ጠበቃ አሊ አወል- Attorney Ali Awol

ጠበቃ አሊ አወል- Attorney Ali Awol legal consultancy & Attorney services

01/05/2026
01/05/2026

ከፍተኛ የህግ ባለሙያ
ደመወዝ 25,510
ልምድ 4/2(LL.b,LL.m)
Join👇
https://t.me/ethiolawtips

24/04/2026
04/03/2026

በፖሊስ ቁጥጥር ሥር የዋለ ግለሰብ ሊከበርለት የሚገባ መሰረታዊ መብቶች
*****//*****//*****//******
በኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት እና በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ-ሥርዓት ሕግ መሠረት፣ አንድ ግለሰብ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር በሚሆንበት ወቅት ሊከበሩለት የሚገቡ መሠረታዊ መብቶች አሉ። እነዚህ መብቶች የተያዘው ሰው ሰብአዊ ክብሩ እንዳይገፈፍና ፍትሃዊ የሕግ ሂደት እንዲያገኝ የታለሙ ናቸው።
​ዋና ዋናዎቹ መብቶች የሚከተሉት ናቸው፦
​1. የመያዝ ምክንያት የማወቅ መብት
​ማንኛውም ሰው በቁጥጥር ሥር ሲውል፣ ለምን እንደተያዘና የቀረበበት ክስ ምን እንደሆነ ወዲያውኑ በዝርዝር የመረዳት መብት አለው።
​2. ዝም የማለት መብት (Right to Silence)
​ተጠርጣሪው የሚሰጠው ማንኛውም ቃል በፍርድ ቤት በማስረጃነት ሊቀርብበት እንደሚችል ሊነገረው ይገባል። ግለሰቡ ቃሉን ከመስጠቱ በፊት፦
​ዝም የማለት መብት አለው።
​በግዳጅ ወይም በማስገደድ ቃል እንዲሰጥ አይደረግም።
​3. የሕግ አማካሪ (ጠበቃ) የማግኘት መብት
​በቁጥጥር ሥር ያለ ሰው ከጠበቃው ጋር የመገናኘትና የመመካከር መብት አለው። ጠበቃ ለማቆም አቅም ለሌላቸውና ፍትህ ሊጓደልባቸው ለሚችሉ ሰዎች መንግሥት ጠበቃ የማቆም ግዴታ ሊኖርበት ይችላል።
​4. በ48 ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት የመቅረብ መብት
​ይህ በጣም ወሳኝ መብት ነው። ፖሊስ ግለሰቡን በቁጥጥር ሥር ካዋለበት ሰዓት ጀምሮ (ወደ ፍርድ ቤት የሚወስደውን ተመጣጣኝ ጊዜ ሳይጨምር) በ48 ሰዓታት ውስጥ ፍርድ ቤት ማቅረብ አለበት። ፍርድ ቤቱም የተያዘበት ምክንያት በቂ መሆኑንና አለመሆኑን መመርመር ይኖርበታል።
​5. ከቤተሰብና ከጎብኚዎች ጋር የመገናኘት መብት
​በቁጥጥር ሥር ያለ ሰው ከቤተሰቦቹ፣ ከጓደኞቹ፣ ከሃይማኖት አባቱ ወይም ከሐኪሙ ጋር የመገናኘትና የመጎብኘት መብት አለው።
​6. በሰብአዊነት የመያዝ መብት
​በአካል ላይ ጉዳት የሚያደርስ ድብደባ፣ ኢ-ሰብአዊ አያያዝ ወይም ክብሩን የሚያዋርድ ቅጣት ሊፈጸምበት አይገባም።
​በማስገደድ ወይም በማሰቃየት የተገኘ የዕምነት ቃል በማስረጃነት ተቀባይነት የለውም።መልካም ውሎ!!!!!!

03/02/2026

ፍትህ ከሌለ መርከቧ ትሰምጣለች፣ የመርከቧ ካፒቴን ደግሞ ዳኛ ነው።
ፍርድ ቤት ብቸኛው የዜጎች የፍትህ ማግኛ አንድ ለናቱ ተቋም ነው። አንድ ሰው የመንግስት ሆስፒታል አገልግሎት ባይመቸው የግል ሆስፒታል ሄዶ ገንዘቡን ፎጭ አድርጎ ይታከማል።

ሆኖም በፍርድ ቤት ያጣኸውን ፍትህ በግል ፍርድ ቤት ሄደህ ከሰህ አታገኘውም። ለዚህም ነው በአለም ላይ ዳኞች በገንዘብ ተፅእኖ ስር ወድቀው ፍትህ እንዳያዛቡ ከፍተኛ ተከፋይ የሆኑት።

እኛ ሀገር ዳኞች የሚሰሩት የስራ ብዛትና ጫና አንፃር የሚከፈላቸው ክፍያ እዚህ ግባ የሚባል አይደለም ሳይሆን የሚያሸማቅቅ ነው።

በድረገፅ ላይ ባገኘሁት የ2026 ዳታ መሰረት የአንድ ዳኛ ደሞዝ ኢትዮዺያ ውስጥ እንደ ስራ ልምዱና እንደተሾመበት ፍ/ቤት 👉ከ300ዶላር እስከ 600ዶላር ሲሆን በአፍሪካ እጅግ ዝቅተኛው ነው።(በግሌ ዳኞችን መተቸት የሚከብደኝ ለዚህ ነው)

ጎረቤታችን ኬንያ ከ4,500ዶላር-14,000 ዶላር፣ አክስታችን ታንዛኒያ ከ2000ዶላር እስከ 20000 ዶላር ለዳኞች ይከፍላሉ። ቤትና ሌላ ጥቅማጥቅም ሳይጨምር ማለት ነው።

ቅንጦት ቢመስልም እንደማንኛውም ፀሀፊ አሜሪካን እና አውሮፓን ሳልጠቅስ ማለፍ አልችልምና የተስፋዋ ምድር አሜሪካ ለአንድ ዳኛ (እንደ ስቴቱ ቢለያይም) ከ82,000ዶላር-250,000 ዶላር፣ አውሮፓ (ሉክዘምበርግ) 117000ዶላር፣ ደቡብ ኮሪያ 64,000 ዶላር ይከፍላሉ ብሎ ድረገፁ ሲነግረኝ ስቅስቅ ብዬ ላለቅስ ነበር።

የሀገራችን ዳኞች አንጀት የሆኑ ኬዞቻችንን እየሰሩ፣ በተለያዩ በሽታዎች እየወደቁ፣ እየሞቱ፣ ስማቸው በሙስና እየተብጠለጠለ፣ “ፍትህ ጠፋ ባገሩ” እየተባለ ጣት እየተጠቆመባቸው፣ አንዳንዶቹም በሙስና ተጠልፈው እየወደቁ ፣ ልምዳቸውን ትተው ክብራቸውን ጥለው ጠበቃ እየሆኑ ያሉት ስራቸውና የሚያገኙት ክፍያ ፍፁም ስለማይጣጣም ነው።

ማንም ሰው የሚማረውና የሚሰራው በቅድሚያ ራሱንና ቤተሰቡን ለማስተዳደር ነው። ለነፍስ የሚሰሩት የሀይማኖት አባቶች እንኳን በየሀይማኖቱ የናጠጠ ኑሮ ሲመሩ ለስጋ የሚሰራ ስራን የሚሰሩ ዳኞች ከሚሰጡት እጅግ አስፈላጊ ፍትህ አንፃር በኢትዮዺያ ከፍተኛ ተከፋይ ሊሆኑ ይገባቸዋል።

ፍርድ ቤቶች በዳኝነት ክፍያ፣ በመቀጮና በተለያዩ አገልግሎቶች በተለይ በአሁኑ ሰአት ከፍተኛ ገቢ በማግኘት ላይ እንደሆኑ እናውቃለን።

እና ምነው አለቆቻችን ዳኞቻችንን ጥሩ ደመዎዝ ከፍላችሁ ተጠያቂነታቸውንም በዛው ልክ ከፍ አድርጋችሁ የተሻለ ፍትህ እንድናገኝ የማይታደርጉልን?

መሰረት ባህሩ

23/01/2026

ሁከትን በተመለከተ የፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የሰጣቼው አስገዳጅ የሕግ ትርጉሞች

🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺
✅የሁከት ይወገድልኝ ክስ የሚያቀርብ ሰው ማረጋገጥ የሚጠበቅበት ዋና ዋና ፍሬ ነገሮች ሁከት ተፈጠረበት የተባለውን ንብረት/ሀብት/ ባልተቆራረጠ መንገድ በእጁ አድርጎ በእውነት የሚያዝበት መሆኑን እና በዚህ ይዞታው ላይ በተከሳሽው ሰው/አካል ሕግ ወጥ በሆነ መንገድ ሁከት የተፈጠረበት መሆኑን፣ በአንጻሩ የባለቤትነት መብት የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለቤት የሆነ ሰው ከንብረቱ ላይ መብት ሳይኖረው ከሕግ አግባብ ውጭ ንብረቱን በእጁ ባደረገው ሰው ወይም ንብረቱን በያዘው አካል ላይ ክስ በማቅረብ የሚያስመልስበት ህጋዊ መብት (Right to bring Petitory Action) ስለመሆኑ፤ የፍ/ብ/ህ/ቁ/1140፣ 1146 እና 1149 ድንጋጌዎች ማብራሪያ ንባብ እና የፍ/ብ/ህ/ቁ/1206
​የሰ/መ/ቁ: 220031 ቅጽ 27

✅​መዝገብ ቁጥር፦ 197183 (ቅጽ 26)
የሁከት ይወገድልኝ ክስ ለማቅረብ የሚቻለው አቤቱታ አቅራቢው ለክርክሩ መነሻ በሆነው ንብረት ላይ በቀጥታ ወይም በወኪል ይዞታ ሊኖረው እና ይህንኑ በኃይል ሊነጠቅ ወይም በይዞታው ስር ባለ ንብረት ላይ የመጠቀም መብቱን የሚያውክ ተግባር ሲፈጸም፣ እንዲሁም ንብረቱ በሕግ አግባብ በይዞታው ስር የነበረና የሁከት ድርጊት ፈጻሚው የኃይል ተግባር በመጠቀም ወይም በሚስጥር ንብረቱን እንደወሰደበት ማረጋገጥ ያለበት ስለመሆኑ።
​➨የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1149/1

✅​መዝገብ ቁጥር፦ 202845 (ቅጽ 26)
ከሁከት ይወገድልኝ ክስ ጋር በተያያዘ የፍርድ ቤት ክርክር የክስ ማቅረቢያ ጊዜ አስመልክቶ ለአስተዳደር አካል የመብት ጥያቄ ማቅረቢያ ጊዜ እና ለፍርድ ቤት ክስ ማቅረቢያ ጊዜን ለይቶ ማየትና የቀረበ የመብት ጥያቄ በእርግጥም በይርጋ የሚታገድ መሆኑን ለማረጋገጥ ለመብቱ መጠየቅ መሰረት የሆነው ጉዳይ የተፈጠረበትን እና ለአስተዳደር አካል እና ለፍርድ ቤት የመብት ጥያቄው የቀረበበትን ጊዜ በአግባቡ ማየት የሚገባ ስለመሆኑ።
​➨የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1149(2) እና የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን የቤቶች አስተዳደር መመሪያ ቁጥር 02/2010 አንቀጽ 56(1(ሀ))

✅​መዝገብ ቁጥር፦ 203882 (ቅጽ 26)
ሁከት እንዲወገድ በሚል በቀረበ ክስ ሁከት ተፈጠረበት የተባለው ቤት ባለቤትነት አከራካሪ፤ ከሳሽም ቤቱ በውርስ የተገኘ ባለቤት እንደሆነ የገለጸ ከሆነ፤ ተከሳሽ የሚያነሳው ባለቤትነትን የተመለከተ ክርክር አግባብነት ያለውና ቤቱ የከሳሽ የግል ሀብት አለመሆኑ ተጣርቶ የሚሰጥ ውሳኔ ከሳሽ ለጠየቁት ዳኝነት ምላሽ የሰጠ እና በአግባቡ የተሰጠ ፍርድ ነው ከሚባል በስተቀር ፍርድ ቤት ከቀረበለት የሁከት ይወገድልኝ ክስ ጭብጥ ወጥቶ የቤት ባለቤትነት ጉዳይ ላይ ፍርድ ሰጥቷል የሚያሰኝ ስላለመሆኑ።

✅​መዝገብ ቁጥር፦ 218309 (ቅጽ 26)
የሁከት ይወገድልኝ የክስ አቤቱታ ቀርቧል ለማለት የሚቻለው ለክርክሩ መነሻ የሆነው ንብረት በእጁ አድርጎ የሚገኝ እና ንብረቱ ላይ በእውነት ለማዘዝ እንዲችል የንብረቱ አያያዝ ያልተጭበረበረና በማናቸውም መንገድ ሕገ ወጥ በሆነ ሁኔታ ያልተያዘ መሆኑ ሲረጋገጥ እና ተከሳሽ ድርጊቱን እንዲፈጽም የተፈቀደለት መብት ወይም ስልጣን የሌለው ስለመሆኑ በማያሻማ ሁኔታ ማስረዳት የሚጠበቅ ስለመሆኑ።
የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1140 እና 1149

✅የሰ/መ/ቁ 181821 (ቅጽ 25)
​በባለቤትነት መብት አለመጠን አገልግሎት በተፈጠረ ጊዜ ይህንን አስመልክቶ በፍትሐ ብሔር ህግ ቁጥር 1149 እና 1225 መሰረት የሁከት ይወገድልኝ ክስ ማቅረብ አይቻልም
የሁከት ይወገድልኝ ክስ ሊቀርብ የሚችለው በተጨባጭ በይዞታ መብት ላይ የተፈጠረን የሁከት ተግባር ለማስወገድ እንጂ፣ ሊሰራ የታሰበ ስራ ሊያስከትል የሚችለውን ስጋት በመገመት ባልተፈጸመና ወደፊት ሊፈጠር በሚችል ድርጊት ላይ የሁከት ክስ ሊቀርብ የማይቻል ስለመሆኑ። (ፍ/ብ/ህ/ቁ 1149)

​✅የሰ/መ/ቁ 184069(ቅጽ 25)
​የአስተዳደር አካል በክርክር ሂደት በፍርድ አደባባይ ከተረታ በኋላ ተከራካሪው ወገን መብት ያገኘበትን ካርታ በማምከን አስቀድሞ የተሰጠው ውሳኔ እንዲለወጥለት የሚያቀርበው አቤቱታ ውድቅ ሊደረግ የሚገባው ስለመሆኑ። (የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 9(1) (2)፣ 12/1 እና 40/1 ድንጋጌዎች እና ፍ/ብ/ህ/ቁ 1195 እና 1196)

​✅ የሰ/መ/ቁ 183001(ቅጽ 25)
​በፍ/ብ/ህግ ቁጥር 1195 (1) መሰረት የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለቤትነት ምስክር ወረቀት በማወቅ በአስተዳደር ክፍል የተሰጠው ሰው ባለቤት እንደሆነ የተወሰደውን የህግ ግምት ማስተባበል የሚቻለው ማስረጃው የተገኘው ከህግ አግባብ ውጭ በሆነ ሁኔታ መሆኑን በማስረዳት እንደሆነ፤ በፍ/ብ/ህ/ቁ 1196 በተደነገገበት ሁኔታ የሰው ምስክር በመስማትና ቦታው ድረስ በመሄድ የችሎት ምልከታ በማድረግ የሚሰጥ ውሳኔ የምስክር ወረቀት በተሰጠበት ንብረት ላይ ባለቤትነትን የማይለውጥ ስለመሆኑ።
​✅የሰ/መ/ቁ 186348(ቅጽ 25)
​የሁከት ይወገድልኝ ክስ የቀረበለት ፍርድ ቤት ሁከት የተፈጠረ መሆን አለመሆኑን አጣርቶ በመወሰን ረገድ ሁከት ተፈጠረ በተባለበት ወቅት ንብረቱ በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ መንገድ በከሳሽ ይዞታ ስር የነበረ መሆን አለመሆኑን እና ተከሳሽ በክሱ የተጠቀሰውን ተግባር ለመፈጸም የሚያስችል መብት ያለው መሆኑን አለመሆኑን እንጂ፣ ከዚህ በላይ በመሄድ በውርስ እና በይዞታ ባለቤትነት መሰረት ተደርጎ የሚሰጥ ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስሕት ነው

​✅የሰ/መ/ቁ 186461(ቅጽ 25)
​ከመሬት ጋር በተያያዘ የሚፈጠሩ መብቶች እና ግዴታዎች የሚመሩት በንብረት ህግ አጠቃላይ መርሆዎች በመሆኑ የከተማም ሆነ የገጠር መሬት አስተዳደር እና አጠቃቀምን አስመልክቶ የሚወጡ ህጎች/አዋጆች በንብረት ህግ ማዕቀፍ ውስጥ የሚመደቡ በመሆኑ ከንብረት ጋር የተገናኙ ያሉ ጽንሰ ሃሳቦች፣ ህጎች እና መርሆዎች ከመሬት ጋር በተያያዘ ለሚቀርብ ክርክር እንደአግባብነታቸው ተፈጻሚነት ያላቸው ናቼው
​አንድን ንብረት አስመልክቶ የሚቀርበውን ክስ ተከትሎ ንብረቱን የሚመለከት የህግ ክፍል ተፈጻሚ የሚሆነው ከሳሽ ክሱን ያቀረበው ንብረቱን በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ መንገድ በእጁ ካደረገ በኋላ በንብረቱ ላይ ያለው መብት እንዲከበርለት የተረጋገጠ ሲሆን በመሆኑ የታዘዘው ዳኝነት ንብረቱን የሚመለከት መሆኑ ብቻውን ጉዳዩን የንብረት ክርክር የማያደርገው ስለመሆኑ።
​✅የሰ/መ/ቁ 186946(ቅጽ 25)

​በፍ/ብ/ህግ ቁጥር 1179 ስር የተመለከተው በሌላ ሰው ይዞታ ላይ የሚደረግ ግንባታን የመቃወም ጉዳይ አግባብ ባለው የአስተዳደር አካል በተሰጠ ይዞታ ላይ በሚደረግ ግንባታ ላይ ተፈጻሚነት የለውም

✅የሊዝ ውል እንዲቋረጥ የተሰጠ አስተዳደራዊ ውሳኔ ባልተሻረበት ሁኔታ በሊዝ ውል የተያዘ መሬት ለማስለቀቅ የመሬት አስተዳደር አካል መሬቱን ለመረከብ እንዲያስችለው የሚሰጠው ማስጠንቀቂያ የሁከት ተግባር ነው ሊባል የማይችል ስለመሆኑ፤
በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1149/3/፤ የከተማ ቦታን በሊዝ ስለመያዝ አዋጅ ቁጥር 721/04 አንቀጽ 25
መዝገብ ቁጥር =158527
ቅጽ 24
✅​የሰ/መ/ቁ 12249፡- የፍርድ ቤቶች ዋናኛ ሚና ክርክሮች በተገቢው የህግ ስርዓት እንዲመሩ ማድረግ ነው፡፡ የክሱ ርዕስ ሁከት ይወገድልኝ እና በሁከት ምክንያት ያወጣሁት ወጪ እንዲከፈለኝ የሚል ሆኖ ይዘቱ ግን ሲታይ የኪራይ ውል ይፈፀምልኝ የሚል ይዘት ካለው ፍርድ ቤቱ በክርክሩ ላይ ባለው የመሪነት ሚና ክሱ እንዲሻሻል ማድረግ ይገባዋል እንጂ ሁከት አለ የለም የሚል ጭብጥ መያዝ የቀረበውን ክስ አከራክሮ መወሰን የፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 187(2)ን ያላገናዘበ ነው፡፡ ቅጽ/20
​የሰ/መ/ቁ 80241፡- የአንድ ንብረት ባለይዞታ የሆነ ሰው ይዞታውን ለመንጠቅ ወይም በይዞታው ላይ ሁከት ለመፍጠር የሚፈፀምን ማንኛውንም ድርጊት እንዲቆም ወይም ንብረቱ እንዲመለስለት ህግ ከጠበቃቸው መንገዶች አንዱ አማራጭ የይዞታ ክስ ማቅረብ ስለመሆኑ የፍ/ብ/ህ/ቁ 1149(1) ድንጋጌ ያሳያል፡፡ በዚህ ድንጋጌ መሰረት የሁከት ይወገድልኝ ክስ መቅረብ የሚችለው አቤቱታ አቅራቢው ለክርክሩ መነሻ በሆነው ነገር በቀጥታ ወይም በጠባቂ ይዞታ ሲኖረው ነው፡፡ እንዲሁም የይዞታ ክስ የሚቀርበው ለክርክሩ መነሻ የሆነውን ንብረት በወቅቱ ለመያዝ ምንም አይነት መብት በሌለው ሰው ላይ ስለመሆኑም የድንጋጌው መንፈስ ያስረዳል፡፡ የሁከት ይወገድልኝ አቤቱታ አቅራቢ በማስረጃ ማረጋገጥ ያለበት ንብረቱ በይዞታው ስር የነበረና የሁከት ድርጊት ፈጻሚው የኃይል ተግባር በመጠቀም ወይም በሚስጥር ንብረቱን የወሰደበት መሆኑን ነው፡፡ ሁከት መፍጠር የሚኖረው ባለይዞታ የሆነው ሰው በይዞታው ስር የሚገኘውን ንብረት እንዳይገለገልበት ሌላ ሰው ጣልቃ ገብቶበት መሰናክል ሲፈጠርበት ወይም ረብሻ ሲፈጠርበት ነው፡፡ ቅጽ/15

✅​የሰ/መ/ቁ 67691፡- አንድ የቤት አከራይ ባለቤት የሆነ ሰው ቤቱን በኪራይ የያዘው ሰው እንዲለቅለት ማስጠንቀቂያ መጥራና የኪራይ ውሉን ለማቋረጥ ሃሳብ ያለው መሆኑን በፍ/ብ/ህ/ቁ. 2966(1) መሰረት ማሳወቁ ከአከራይ ተከራይ ውልና ግንኙነት አንፃር የሚታይ እንጂ እንደ ሁከት ተግባር የሚቆጠር አይደለም፡፡ የፍ/ብ/ህ/ቁ. 1149(1) እንዲህ አይነት ጉዳይን አይሸፍንም፡፡ በእንዲህ አይነት ጊዜም መጠየቅ ያለበት ዳኝነት የቤቱ አከራይ ከህግ ውጭ የኪራይ ውሉን ለማቋረጥ ካሰበ በኪራይ ውሉ እንዲገደድ ውሳኔ ይሰጠኝ በማለት እንጂ ማስጠንቀቂያ በመስጠቱ ሁከት ስለፈጠረብኝ ይወገድልኝ የሚል መሆን የለበትም፡፡ ሁከት ተፈጠረብኝ ተብሎ ክስ የተመሰረተ ቢሆን እንኳን ፍ/ቤቶች የሚይዙት ጭብጥ ሁከት አለ ወይስ የለም የሚል ጭብጥ ሳይሆን አከራዩ ውሉን ለማቋረጥ ማስጠንቀቂያ መስጠቱ ተገቢ ነው ወይስ አይደለም የሚለውን መያዝ የፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 182(2)ን የሚከተል ነው፡፡ ቅጽ/13

✅​የሰ/መ/ቁ 70801፡- አንድ ንብረት በአንድ ህጋዊ ተግባር ሰበብ ወደ እጅ ገብቷል፡፡ በይዞታዬ ላይ እያለ ሁከት ተፈጠረብኝ የሚል ክስ ትክክለኛውን የሁከት ገብነት ሃሳብ ተከተሎ መቅረቡ ከተረጋገጠ ተከሳሹ ከተሰማ በኋላ በፍርድ የህግ ፅንሰ ሃሳብ ተከተሎ መቅረቡ ከተረጋገጠ...
​Transcription: Page 406 (Image 2)
​ቤቱ ሊሰጥ የሚገባው ዳኝነት ሁከት ተፈጥሯል ይወገድ ወይም የተፈጠረ ሁከት የለም በማለት የሚወሰን እንጂ በከሳሽ እጅ ንብረቱ ሊገባ የቻለበትን ህጋዊ ተግባር ለመመርመር የሚያበቃ ወይም የሚያስችል ምክንያት አይኖርም፡፡
​በፍ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ.224 መሰረት የሚሰጠው ውሳኔ ተከሳሽ የጠየቀው መሆን አለበት፡፡ ሁከት ተፈጠረብኝ ይወገድልኝ በሚል ለሚጠየቅ ዳኝነትም ሁከት መፈጠሩ መረጋገጥ አለበት፡፡ ካልተረጋገጠ ደግሞ የተፈጠረ ሁከት የለም የሚል ውሳኔ እንጅ አመልካች ንብረቱን የያዘበት ውል ወይም መንገድ ዋጋ ያለው ነው ወይስ የለውም በሚል አጥሮ መወሰን ከተጠየቀው የዳኝነት ክልል የወጣ ነው፡፡ በሽያጭ ውል መሰረት በእጅ የገባ የንግድ ድርጅት ተወሰደበት ከሆነ በፍ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ 226 ንዑስ አንቀጽ 3 እንደተመለከተው የተወሰደውና ተለይቶ የታወቀን ንብረት ለማስመለስ የፈለገ እንደሆነ የዚህ ንብረት ዋጋ ተገምቶ የስረ-ነገር ስልጣን ላለው ፍርድ ቤት ተገቢውን የዳኝነት ክፍያ በመክፈል ክሱን አቅርቦ በዚህ የክስ መስመር ተገቢው ክርክርና ንጥጥር ተደርጎ ተገቢውን ዳኝነት ማግኘት ይገባል እንጅ እንዲህ አይነቱ ሁኔታ በሁከት ይወገድልኝ አቅርቦ አይችልም፡፡ ምክንያቱም በፍ/ብ/ህ/ቁ 1149 እንደተመለከተው በሁከት ይወገድልኝ አቤቱታ ሊስተናገድ የሚገባው ጉዳይ በንብረት ላይ የተፈጠረውን ሁከት ለማስቆም (cessation interferance) ወይም ሁከት መፍጠር ተግባር እንዲታገድ (injection) ለመጠየቅ እንጂ የተወሰደ ንብረት እንደገና ወደ እጅ ለማስገባት የሚያስችል አይደለም፡፡ ቅጽ/13

✅​የሰ/መ/ቁ 27506፡- አቤቱታው ሁከት ይወገድልኝ የሚል ከሆነ ክርክሩ የይዞታ መብትን/Possessory action/ የሚመለከት በመሆኑ በጭብጥ ተይዞ እልባት ሊሰጠው የሚገባው ነጥብ ሁከት ተፈጥሯል ወይስ አልተፈጠረም የሚለው ነው፡፡ የባለቤትነት የመፋለም ክስ (petitory action) ራሱን የቻለ ክርክር ነው፡፡ በመሆኑም በሁከት ይወገድልኝ ክርክር የባለቤትነት ክርክር ማንሳት አግባብነት አይኖረውም፡፡ ቅጽ/6

✅​የሰ/መ/ቁ 36645፡- አንድ ሰው በአንድ ንብረት ላይ ባለይዞታ ለመባል ነገሩን በእጅ አድርጎ መገኘትና በእውነት የሚያዝዝበት ሆኖ መገኘት አለበት፡፡ በእውነት ብቻ ሳይሆን በዚህ ንብረት ላይ በእውነት ማዘዝ እንዲችል የንብረቱ አያያዝ ያልተጭበረበረ እና በማንኛውም መንገድ ህገ ወጥ በሆነ ሁኔታ ያልተገኘ መሆን እንደማይገባው ነው፡፡ አንድ ሰው አንድን ንብረት በሽያጭ የያዘው ከሆነ ውሉ ተገቢውን የአፃፃፍ ስርዓት /form/ ተከተሎ አልተደረገም ቢባል እንኳን ገዥው ስለመያዙ እና ገዥው በንብረቱ በእውነት የማያዝዝ መሆኑን አያረጋግጥም፡፡ የውል የአጻጻፍ ጉድለት አለበት ከተባለ በንብረቱ መብት አለን የሚሉ ሰዎች ውሉ ፈራሽ ነው እንዲባል የክስ ምክንያት ከሚሆን በስተቀር ሁከት ይወገድልኝ ተብሎ በሚቀርብ ክስ ላይ ሊስተናገድ የሚችል አይደለም፡፡ በመሆኑም ገዥው ንብረቱን ከሻጭ ጋር ባደረኩት ውል መሰረት ይዘው እያለ ሻጭ ሁከት​እየፈጠረብኝ ነው በማለት የሚያቀርበው የሁከት ይወገድልኝ አቤቱታ ተቀባይነት ካለው የፎርም ጉድለት ተለይቶ ሊስተናገድ ይገባዋል (አብላጫ ድምጽ)፡፡
​በልዩነት ሃሳብ አንድ ዳኛ በውሉ መሰረት ንብረቱ በገዢው ስም እስካልተዛወረ ድረስ ሻጭ ባለንብረት ተደርጎ ስለሚወሰድ የንብረቱ ባለይዞታ የሆነው ገዢ ሊፈጽም የሚችለው የባለቤትነት መብት ያለውን ሰው ሁከት ፈጥሮብኛል ብሎ ሊከሰስ አይችልም፡፡ የይዞታ መብትን ለማስከበር የሚቀርብ ክስ የንብረቱ ባለቤትነት ሳይሆን በይዞታ ጣልቃ የሚገቡ ሌሎች ሰዎችን ለማስቆም እና ለመከላከል የሚቀርብ የክስ አይነት ነው በማለት በልዩነት ወስኗል፡፡ ቅጽ/9

​✅​የሰ/መ/ቁ 39940፡- የይዞታ ክስ የሚቀርበው ለክርክሩ መነሻ የሆነውን ንብረት በወቅቱ ለመያዝ ምንም አይነት መብት በሌለው ሰው ሲያዝ ነው፡፡ የሁከት ይወገድልኝ አቤቱታ አቅራቢ ንብረቱ በህግ አግባብ በይዞታው የነበረና የሁከት ድርጊት ፈጻሚው የኃይል ተግባር በመጠቀም ወይም በሚስጥር ንብረቱን የወሰደበት መሆኑን፤ ሁከት ይወገድልኝ አቤቱታ አቅራቢው ሁከት ፈጥሯል ከተባለው ሰው በንብረቱ ላይ የተሻለ መብት ያለው መሆኑን ማረጋገጥ አለበት፡፡ ሁከት ፈጥሯል የተባለው ሰው ከከሳሽ የተሻለ መብት ያለው እና በአግባቡ መብት አግኝቶ ንብረቱን ይዞ ከተገኘ ሁከት ፈጥሯል ሊባል አይገባም፡፡ ቅጽ/9
✅​የሰ/መ/ቁ 42861፡- ይዞታና ባለቤትነትን የሚመለከቱ ጉዳዮች የተለያዩ እንደ መሆናቸው መጠን የሚሸፈኑት በተለያዩ የህግ ድንጋጌዎች ነው፡፡ አንድ ሰው ባደረገው የኪራይ ውል ሰበብ ቤቱን በሃይል ይዞ ለመልቀቅ ፍቃደኛ ባለመሆኑ ኪራዩን ከፍሎ ቤቱን እንዲለቅልኝ በሚል የሚያቀርበው አቤቱታ ባለሀብት የሆኑበትን ቤት ለማስለቀቅ የቀረበ የመፋለም ክስ እንጂ የይዞታ ክርክር አይደለም፡፡ በሃይል ይዟል ስለተባለ ብቻ ክሱን የሁከት ይወገድልኝ ክስ የሚያሰኘው አይደለም፡፡ እንደዚህ አይነት ክስ ላይም የፍ/ብ/ህ/ቁ 1149 ተፈጻሚ አይሆንም፡፡ ቅጽ/10

​✅ የይዞታ ይርጋ
​የሰ/መ/ቁ 60392፡- ይዞታን አስመልክቶ የሚነሳ የሁከት ይወገድልኝ አቤቱታ ጋር በተያያዘ ተፈጻሚ የሚሆነው የይርጋ ጊዜ መቆጠር ያለበት አቤቱታ አቅራቢው የይዞታ መብቱን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ከሚመለከተው አካል ካገኘበት ቀን ጀምሮ እንጂ አቤቱታ የቀረበበት ድርጊት መፈጸም ከጀመረበት ዕለት አንስቶ አይደለም፡፡ ቅጽ/11
✅​የሰ/መ/ቁ 49985፡- የፍ/ብ/ህ/ቁ/ 1149(1) ሁከት የተፈጠረበት ሰው እንዲወገድለት እና ይዞታው የተወሰደበት ሰው የተወሰደበት ነገር እንዲመለስለት የሚሉትን ሁለቱንም ዓይነቶች ሁኔታዎች ለይቶ የደነገገ ነው፡፡ ተለይቶ የታወቀ ንብረት ተወስዶብኛል ይመለስልኝ በሚል የሚቀርብ አቤቱታ በፍ/ብ/ህ/ቁ 16 እና 226(3) መሰረት ትክክለኛ ዋጋው ተገምቶ ነገሩን አይቶ ለመወሰን ስልጣን ​ላለው ፍርድ ቤት ተገቢው የዳኝነት ገንዘብ ተከፍሎበት ይቀርባል እንጂ የተፈጠረ ሁከት እንዲወገድ (cessation of interference) እንደሆነ ተቆጥሮ በገንዘብ በማይመዘኑ አቤቱታዎች በሚቀርቡበት ሁኔታ ሊስተናገድ አይገባም፡፡ አቤቱታው ተለይቶ የታወቀን ንብረት ለማስመለስ የቀረበ መሆኑን ይዘቱ የሚያመለክት ከሆነ የክስ አርዕስት ሁከት ይወገድልኝ ስለተባለ ብቻ ጉዳዩ ሁከት ይወገድልኝ ነው በማለት በፍ/ብ/ህ/ቁ 1149(2) የተቀመጠው ይርጋ ተፈጻሚ ሊሆን አይችልም፡፡ ቅጽ/11

✅​የሰ/መ/ቁ 42824፡- በፍ/ብ/ህ/ቁጥር 1225 ስር በባለቤትነት መብት ያለመጠን መገልገልን የሚደነግገው ድንጋጌ በፍ/ብ/ህ/ቁ 1149 ስር ከተመለከተው በይዞታ ላይ ሁከት ስለመፍጠር እጅጉን የተለየ ነው፡፡ በፍ/ብ/ህ/ቁ 1225 ስር የተመለከተው ጉዳይ በሰፊው በባለቤትነት መብት ላይ በህጉ ከተመለከቱት ገደቦች መካከል አንዱ ነው፡፡ ባለቤት ድርጊቱን የሚፈጽመው ወይም ሥራውን የሚፈጽመው በራሱ ንብረት ወይም ቤት ውስጥ ቢሆንም የድርጊቱ ወይም የሥራው ውጤት መገለጫዎች ሌላውን ጎረቤት ወይም ባለቤት፤ በሌላ ህጋዊ አግባብ ተጠቃሚ የሆነውን ሰው እንዳይረብሽ፤ እንዳያውክ ወይም በማንኛውም መልኩ ከተገቢው በላይ የሆነ ችግርን እንዳያስከትል በማድረግ መብቱን በልክ ባለቤቱ ይጠቀም ዘንድ ህጉ ያስቀመጠው፤ የባለቤትነት መብትን አጠቃቀም አድማሱን የሚወስን ሥርዓት ስለመሆኑ ከአንቀጽ 1226 እና ተከታዮቹ ድንጋጌዎች ጋር አዛምደን በምናነብበት ጊዜ የምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡ በመሆኑም በፍ/ብ/ህ/ቁ. 1149 ስር የተመለከተው የይርጋ ጊዜ ለጉዳዩ አግባብነት የለውም፡፡ የጉዳዩ ይዘት በፍ/ብ/ህ/ቁ. 1225 እና 1226 ድንጋጌ ስር የተመለከተውን የሚመለከት ሆኖ እያለ በይዞታ ላይ ሁከት ሲፈጠር የይርጋ ጊዜን የሚመለከተውን ድንጋጌ መሰረት በማድረግ ውሳኔ መስጠት መሰረታዊ የሆነ የህግ ስህተት ነው፡፡ ቅጽ/11

15/01/2026

Address

Addis Ababa

Telephone

+251911725753

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ጠበቃ አሊ አወል- Attorney Ali Awol posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Share

Category