26/04/2026
አዳዲስ የጊዜ ገደቦች
አዲሱ የወንጀል ሕግ ሥነ ሥርዓት እና ማስረጃ ዐዋጅ ቁጥር 1410/2018 ከሚደነቅባቸው አንዱ ነገር ብዙ አዳዲስ የወንጀል ፍትሕ ሂደት የጊዜ ገደቦችን መደንገጉ ነው:: ከእነዚህ መካከል ዋና ዋናዎቹን እንጠቃቅሳለን::👴🏽
(By Hailu Hasena (Lawyer)
1. የተጨማሪ የወንጀል ምርመራ ጊዜ ቀጠሮ በአንድ ጊዜ እስከ 14 ቀን ሊፈቀድ የሚቻል ሲሆን አጠቃላይ የምርመራ ጊዜ ግን #በማናቸውም ምክንያት ከ4 (አራት) ወር ሊበልጥ አይችልም: ተብሎ ትደንግጓል:: አንቀጽ 119(2)
ይሁንና ወንጀሎች ቀላል፣ መካከለኛ እና ከባድ ተብለው የተከፋፈሉ እንደመሆኑ አጠቃላይ የምርመራ ጊዜ ቀጠሮም በዚህ አግባብ ቢከፋፈል ጥሩ ነበር::👴🏽
2. የወንጀል ምርመራው ተጠናቆ በዐቃቤ ሕግ ክስ እስኪመሠርት ያለው የመሸጋገሪያ ጊዜ ቀጠሮ በመደበኛነት እስከ 20 ቀን ሆኖ በአጠቃላይ ግን ከ 34 ቀን ሊበልጥ አይችልም: ተብሎ ተደንግጓል:: አንቀጽ 119(4)፣ 197(1)፣ 198(2)
* የጊዜ ገደቡ የሚሠራው ተጠርጣሪው ተይዞ ያለ ከሆነ ብቻ ነው::
3. ፍርድ ቤት በዐቃቤ ሕግ የተመሠረተን መደበኛ ክስ አይቶ ውሳኔ የሚሰጥበት ጊዜ ተገድቧል:: አንቀጽ 232 (1), (2)::
በዚህ መሠረት:-
*ቀላል ክሶች=3 ወር (+45 ቀን) ማለትም በአጠቃላይ በ4 ወር ከ15 ቀን ውስጥ በፍ/ቤት ውሳኔ ማግኘት አለባቸው::
*መካከለኛ ክሶች =6 ወር (+3ወር) ማለትም በአጠቃላይ በ9 ወር ውስጥ በፍ/ቤት ውሳኔ ማግኘት አለባቸው::
*ከባድ ክሶች=12 ወር (+6ወር) ማለትም በአጠቃላይ በአንድ ዓመት ከ6 ወር ውስጥ በፍ/ቤት ውሳኔ ማግኘት አለባቸው::
~ያልገባኝ በእነዚህ የጊዜ ገደቦች ውስጥ ውሳኔ ካልተሰጠ ውጤቱ ምን ይሆናል የሚለው ነው—ዳኛው መዝገቡን ባለበት ይዘጋል ቢባል ጥሩ ነበር::🙄
4. በዋስትና በመስጠት፣ በመከልከል ወይም በተፈቀደ የዋስትና ዓይነት ወይም መጠን ላይ ይግባኝ ማቅረብ የሚቻለው ብይኑ በተሰጠ በ20 ቀን ውስጥ ነው::
*ይህ እንኳን ከጊዜ ገደብ አኳያ አዲስ አይደለም—ከነባሩ የወ/መ/ሥ/ሥ/ቁ. 75(1) ጋር ተመሳሳይ ነው::
ይሁንና የዋስትና ይግባኝ የቀረበለት ፍ/ቤት ይግባኙ ከቀረበበት ቀን ጀምሮ ባሉት 5 ቀናት ውስጥ በይግባኙ ላይ ውሳኔ መስጠት እንዳለበት ተደንግጓል:: አንቀጽ 152(1), 153
*ይሁንና በተለይ በቀድሞው የወ/መ/ሥ/ሥ/ቁ. 66 ሥር ማናቸውም ፍ/ቤት የዋስትና ጉዳይ ሲመጣለት በ48 ሰዓት ውስጥ መወሰን አለበት ከሚለው አኳያ ሲታይ አዲሱ ሕግ ያዘገየዋል::
5. ፍ/ቤት የቅጣት ውሳኔ የሚሰጥበት ጊዜ ተገድቧል:: ይህም ፍ/ቤት በተከሳሽ ላይ የጥፋተኛነት ፍርድ ከሰጠ በኋላ ግራ ቀኝ የቅጣት አስተያየታቸውን አጠቃለው ካቀረቡበት ቀን ጀምሮ ባሉት 15 ቀናት ውስጥ ፍ/ቤቱ የቅጣት ውሳኔ ማስተላለፍ አለበት ተብሎ ተደንግጓል:: አንቀጽ 301(1)
6. በዋናው የወንጀል ጉዳይ ላይ ይግባኝ የሚቀርብበት ጊዜ ፍርዱ፣ ውሳኔው፣ ብይኑ ወይም ትእዛዙ ከተሰጠበት ቀን ጀምሮ ባሉት 60 ተከታታይ ቀናት ውስጥ እንዲሆን ተደንግጎአል:: አንቀጽ 332(4)
*ይህም በቀድሞው የወ/መ/ሥ/ሥ/ቁ. 187 (1)፣ (2) መሠረት ይግባኝ ለማለት የሚፈልግ አካል ለይግባኝ የመዝገብ ግልባጭ እንዲሰጠው ውሳኔው በተሰጠ 15 ቀን ውስጥ ለወሰነው ፍ/ቤት ማመልከቻ የማቅረብ እና እና የውሳኔ ግልባጩ በደረሰው 30 ቀን ውስጥ ይግባኝ የማከፈት በድምሩ የ45 ቀን አሳሳች አሠራርን ቀሪ የሚያደርግ ነው::
ስለሆነም የወንጀልና የፍ/ብሔር ይግባኝ አቀራረብ የጊዜ ገደብ ተመሳሳይ ሆነ ማለት ነው::
7. የሰበር አቤቱታ የሚቀርብበት ጊዜ የመጨረሻ ውሳኔ በተሰጠ 90 ተከታታይ ቀናት ውስጥ መሆን እንዳለበት ተደንግጎአል:: አንቀጽ 344(3)
*ያው በቀድሞው የወ/መ/ሕ/ሥ/ሥ ኮድ ውስጥ ባለመጠቀሱ ምክንያት ለፎርማሊቲ ያህል አዲስ ነው ብለን ጠቀስነው እንጂ በተግባር አዲስ አይደለም::
8. የፍ/ቤት መጥሪያ ከቀነ ቀጠሮ 10 ቀን በፊት እንዲደርስ ተደንግጓል:: ማለትም የዐ/ሕግ ክስ ማመልከቻ ፍ/ቤቱ ቀጠሮ ክስ ለማንበብ ከያዘው ቀን አሥር (10) ቀን ቀደም ብሎ ለተከሳሽ ሊደርሰው ይገባል:: አንቀጽ 214(3)
እንዲሁም የተከሳሽ የመከላከያ ማስረጃ ዝርዝር መግለጫ ፍ/ቤቱ የመከላከያ ማስረጃ ለመስማት ከቀጠረበት ቀን አስቀድሞ ከ10 ቀናት በፊት ለዐ/ሕግ ሊደርሰው ይገባል:: አንቀጽ 288(2)
9. የግል አቤቱታ (private prosecution) እንዲያቀርብ በዐ/ሕግ የተፈቀደለት ሰው ፈቃዱን ባገኘ 15 የሥራ ቀን ውስጥ ክሱን አዘጋጅቶ ሥልጣን ላለው ፍ/ቤት ማቅረብ አለበት።
በመሆኑም ይህ ጊዜ ካለፈ በኋላ ክስ ማቅረብ አይችልም:: አንቀጽ 200(3)
10. የግል የወንጀል ምርመራ አቤቱታ (complaint) የሚያቀርብ ሰው አቤቱታውን ባቀረበ 10 የሥራ ቀናት ውስጥ ቀርቦ ለመርማሪ ፖሊስ ካላስረዳ የግል አቤቱታው ይሠረዛል::
አቤቱታው ከተሠረዘ በኋላ በጉዳዩ ላይ ድጋሚ አቤቱታ ማቅረብ አይችልም: ተብሎ ተደንግጓል:: አንቀጽ 64(4)
11. በልዩ የወንጀል ምርመራ ዘዴ ማስረጃ እንዲሰበሰብ በፍ/ቤት የሚሰጥ ጊዜ በመደበኛነት ከሦስት ወር አይበልጥም:: ይሁንና በዚህ ዘዴ ማስረጃ እንዲሰበሰብ በፍ/ቤት የሚሰጥ ጊዜ በማንኛውም ምክንያት ከ12 ወራት ሊበልጥ አይችልም::
አንቀጽ 105 (1)፣ (2)፣ (3)
12. የጥፋተኛነት ድርፍር (Plea bargaing) ማድረጊያ ጊዜም ተገድቧል:: ማለትም ዐቅም በላይ የሆነ ምክንያት ካላጋጣመ በስተቀር ዐ/ሕግና ተከሳሹ (ጠበቃው) የጥፋተኛነት ድርድር ለማካሄድ ከተስማሙበት ቀን ጀምሮ 45 (አርባ አምስት) ቀናት ውስጥ ድርድሩ መጠናቀቅ አለበት፡፡
አንቀጽ 175(4)
*"ከዐቅም በላይ የሆነ ምክንያት ድርድሩ እስከመቼ እንደሚራዘም ቁርጥ ገደብ ቢቀመጥ ሸጋ ነበረ::
13. ተከሳሽ በሌለበት የተሰጠ ፍርድ ድጋሚ እንዲታይ የሚቀርብ አቤቱታ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ መቅረብ አለበት:: አንቀጽ 221
*ይህ ጊዜ ከቀድሞው የወ/መ/ሥ/ሥ/ቁ. 198 ጋር ተመሳሳይ ነው::
ይሁንና በቀድሞው ኮድ የአንድ ወሩ ጊዜ መቆጠር የሚጀምረው ተከሳሹ በሌለበት ጉዳዩ ታይቶ ፍርድ እንደተሰጠበት ካወቀበት ቀን አንሥቶ ሲሆን በአዲሱ ኮድ ግን በሌለበት ጉዳዩ ታይቶ ፍርድ እንዲሰጥበት ያደረገው ምክንያት ከቀረበት ወይም ከተወገደበት ቀን ጀምሮ ነው::
*በነገራችን ላይ ጉዳዩ ተከሳሽ በሌለበት በመታየት ሂደት ላይ ያለ (ፍርድ ያላገኘ) ከሆነ ተከሳሹ በማንኛውም ጊዜ ክርክሩን መቀላቀል ይችላል:: ማለትም ፍ/ቤቱ በሌለህበት ጉዳዩን ለማየት ብይን (Ex parte ruling) ስለሰጠሁ ወደ ክርክሩ መግባት አትችልም ሊለው አይችልም:: አንቀጽ 218(4)
* አደራ! ተከሳሽ በሌለበት (trial in absentia) የተሰጠ ፍርድን ድጋሚ ማየት [አንቀጽ 218-222] እና ተከሳሽ ባለበት (trial in praesentia) ታይቶ የተሰጠ ፍርድን ድጋሚ ማየት [አንቀጽ 353-357] የተለያዩ ፅንሰ ሀሳቦች ናቸውና አይቀላቀል::
በዚህ መሠረት ተከሳሽ ባለበት ታይቶ የተሰጠ ፍርድ ድጋሚ እንዲታይ (review of judgement) ለመጠየቅ የሚቀርብ አቤቱታ የመጨረሻው ፍርድ ከተሰጠ በኋላ በማንኛውም ጊዜ ፍርዱን ለሰጠው ፍ/ቤት ሊቀርብ ይችላል:: አንቀጽ 355(1)
ነገሮች እየተወሳሰቡ፣ ጽሑፉም እየረዘመ ስለሆነ እዚህ እንቋጨው::😌
ማሳሰቢያ:- ስማችን ሳይጠቀስ በሌላ ገጽ ላይ ኮፒ-ፔስት ሲደረግ እውነቱን ለማያውቅ ሰው እኛው ራሳችን የሌላን ሰው ጽሑፍ የሰረቅን ሁሉ ሊያስመስል ስለሚችል ደስ አይለንም::😔
መልካም ጊዜ!👴🏽