26/05/2026
እንኳን ለ1 ሺህ 447ኛው የዒድ አል-አደሃ (የዓረፋ) በዓል በሰላም አደረሳችሁ።
የአርጎባ ብሔረሰብ ልዩ ወረዳ ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ መሃመድ ሰይድ አረቡ ለመላው የእስልምና እምነት ተከታዮች የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
አቶ መሃመድ ባስተላለፉት መልዕክት፣ የዒድ አል-አድሃ በዓል በእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ ትልቅ መንፈሳዊ ትርጉም የሚሰጠውና የአብሮነት እሴቶች በጉልህ የሚንጸባረቁበት መሆኑን ገልጸዋል። ሕዝበ ሙስሊሙ ከመቼውም ጊዜ በላይ በመተባበር፣ አብሮነትን በማጠናከር፣ እርስ በእርስ በመደጋገፍና በመቻቻል በዓሉን ሊያከብር እንደሚገባም አሳስበዋል።
ኃላፊው አክለውም፣ የተቸገሩ ወገኖችን መርዳት የዓረፋ በዓል ዋነኛ መገለጫ መሆኑን በመጥቀስ፣ ሕዝበ ሙስሊሙ እንደ ከዚህ ቀደሙ ሁሉ አንድነቱን በማጠናከር እምነቱ በሚያዘው መሠረት አቅመ-ደካሞችን በመርዳትና ካለው ለሌለው በማካፈል በዓሉን ሊያከብር እንደሚገባ ጥሪ አቅርበዋል።
ከተገነባው ጠንካራ አንድነት ጋር የተሻለችና የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አብሮነትን፣ ወንድማማችነትንና ይቅር ባይነትን በበለጠ ማጎልበት እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
አቶ መሃመድ ሰይድ አረቡ በመጨረሻም፣ ለመላው የእስልምና እምነት ተከታዮች በሙሉ ይህ የዒድ አል-አደሃ (የዓረፋ) በዓል የሰላም፣ የአንድነት፣ የመተሳሰብ፣ የደስታና የፍቅር እንዲሆንላቸው መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።
ዒድ ሙባረክ!