አንደኛው ተጋቢ የሶስተኛ ወገኖች የጋራ ዕዳ አለብን ብሎ ለመጠየቅ /የተከሳሽ ከሳሽነት ክስ ለማቅረብ/ መብትና ጥቅም የለውም፡፡4 ለ 1 በሆነ...
25/07/2022

ሰ/መ/ቁ. 181649
በጋራ ንብረት ክፍፍል ወቅት አንደኛው ተጋቢ የሶስተኛ ወገኖች የጋራ ዕዳ አለብን ብሎ ለመጠየቅ /የተከሳሽ ከሳሽነት ክስ ለማቅረብ/ መብትና ጥቅም የለውም፡፡
4 ለ 1 በሆነ አብላጫ ድምጽ የተሰጠ

C-F-No. 181649 Debt of sposes – standing Ruling One of the spouses lacks standing to claim payment of common debt of spouses before partition of common property. The cassation bench stated de…

10/06/2022

PROCLAMATION No. —–/2022 A PROCLAMATION TO PROVIDE FOR THE AMENDMENT OF THE NATIONAL INTELLIGENCE AND SECURITY SERVICE RE-ESTABLISHMENT PROCLAMATION WHEREAS, it has become necessary to …

15/04/2022

PROCLAMATION No. 1267/2022 A PROCLAMATION TO PROVIDE FOR PUBLIC SERVANTS’ PENSION WHEREAS, it is part of the country’s social protection policy to expand social insurance system and reach citizens …

The first Law Firm License in Ethiopia issued to Habesha Legal Advocates LP
07/04/2022

The first Law Firm License in Ethiopia issued to Habesha Legal Advocates LP

The Ministry of Justice has issued the first license of the Ethiopian Bar Association to Habesha Legal Advocates LP. He gave. It is also noted that the license was issued in accordance with the Fed…

Address

Addis Ababa

Opening Hours

Monday 09:00 - 17:00
Tuesday 09:00 - 17:00
Wednesday 09:00 - 17:00
Thursday 09:00 - 17:00
Friday 09:00 - 17:00

Telephone

+251915735560

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Abrham Yohannes Law Corner posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to Abrham Yohannes Law Corner:

Share