19/03/2023
በወንጀል ክርክር ፍርድ ቤት ቀርበው የእምነት ክሕደት ቃል ስለመስጠት /Plea of the accused)
========================
ክሱን እየሰማ ያለ ፍርድ ቤት ተከሳሹ የእምነት ክህደት ቃሉን እንዲሰጥ ማዘዝ የሚችለው የመጀመሪያ መቃወሚያ ያልቀረበ እንደሆነ ወይም መቃወሚያው ቀርቦ የሕግ መሰረት የለውም ተብሎ ውድቅ ከተደረገ ወይም ሕጉ በሚያዘው መሰረት መዝገቡ ለጊዜው ካልተዘጋ ብቻ ነው። የእምነት ክሕደት ቃል (plea) ስንል ተከሳሹ ጉዳዩን በያዘው (ክሱን እየሰማ ባለው) ፍርድ ቤት ፊት ቀርቦ ስለቀረበበት ክስ ፍሬ ነገር መፈፀሙን ኣለመፈፀሙን እና ጥፋተኛ መሆኑን ኣለመሆኑን ለመግለፅ የሚናገረው ቃል ማለት ነው።
#ስለ እምነት ቃል (Plea of guilty)
በአጠቃላይ ስለ እምነት ቃል ሲወሳ ሁለት ነገሮች ወደ ኣእምሮኣችን ይመጣሉ፡፡ እነሱም ዓ/ሕግ እና ተከሳሽ በሚያደርጉት ስምምነት (Plea bargaining) በተከሳሹ የሚሰጥ እምነት ቃል ኣንዱ ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ ተከሳሹ ጉዳዩን በያዘ አሟጓች /የስር/ ፍርድ ቤት ፊት ቀርቦ ክሱን ከተነበበለት በyላ የሚሰጠው የእምነት ቃል (Plea of guilty) ነው።
የእምነት ቃል ለመስጠት መስማማትን /plea bargaing/ በዋነኝነት በኮመን ሎው የሕግ ስርዓት ተከታይ ኣገሮች የሚታወቅ ሆኖ ሁለቱ ተከራካሪ ወገኖች (ዓ/ሕግና ተከሳሽ) የሚስማሙት፤ ተከሳሽ የእምነት ቃል እንዲሰጥና በአንፃሩ ደግሞ ዓቃቤ ሕግ በተከሳሹ ላይ የሚያቀርበው ክስ እንዲቀንስ ወይም ተመስርቶ የነበረ ክስ ቀንሶ እንዲያነሳ ወይም ቅጣት እንዲቀልለት ለፍርድ ቤት ሓሳብ ማቅረብ ነው (ኣንዳንዱ ጊዜ እስከ 30% ቅጣት ይቀነሳል)። በእነዚህ አገሮች አብዛኛዎቹ የወንጀል ጉዳዮች ውሳኔ የሚያገኙት በእምነት ቃል መሰረት ነው። ለዚህ ኣስራር መምጣት ምክንያት የሆኑት ደግሞ በየጊዜው እየጨመረ የመጣው የፍ/ቤት ጉዳዮች ለማቃለልና የክርክር ስርዓት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተወሳሰበ በመምጣቱ ነው ይባላል።
ክሱን ለሚሰማ ፍርድ ቤት የሚሰጥ የእምነት ቃል ተቀባይነት በሚመለከት የተለያዩ የሕግ ስርዓቶች የተለያየ ኣም ኣላቸው$ የኮመን ሎው የሕግ ስርዓት የሚከተሉ አገሮች ያየን እንደሆነ በተከሳሾች የሚሰጥ የእምነት ቃል በማንኛውም ሁኔታ ተቀባይነት ሊያገኝ ይገባል ይላሉ። ስለሆነም ኣብዛኛው የወንጀል ጉዳዮች ውሳኔ የሚያገኙት ተከሳሾች በሚሰጡት የእምነት ቃል ነው። የእምነት ቃል ተቀባይነት እንዲኖረው የሚያደርጉ ሁኔታዎች/ ምክንያቶች :: ለምሳሌ:- የአሜሪካን ኣገር ብንወስድ
ሀ) የእምነት ቃል ከመሰጠቱ በፊት የሕግ ኣማካሪ (ጠበቃ) እና ከጠበቃው ለመነጋገር የሚያስችል በቂ ጊዜ ሊያገኝ ይገባል።
ለ) ፍ/ቤቱ ሌላ ኣስፈላጊ ምክር መስጠት ኣለበት። ከሚሰጠው ምክር ኣነዳንዶቹ ለመጥቀስ ያህል የቀረበበት ክስ በሚገባ የተረዳው መሆኑን ማረጋገጥ፤ በጁሪ ኣልዳኝም የማለት መብት እንዳለው ሊወሰንበት የሚችል ኣነስተኛ እና ከፍተኛ ቅጣት ምን እንደሆነ እና ሌሎች ተጨማሪ ቅጣቶችም ሊወሰንበት እንደሚችል መንገር
ሐ) የሚሰጠው የእምነት ቃል በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ መሆኑን ማረጋገጥ አና
መ) ክሱ የፍሬ ነገር መሰረት ያለው መሆኑን ማረጋገጥ ናቸው።
የኮንቲኔንታል የሕግ ስርዓት የሚከተሉ ኣገሮች ግን ተከሳሹ በሰጠው እምነት ቃል መሰረት ብቻ እነዲፈረድበት ፍ/ቤቱን በአፅንኦት ያሳሰበ ካልሆነ በስተቀር ከጣልያን በስተቀር በሌሎች ኣገሮች ተቀባይነት የለውም። ስለዚህ ተከሳሽ የእምነት ቃል ቢሰጥም ማስረጃ የግድ መስማት ኣስፈላጊ ተደርጎ ይወሰዳል።
የአገራችን የሕግ ስርዓት ስንመለከት ደግሞ መጀመሪያ የተከሳሹ እምነት ክህደት ቃል ከመጠየቁ በፊት ተከሳሹ የቀረበበትን ክስ በሚገባ እንዲረዳው ፍ/ቤቱ የክሱን ዝርዝር ለተከሳሹ ማስረዳት አለበት (የወ/መ/ሕ/ስ/ስ/ቁ.132 (1) እና ሕገ መንግስት ዓንቀፅ 20 (2)። በመሆኑም ፍ/ቤቱ ለተከሳሹ መግለፅ ያለበት ነገር ፤ የወንጀሉ ዝርዝር ፣ የወንጀሉ ኣፈፃፀም የሚያቁሙ የሕግ ፣ የሞራል እና የግዙፍ ተግባር ጠባዮች ሁሉ (Legal, material and moral elements of the offence) (የወ/መ/ሕ/ስ/ስ/ቁ.111 (1) (ለ) እና የወ/ሕግ ዓነቀፅ 23 ፣ ተከሳሹ ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘ ሊወሰንበት የሚችለውን የቅጣት ዓይነትና የቅጣቱ መነሻና ጣሪያ ፣ የተከሳሹን ሕገ መንግስታዊ መብቶች ማለትም ፣ ያለመናገር መብቱን ፣ ክሱን ለማመን ወይም ለመካድ ሙሉ መብት እንዳለው እና ጥፋተኛነቱን ማረጋገጥ የዓ/ሕግ ግዴታ መሆኑንና ጥፋተኛነቱ በማስረጃ እስኪረጋገጥ ንፁህ ሆኖ የመገመት መብት ያለው መሆኑን ነው። ኣስፈላጊው ገለፃ ከተደረገለት በኋላ ተከሳሹ የቀረበለትን ክስ መፈፀሙንና ጥፋተኛ መሆኑን የሚያምን ወይም የሚክድ መሆኑን ፍ/ቤቱ ይጠይቃል።
ተከሳሹ በክሱ ማመልከቻ ላይ የተዘረዘረውን ወንጀል መፈፀሙን ያመነ እንደሆነ ፍ/ቤቱ የእምነት ቃሉን ወድያው መቀበል የለበትም። ቃሉን ከመቀበሉ በፊት ተከሳሹ ሙሉ በሙሉ ያመነ መሆኑን ማረጋገጥ አለበት። ኣንድ ተከሳሽ ለቀረበበት ክስ ሙሉ በሙሉ ኣምኗል የሚባለዉ መቼ ነው? የሚል ጥያቄ በዚህ አጋጣሚ ማንሳት ተገቢነት አለው። ተከሳሹ ወንጀሉን ፈፅሜኣሎህ ብሎ ማመኑ ብቻ ሙሉ በሙሉ ማመኑን ኣያረጋግጥም። ሙሉ በሙሉ ኣምኗል የሚባለው የእምነት ቃሉን የሰጠው በነፃ ፈቃዱ (voluntarily) መሆኑ ሲረጋገጥና ወንጀሉን ለመፈፀሙ የሚያመለክቱ መሰረታዊ እውነታዎች (Factual basis) መኖራቸው ሲረጋገጥ ነው።
ፍ/ቤቱ እነዚህን ሁኔታዎች ለማጣራት የሚከተሉትን ማጣሪያዎችና ገለፃዎች ማከናውን አለበት፣
ሀ) ተከሳሹ የወንጀሉን ዝርዝር በትክክል መረዳቱን ጠይቆ ማረጋገጥ ፣
ለ) የተከሳሹን የእምነት ቃል ፍ/ቤቱ ከተቀበለው ወድያው የጥፋተኛነት ውሳኔ እንደሚሰጥና ተከሳሹ የመከላከል መብት እንደማይኖረው ማስረዳት ፣
ሐ) ወንጀሉን መፈፀሙን እንዲያምን ተፅእኖ ወይም ማስፈራራት ደርሶበተ እንደሆነ ይህንኑ ከተከሳሹ ጠይቆ ማረጋገጥ ፣
መ) ተፅዕኖ ደርሶበት እንደሆነ ያለ ፈቃዱ እንዲያምን መገደድ እንደሌለበት ማስረዳት፣
ሠ) በክስ ማመልከቻው ላይ የተዘረዘረውን የወንጀሉን ኣፈፃፀም ዝርዝር ተከሳሹ ፈፀምኩ ከሚለው አገላለፅ (አነጋገር) ጋር በማስተያየት እንዲሁም ተከሳሹ ቢክድ ኖሮ ዓ/ሕግ ሊያቀርብ ያዘጋጀውን ማስረጃ በአጭሩ በመጠየቅ ተከሳሹ ወንጀሉን ለመፈፀሙ የሚያሳዩ መሰረታዊ እውነታዎች (Factual basis) መኖራቸውን ማረጋገጥ አለበት።
ይህን ሁሉ ማጣሪያ ካደረገ በyላ ፍ/ቤቱ ሁለት ኣማራጮች ይኖሩታል፡፡ ይኸውም በተከሳሹ እምነት ቃል ላይ ጥርጣሬ ካደረበት ዓ/ሕግ ማስረጃውን እንዲያሰማና ተከሳሹም የመከላከያ ማስረጃውን እንዲያቀርብ ለመፍቀድ ይችላል (ቁ.134 (2))። ባደረገው ማጣሪያ የተከሳሹን የእምነት ቃል ከተቀበለው ግን ተከሳሹ ጥፋተኛ ነኝ ብሏል በማለት ከመዘገበ በኃላ ከዚህ ጋር ተያይዞ ሲነሳ የሚገባው ነጥብ የስነ ስርዓት ሕጉ በተከሳሹ እምነት ቃል ብቻ ውሳኔ ሊሰጥባቸው የሚችሉና የወንጀል ክሶች ቢኖሩም ከወንጀሉ ከባድነት ኣንፃር ታይቶ ማስረጃ ሲሰማባቸው የሚገባ የወንጀል ዓይነቶች ለይቶ ኣለማስቀመጡ ነው። በልምድ እንደሚሰራበት ግን በዕድሜ ልክ ወይም በሞት ሊያስቀጣ በሚችል ወንጀል የተከሰሰ ሰው ወንጀሉን ስለመፈፀሙ ቢያምንም ፍ/ቤቱ ማስረጃ እንዲቀርብ የሚያዝበት ሁኔታ ነው ያለው።
የፍትሕና ሕግ ስርዓት ምርምር ኢንስቲቱት ባዘጋጀው የወ/ሕ/ስ/ስ/ ረቂቕ በዓንቀፅ 128 ላይ እንደተመለከተው ከሆነ ግን በተከላሹ እምነት ቃል ብቻ ሊወሰኑ የማይችሉና የሚችሉ ለይቶ ኣስቀምጧል። የዓንቀፁ ይዘት እንደሚከተለው ይላል።
ተከሳሹ ጥፋተኛ ነኝ በማለት የእምነት ቃሉን ቢሰጥም ፍ/ቤቱ ማስረጃ ሰምቶ መወሰን ኣለበት። ሆኖም የክስ ኣቤቱታ በማቅረብ በሚያስቀጣ በማንኛውም ወንጀል ወይም በደንብ መተላለፍ ፍርድ ቤቱ ማስረጃ ሳይሰማ በተከሳሹ የእምነት ቃል ብቻ የጥፋተኛነት ውሳኔ ለመስጠት ይችላል።
ይህ ረቂቅ እንዳለ ወይም በተወሰነ መልኩ በማሻሻል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያፀደቀው እንደሆነ ካለማወቃቸውና የባለሙያ ድጋፍ ሳያገኙ ወይም በሌላ ምክንያት ያልፈፀሙትን ወንጀል ፈፅመናል ብለው ለሚያምኑ ተከሳሾች ጠቃሚና በሚያስተማምን ማስረጃ ተንተርሶ ውሳኔ ለመስጠት የሚያስችል ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል።
ሆኖም በተግባር በተደጋጋሚ እንደሚታየው ተከሳሹ የተከሰስኩበት ወንጀል ፈፅሜዋሎህ፣ ጥፋተኛ ነኝ በማለት የእምነት ቃሉን ሲሰጥ ወንጀሉን ለምንና እንዴት እንደፈፀመው የሚያመለክት ዝርዝር ሁኔታ ሲገልፅ አይታይም ፣ ፍ/ቤቱም ይህን ዝርዝር ነገር እንዲገልፅ የማያደርግ መሆኑን ነው። በሌላ መልኩ ደግሞ ተከሳሽ የሰጠው የክህደት ቃል መሆኑ በግልፅ የሚያሳይ እያለ የእምነት ቃል ሰጥቷል እየተባለ የጥፋተኛነት ፍርድ ሲሰጥ ይታያል።