19/12/2025
የዳኞች ደሞዝ (የሕግ ጉዳይ)
ሰሞኑን ዳኞች ከፌደራል ፍርድ ቤቶች በብዛት ሥራ ሲለቁ ይስተዋላል፡፡ ሌላው ቀርቶ ከመጨረሻው የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤትም ከአንድ ዓመት ወዲህ የተለያዩ ዳኞች ሥራ ለቀዋል። ከሥራ የሚልቁበት አንዱና ዋናው ምክንያት የደሞዝ ማነስ ነው። በሌላው የአፍሪካ ሀገር ግን ዳኝነትን የሚያክል የተከበረ ሥራ ለቆ መውጣት ያልተለመደ ነው።
እስኪ የሀገራችንን እና የሌሎች አፍሪካ ሀገሮችን የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች ደሞዝ እናነጻጽር። የ6 አፍሪካ ሀገሮች (ኬንያ፣ ግብፅ፣ ሞዛምቢክ፣ ታንዛንያ፣ ደቡብ አፍሪካ እና ቻድ) የጠቅላይ ፍርድ ቤቶቻቸውን ደሞዝ እንመልከት።
1. ኬንያ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ በዶላር $ 2,170 ነው። የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞቿ አማካይ ደሞዝ በዶላር ሲመነዘር 65,000 – 80,000 ነው። ይህ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ 33 እጥፍ ነው።
2. ግብፅ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ በዶላር $ 4,320 ነው። የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞቿ አማካይ ደሞዝ በዶላር ሲመነዘር 16,000 – 22,000 ነው። ይህ የዳኞች ደሞዝ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ 4.5 እጥፍ ነው።
3. ሞዛምቢክ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ በዶላር $1,370 ነው። የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞቿ አማካይ ደሞዝ በዶላር ሲመነዘር 25,000 – 35,000 ነው። ይህ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ 21.9 እጥፍ ነው።
4. የታንዛኒያ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ በዶላር $ 1,320 ነው። የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞቿ አማካይ ደሞዝ በዶላር ሲመነዘር 45,000 – 60,000 ነው። ይህ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ 39.8 እጥፍ ነው።
5. ደቡብ አፍሪካ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ በዶላር $ 6,770 ነው። የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞቿ አማካይ ደሞዝ በዶላር ሲመነዘር 150,000 – 200,000 ነው። ይህ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ 25.9 እጥፍ ነው።
6. ቻድ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ በዶላር $ 690 ነው። የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞቿ አማካይ ደሞዝ በዶላር ሲመነዘር 15,000 – 20,000 ነው። ይህ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ 25.4 እጥፍ ነው።
ሰው እንደ ቤቱ እንጂ እንደ ጎረቤቱ አይኖርም እንዲሉ ከላይ የተጠቀሱት ሀገሮች የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች ዓመታዊ የደሞዝ ገቢ ይለያያል፡፡ ከፍተኛ ተከፋዮች የደቡብ አፍሪካ ዳኞች ሲሆኑ በዓመት ከ200 ሺህ እስከ 300 ሺህ ዶላር ጋር የሚመጣጠን ደሞዝ ይከፈላቸዋል፡፡ ከስድስቱ ሀገራት መካከል ዝቅተኛው ተከፋዮች የቻድ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች ሲሆኑ በአማካይ በዓመት ከ15,000 እከ 20,000 ዶላር የሚገመት መጠን ያለው ገንዘብ ይከፈላቸዋል፡፡ ሆኖም በአማካይ የነፍስ ወከፍ ገቢያቸውን 20 እና 25 እጥፍ የሚከፍሉ መሆኑ ሀገራቱን ያመሳስላቸዋል፡፡ ከሀገራቱ ውስጥ ታንዛንያ 39.8፣ ኬንያ ደግሞ 33 እጥፍ በመክፈል ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛሉ፡፡
የኢትዮጵያ ዓመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ 1,260 ዶላር ሲሆን ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞቿ እንደ ኬንያ 33 እጥፍ ቀርቶ 25 እጥፍ እንኳን ብትከፍል የአንድ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኛ ደሞዝ (25 X $1,260 = $31,500 ወይም አሁን ባለው ምንዛሪ በብር 31,500 X 170 = 5,355,000 (አምስት ሚሊዮን ሦስት መቶ ሃምሳ አምስት ሺህ) ይሆን ነበር፡፡ ጽድቁ ቀርቶብኝ በወጉ በኮነነኝ እንዲሉ የአንድ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኛ ዓመታዊ ገቢ 5 ሚሊዮን ቀርቶ 5 መቶ ሺህ እንኳን አይደርስም፡፡
ሀገርን ጥሩ ሀገር ከሚያሰኙት ዋና ዋና ነገሮች አንዱ የሕግ መከበርና የትክክለኛ ፍርድ መገኘት ነው፡፡ ትክክለኝ ፍርድ የሚኖረው ዕውቀቱና ልምዱ እንዲሁም ሥነ ምግባሩና ፍላጎቱ ያለው ዳኛ በቦታው ላይ ሲቀመጥ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ በሥራ ላይ ያሉትን ዳኞች ሥራቸውን ጥለው እንዳይወጡ ይዞ የሚያቆያቸው እንዲሁም ከውጪ ያሉትን ባለሞያዎች ስቦ የሚያመጣ ደሞዝ ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ዳኞች ግር ብለው እንዳይወጡ እና ፍርድ ቤቱም የሀገር አለኝታ የሆነ ተቋም እንዲሆን ከሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች ልምድ በመቅሰም እንደ እራሳችን ዐቅም ለዳኞች ደሞዝ ማሻሻል ይገባል፡፡
(ታምራት ኪዳነማርያም)