03/02/2026
ፍትህ ከሌለ መርከቧ ትሰምጣለች፣ የመርከቧ ካፒቴን ደግሞ ዳኛ ነው።
ፍርድ ቤት ብቸኛው የዜጎች የፍትህ ማግኛ አንድ ለናቱ ተቋም ነው። አንድ ሰው የመንግስት ሆስፒታል አገልግሎት ባይመቸው የግል ሆስፒታል ሄዶ ገንዘቡን ፎጭ አድርጎ ይታከማል።
ሆኖም በፍርድ ቤት ያጣኸውን ፍትህ በግል ፍርድ ቤት ሄደህ ከሰህ አታገኘውም። ለዚህም ነው በአለም ላይ ዳኞች በገንዘብ ተፅእኖ ስር ወድቀው ፍትህ እንዳያዛቡ ከፍተኛ ተከፋይ የሆኑት።
እኛ ሀገር ዳኞች የሚሰሩት የስራ ብዛትና ጫና አንፃር የሚከፈላቸው ክፍያ እዚህ ግባ የሚባል አይደለም ሳይሆን የሚያሸማቅቅ ነው።
በድረገፅ ላይ ባገኘሁት የ2026 ዳታ መሰረት የአንድ ዳኛ ደሞዝ ኢትዮዺያ ውስጥ እንደ ስራ ልምዱና እንደተሾመበት ፍ/ቤት 👉ከ300ዶላር እስከ 600ዶላር ሲሆን በአፍሪካ እጅግ ዝቅተኛው ነው።(በግሌ ዳኞችን መተቸት የሚከብደኝ ለዚህ ነው)
ጎረቤታችን ኬንያ ከ4,500ዶላር-14,000 ዶላር፣ አክስታችን ታንዛኒያ ከ2000ዶላር እስከ 20000 ዶላር ለዳኞች ይከፍላሉ። ቤትና ሌላ ጥቅማጥቅም ሳይጨምር ማለት ነው።
ቅንጦት ቢመስልም እንደማንኛውም ፀሀፊ አሜሪካን እና አውሮፓን ሳልጠቅስ ማለፍ አልችልምና የተስፋዋ ምድር አሜሪካ ለአንድ ዳኛ (እንደ ስቴቱ ቢለያይም) ከ82,000ዶላር-250,000 ዶላር፣ አውሮፓ (ሉክዘምበርግ) 117000ዶላር፣ ደቡብ ኮሪያ 64,000 ዶላር ይከፍላሉ ብሎ ድረገፁ ሲነግረኝ ስቅስቅ ብዬ ላለቅስ ነበር።
የሀገራችን ዳኞች አንጀት የሆኑ ኬዞቻችንን እየሰሩ፣ በተለያዩ በሽታዎች እየወደቁ፣ እየሞቱ፣ ስማቸው በሙስና እየተብጠለጠለ፣ “ፍትህ ጠፋ ባገሩ” እየተባለ ጣት እየተጠቆመባቸው፣ አንዳንዶቹም በሙስና ተጠልፈው እየወደቁ ፣ ልምዳቸውን ትተው ክብራቸውን ጥለው ጠበቃ እየሆኑ ያሉት ስራቸውና የሚያገኙት ክፍያ ፍፁም ስለማይጣጣም ነው።
ማንም ሰው የሚማረውና የሚሰራው በቅድሚያ ራሱንና ቤተሰቡን ለማስተዳደር ነው። ለነፍስ የሚሰሩት የሀይማኖት አባቶች እንኳን በየሀይማኖቱ የናጠጠ ኑሮ ሲመሩ ለስጋ የሚሰራ ስራን የሚሰሩ ዳኞች ከሚሰጡት እጅግ አስፈላጊ ፍትህ አንፃር በኢትዮዺያ ከፍተኛ ተከፋይ ሊሆኑ ይገባቸዋል።
ፍርድ ቤቶች በዳኝነት ክፍያ፣ በመቀጮና በተለያዩ አገልግሎቶች በተለይ በአሁኑ ሰአት ከፍተኛ ገቢ በማግኘት ላይ እንደሆኑ እናውቃለን።
እና ምነው አለቆቻችን ዳኞቻችንን ጥሩ ደመዎዝ ከፍላችሁ ተጠያቂነታቸውንም በዛው ልክ ከፍ አድርጋችሁ የተሻለ ፍትህ እንድናገኝ የማይታደርጉልን?
መሰረት ባህሩ