09/08/2021
ወራሽነትን ስለማጣራትና ስለ ውርስ አጣሪ
=======================
የሟች ውርስ ሟች በሞተበት ጊዜና ቦታ የሚከፈት ቢሆንም የሟች ውርስ እስከሚጣራ ድረስ የሟች ንብረት ''አንድ የተለየ ንብረት፣፣ አንደሆነ ይቆጠራል፡፡ ይኸም ማለት የሟች ንብረት ከሌሎች ሰዎች ንብረት ወይም ከወራሾቹ ንብረት ጋር ሣይቀላቀል የባለቤትነት መብቱ ለወራሾች ሣይተላለፍ እንደ አንድ ልዩ ንብረት፣ Distinct estate፣ ሆኖ መያዝ እንዳለበት የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 942 ይደነግጋል፡፡ ይኸም የሚሆነው ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ የሟች ውርስ ሣይጣራ ንብረቱ ከሌሎች ሰዎች ንብረት ጋር ቢቀላቀል ውርሱን ለማስተዳደርም ሆነ ለማከፋፈል የሚያጋጥመው ችግር ከባድ በመሆኑ ነው፡፡ በመሆኑም ውርስን የማጣራቱ ሥራ በሟች የውርስ ስርዓት አፈጻጸም ውስጥ በቀላሉ የማይታይና እጅግ በጣም አስፈላጊ ተግባር ነው፡፡ የውርስ ማጣራት ሥራ በሟች የውርስ ስርዓት ለማስፈፀም አስፈላጊ ተግባር ነው ካልን የውርስ ማጣራቱን ተግባር ሀላፊነት ወስዶ የሚያስፈጽም አንድ ወይም ከዚያ በላይ የሆኑ ሰዎች መኖር አለባቸው፡፡ እነዚህ ውርሱን የማጣራት ተግባር የሚፈጽሙትን ሰዎች የውርስ አጣሪ በመባል ይታወቃሉ።
1. #ወራሽነትን ስለማጣራት
ውርስ ማጣራት ማለት፣
የሟች ወራሾች እነማን እንደሆኑ አጣርቶ መወሰን፣
የውርሱ ሀብት መጠን አይነትና ግምት እንደዚሁም የሚገኝበትን ቦታ አጣርቶ መወሰን፣
ሌሎች ሰዎች ከሟች የተበደሩትን ገንዘብ መሰብሰብና በሟች ውርስ ላይ ሊከፍላቸው የሚገቡ አስገዳጅ የሆኑ አዳዎችን አጣርቶ መክፈል፣
እንደዚሁም ሟች ልዩ የኑዛዜ ስጦታ ያደረጉላቸውን ሰዎች የተሰጣቸውን ልዩ የኑዛዜ ስጦታ መክፈል፣
ማለት እንደሆነ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 944 ድንጋጌዎች ያስረዳሉ፡፡
እነዚህ የውርስ ማጣራት ተግባራት በብቃት እስኪከናወኑ፣ የውርሱ ንብረት እንደ ናአንድ የተለየ ንብረትን እንደሚቆጠርና ከውርሱ ሀብት ላይ ገንዘብ ለመጠየቅ መብት ያላቸው ሰዎች ማለትም የሟች አበዳሪዎች እና የፍርድ ባለመብቶች ለገንዘባቸው ዋስትናና መያዥያ የሚሆናቸው ይኸው በመጣራት ላይ ያለው የውርሱ ንብረት ነው፡፡ ይኸም በመሆኑ ውርሱ በመጣራት ላይ እያለ ከሟች ወራሾች ገንዘብ ጠያቂ የሆኑ ሰዎች በውርሱ ንብረት ላይ አንዳችም የይገባኛል ጥያቄ ማቅረብ እንደማይችሉና ምንም አይነት መብት እንደሌላቸው ከፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 943/1/ እና 943/3/ ድንጋጌዎች ያመለክታሉ፡፡
እነዚህ ድንጋጌዎች የራሣቸው ጠቀሜታና ግብ አላቸው፡፡ ምክንያቱም የሟች ውርስ በሚጣራበት ጊዜ የሟች ወራሾች አበዳሪዎችና ገንዘብ ጠያቂዎች የውርሱን ንብረት በመያዥያነት አንዳይዙ የሚያደርገው የሟች ወራሾች ከውርሱ ንብረት ድርሻ ሊያገኙ የሚችሉት ከሟች እዳ የተረፈ ንብረት ሲኖር ብቻ በመሆኑ ነው፡፡
ህጉ የሟች ወራሾች አበዳሪዎች ውርሱ በመጣራት ላይ እያለ በውርሱ ንብረት ላይ የይገባኛል ጥያቄ እንዳያቀርቡ በሟች ወራሾች እዳ ምክንያት የውርሱ ንብረት በመያዣነት እንዳይያዝ የሚከለክል ነው፡፡
እንደዚሁም ውርሱ በመጣራት ላይ እያለ ከሟች ውርስ ገንዘብ የሚጠይቁ ሰዎች ከሟች ወራሾች የግል ሀብት ላይ አንዳችም መብት እንደሌላቸው እና የሟችን የውርስ ንብረት ብቻ መከታተል እንዳለባቸው የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 943 ድንጋጌዎች ያሣያሉ፡፡
እዚህ ላይ ውርስን ማጣራት አስፈላጊነት በመጀመሪያ ከሟች ገንዘብ የሚጠይቁ ሰዎች ውርሱ ከመከፋፈሉ በፊት ገንዘባቸውን እንዲያገኙ ለማድረግ፣ በማስከተልም ከውርሱ በእዳነት የሚጠየቁ ለምሣሌ ለሟች የቀብር ስነ ስርዓት የወጣው ወጭ፣ ከውርሱ መከፈል ያለበት የቀለብ እዳ እና ሟች በልዩ ኑዛዜ የሰጣቸው ስጦታዎች በቅደም ተከተል ተከፍለው ሲያበቁ ነውና ከዚህ የተረፈ ንብረት ካለ ነው የሟች የሕግ ወራሾችና ጠቅላላ የኑዛዜ ተጠቃሚዎች ከሟች ውርስ ንብረት ድርሻቸውን ያገኛሉ፡፡
በመጨረሻም የውርስ ሕጋችን ወራሾችና የኑዛዜ ስጦታ የተደረገላቸው ሰወች ውርሱን ስለማጣራት ወይም ስለመካፈል በመካከላቸው በሚደረገው ክርክር ሁሉ አንድ ወይም ብዙ የዘመድ አስታራቂ ዳኞች እንዳያዩት ለመስማማት እንደሚችሉ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 945 ይደነግጋል፡፡
2. #የውርስ አጣሪ
ከላይ እንደተገለፀው ውርስን ማጣራት በሟች የውርስ ስርዓት አፈጻጸም ወቅት እጅግ በጣም አስፈላጊ ተግባር ነው፡፡ ይህንን ውርሱን የሚያጣራው ሰው ወይም ሰዎች የውርስ አጣሪ ተብለው ይጠራሉ፡፡ የውርስ አጣሪ ከሶስቱ በአንደኛው መንገድ ሊሾም እንደሚችል የውርስ ሕጋችን ይደነግጋል፡፡ የውርስ አጣሪ፣
በሟች ኑዛዜ መሠረት፣
በሕግ ሊመረጥ ወይም ሥልጣኑን ከሕግ ሊያገኝ፣
በዳኞች ሊሾም ይችላል፡፡
የመጀመሪያውን በተመለከተ ሟች አንድ ኑዛዜ የተወ እንደሆነና ሟቹ በዚሁ ኑዛዜ ውስጥ የኑዛዜው አስፈጻሚ የሾመ እንደሆነ ሟች የመረጠው ሰው የውርሱ አጣሪ ሆኖ ያገለግላል፡፡ ሟች በኑዛዜ የውርስ አጣሪ የሾመ እንደሆነ ሟች በግልጽ በኑዛዜው ካላመለከተ በስተቀር በሟች ኑዛዜ ጠቅላላ የኑዛዜ ስጦታ የተደረገለት ሰው ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ውርሱን የማጣራት መብት ይኖረዋል፡፡ ሟች የውርስ አጣሪውን በኑዛዜ የሾመ እንደሆነ ወይም ጠቅላላ የኑዛዜ ስጦታ አድርጐ እንደሆነ ጠቅላላ ኑዛዜ ስጦታ የተደረገለት ሰው ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ውርሱን የማጣራት መብት በቅደም ተከተል ይኖራቸዋል፡፡ ሟች የውርስ አጣሪውን በኑዛዜ የሾመ እንደሆነ ወይም ጠቅላላ የኑዛዜ ስጦታ የተደረገለት ሰው የተገኘ እንደሆነ የሟችን ያሉ ኑዛዜ ወራሾች የውርስ አጣሪነት ስልጣን የሚያስቀረው እንደሆነ በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 948 ተደንግጓል፡፡
በሁለተኛ ደረጃ ሟች በኑዛዜ የውርስ አጣሪ ያልሾሙ እንደሆነ ወይም ሟች ጠቅላላ የኑዛዜ ስጦታ ያደረገለት ሰው የሌለ እንደሆነ የሟች ያለ ኑዛዜ ወራሽ የሆኑ ሰዎች ሰውየው ከሞተበት ቀን አንስቶ ያለ አንዳች ፎርማሊቲ የውርስ አጣሪነት መብት እንደሚኖራቸው የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 947 የሚደነግግ ሲሆን ብዙ ሰዎች የውርስ አጣሪ በሆኑ ጊዜ የአጣሪነቱን ተግባር በመተባበር መስራት እንዳለባቸው ወይም አንዱን በመወከል ለማሠራት እንደሚችሉ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 958 ይደነግጋል፡፡
ሶስተኛው የውርስ አጣሪ የሚሰየምበት ስርዓት በፍርድ ቤት ውሣኔ የውርሱ አጣሪ የሚሰይምበት ሁኔታ ነው፡፡ የውርስ አጣሪ በፍርድ ቤት የሚሰየመው፣
የሟች ወራሾች የማይታወቁ አንደሆነ፣
ያለ ኑዛዜ ወራሾች ውርሱን ለማጣራት የማይፈቅዱ መሆናቸውን ገልፀው ያሣወቁ እንደሆነ፣
ሟች የኑዛዜም ሆነ ያለ ኑዛዜ ወራሽ ያልተወና የሟችን ሀብት መንግስት የሚወርሰው በሆነ ጊዜ፣
የአስተዳደር ሕጐችን ወይም ደንቦችን መሠረት በማድረግ ዳኞች የውርሱን አጣሪ እንደሚሰይሙ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 949 ድንጋጌዎች ያስረዳሉ፡፡
እንደዚሁም ዳኞች በሟች ኑዛዜ፣ በሕግ ወይም በፍርድ ቤት የተሰየመውን የውርስ አጣሪ በሌላ የውርስ አጣሪ የመተካት ስልጣን እንዳላቸው የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 951 ይደነግጋል፡፡ የውርስ አጣሪን በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 949 መሠረት መሰየምንና በሕግ ወይም በሟች ኑዛዜ ወይም ፍርድ ቤቱ ራሱ የሰየመውን የውርስ አጣሪ መተካት /replacement / እና substitution/ ሁለት የተለያዩ ጽንሰ ሀሣቦች ናቸው፡፡ ፍርድ ቤቱ በሕግ በሟች ኑዛዜ ወይም በፍርድ ቤቱ የተሰየመን አንድ የውርስ አጣሪ ስልጣንና ሀላፊነት በማንሣት ሌላ/ሌሎች/ የውርስ አጣሪ የሚሰይመው፣
ውርስ አጣሪው የተሾመበት ኑዛዜ ዋጋ ያለው ኑዛዜ መሆኑ አከራካሪ ሆኖ ሲገኝ ወይም፣
በሌላ ምክንያት ውርስ አጣሪውን በመለየት ላይ የሚያጠራጥር ነገር ሲኖር ወይም፣
ብዙ ውርስ አጣሪዎች ለምሣሌ ስልጣናቸው 947 የሚመነጭ ብዙ ያለ ኑዛዜ ወራሾች ኖረው በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 958 በሚደነግገው መሠረት ውርሱን በመተባበር በመግባባት ለማስተዳደርና ለማጣራት ያልተስማሙ እንደሆነ ወይም፣ ከወራሾቹ መካከል አንዱ አካለ መጠን የላደረሰ ልጅ ወይም የተከለከለ ሰው ወይም በማናቸውም ሌላ ምክንያት ለምሣሌ በአገር ባለመኖሩ፣ እብደቱ በግልጽ ያልታወቀ ሰው በመሆኑና በሌሎች ምክንያቶች ጥቅሙን ለማስከበር የማይችል በሆነ ጊዜ ወይም፣
የውርሱ አስተዳዳር ወይም የማጣራቱ ስራ ልዩ ችግር ያስነሣና ልዩ ሙያ ያላቸውን ሰወች ወይም ሌላ ችግሩን ለመቅረፍ የሚችል የውርስ አጣሪ መሰየም አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ወይም፣
በሕግ ሟች ኑዛዜ ወይም በዳኞች የተሰየመው አጣሪ ቸልተኛና ትጉህ ያልሆነ እንደሆነ ወይም የማጭበርበር ባህሪ የሚታይበትና ሀቀኝነት የጉደለው የሆነ አንደሆነ ወይም አጣሪው የማጣራት ስራውን በሚገባ ለመፈፀም ችሎታ የሌለው መሆኑ የታወቀ እንደሆነ፣
ዳኞች ከማናቸውም በጉዳዩ ያገባኛል ከሚል ባለጉዳይ ጥያቄ አቅራቢነት በሕግ፣ በኑዛዜ ወይም በፍርድ ቤት ውሣኔ ተሰይሞ የነበረውን የውርስ አጣሪ በመሻር በአካባቢው ውል ለማዋዋል ስልጣን የተሰጠውን ሰው ወይም ማናቸውንም ለስራው ብቁ ነው ብለው የሚመርጡትን ሌላ ሰው በውርስ አጣሪነት ለመሰየምና ለመተካት እንደሚችሉ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 951 ተመልክቶ እናገኘዋለን፡፡
በውርስ ህጋችን በግልጽ እንደተመለከተው በህግ፣ በሟች ኑዛዜ ወይም በፍርድ ቤት ውሳኔ የተመረጠ ወይም የተተካ የውርስ አጣሪ የሚከተሉት ግዴታዎችና ሀላፊነቶች ይኖሩበታል፡፡
ሟች በህይወት ዘመኑ ያደረገው ኑዛዜ ካለ ኑዛዜውን መፈለግና የሟችን የኑዛዜ ወይም ያለኑዛዜ ወራሾች እነማን እንደሆኑ ማረጋገጥ፣
የውርስ ንብረት ከብልሽትና ከብክነት ለመታደግ ተገቢውን የጥንቃቄ እርምጃ በመውሰድና ሌሎችንም አስፈላጊ ተግባራት በመፈጸም የውርሱን ሀብት ማስተዳደር፣
በግልጽ የታወቁ፣ ክርክርን የማያስነሱ መከፈል ያለባቸውን የውርስ እዳዎች በፍትሀብሄር ህግ ቁጥር 1014 በተቀመጠው ቅደም ተከተል መሰረት መክፈል፣
ሟቹ በልዩ ኑዛዜ ያደረጋቸውን ስጦታዎች መክፈልና የሟችን የኑዛዜ ቃል ለመፈጸምና ውጤት ለመስጠት ማንኛውንም አስፈላጊ ጥንቃቄ ማድረግ፣
ጥያቄው ያገባኛል በሚል ማናቸውም ባለጉዳይ ሲቀርብና ዳኞችን የሚያሳምን ሆኖ ሲገኝ ስለስራው መልካም አፈጻጸም አንድ ዋስ ወይም ሌላ የመልካም ስራ አፈጻጸም ማረጋገጫ ሊሆን የሚችል መያዣ ማቅረብ፣
ስራውን ለመተው ሲፈልግ አዲስ አጣሪ እስከሚሰየምና ተተክቶ ስራውን እስከሚጀምር ድረስ የአጣሪነት ስራውን የማከናወን፣
ሟች በአደረገው ኑዛዜ ስለአጣሪነቱ የስልጣን ወሰንና ስለስራው አፈጻጸም የሰጠውን መመሪያና ትእዛዝ ተከትሎ የመስራትና ዳኞችም ስለስልጣኑ ወሰንና ስለስራው አፈጻጸም የሚሰጡትን ትእዛዞች በማክበር የአጣሪነት ስራውን ማከናወን፣
ውርሱን አጣርቶ ከጨረሰ በኋላ ለወራሾቹ ስለማጣራቱ የስራ ክንውን ሪፖርት ማቅረብ፣
ውርስ አጣሪው ማናቸውንም የህጉን ድንጋጌዎች በሟች ኑዛዜ የተሰጡትን መመሪያዎች ወይም በዳኞች የተሰጡትን ትእዛዞች በሚቃረን በጥፋቱ ወይም በቸልተኝነቱ መንገድ ለሚያደርጋቸው ጉዳዮችና በዚያ መሰረት ለሚደርስ ጉዳት በሀላፊነት የመጠየቅ ግዴታ እንዳለበት፣
ከፍትሀብሄር ህግ ቁጥር 952፣ 954-957 እንደዚሁም የፍትሀብሄር ህግ ቁጥር 960 እና 961 በማየት መረዳት ይቻላል፡፡
በሌላ በኩል ህጉ በህግ፣ በሟች ኑዛዜ ወይም በፍርድ ቤት ውሳኔ በውርስ አጣሪነት ለሚሰየሙ ሰዎች ያስቀመጠላቸው መብት አለ፡፡ ከመብቶቹ መካከል እጅግ በጣም አስፈላጊው የውርስ አጣሪነት ስራ ማንም ሰው በፈቃዱ ብቻ ሊያከናውነው የሚገባና ማንም ሰው ያለፈቃዱ የአጣሪነት ስራዎችን ለመቀበል የማይገደድ መሆኑ ነው፡፡ አንድን ተግባር አንድ ሰው ተገድዶ እንዲያከናውን ማድረግ የተከለከለና መሰረታዊ የሆነውን የሰው ልጅ ነጻነት መብት የሚነካ በመሆኑ የውርስ አጣሪነትን ተግባር አንድ ሰው ሳይፈልግ እንዲቀበልና እንዲሰራ ማድረግ እንደማይቻል የፍትሀብሄር ህግ ቁጥር 953 በግልጽ ይደነግጋል፡፡ ሁለተኛው መብቱ ደግሞ ውርስ አጣሪው ስራውን እፍጻሜ ለማድረስ ወይም ለተወሰነ ጊዜ ለመስራት በግልጽ ግዴታ የገባ ካልሆነ በቀር በማናቸውም ጊዜ ስራውን መተው የሚችል መሆኑ ነው፡፡ እዚህ ላይ በጥንቃቄ መታየት ያለበት ጉዳይ ‹በግልጽ ግዴታ የገባ ካልሆነ በቀር› የሚለው ሀረግ ነው፡፡ በዝምታ በህግ፣ በሟች ኑዛዜ ወይም በዳኞች የውርስ አጣሪ ሆኖ እንዲሰራ መመረጡን ተቀብሎ ስራ መጀመሩ ብቻውን የማጣራት ስራውን በማናቸውም ጊዜ የመተው መብቱን አያስቀርበትም፡፡ ስራውን የመተው መብቱ ቀሪ የሚሆነው በግልጽ እራሱን ግዴታ ያስገባ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡
ሌላው እዚህ ላይ መታየት ያለበት ውርስ አጣሪው ይህንን የማጣራቱን ስራ የመተው መብቱን እንደፈለገው ሊጠቀምበት አይችልም፡፡ የሟች ውርስ ንብረት የግድ መጠበቅና በጥንቃቄ መያዝ ስለሚገባው ሌላ ተተኪ አጣሪ እስኪመረጥና ስራውን እስኪረከብ ድረስ ስራውን እየሰራ መቆየት ያለበት መሆኑ የፍትሀብሄር ህግ ቁጥር 954 ድንጋጌዎችን በማየት ለመረዳት ይቻላል፡፡
በሶስተኛ ደረጃ ለውርስ አጣሪ የተቀመጠለት መብት አጣሪው ውርሱን ለማጣራት ለሰራው ስራ የአገልግሎት ዋጋ የማግኘት መብት ያለው መሆኑ ነው፡፡ የውርሱ አጣሪ የአገልግሎት ክፍያውን የሚያገኘው ሟች በኑዛዜው ውስጥ በሰጠው መመሪያ ወይም ወራሾቹ በሚያደርጉት ስምምነት ወይም ዳኞች በሚሰጡት ውሳኔ መሰረት ሊሆን እንደሚችል የፍትሀ ብሄር ህግ ቁጥር 959 ይደነግጋል፡፡ በመሆኑም አጣሪው ውርሱን በማጣራት ለሰራው ስራና ግልጋሎት ከውርሱ ንብረት ላይ ከላይ ባስቀመጥናቸው ሁኔታዎች ሲወሰንለት የአገልግሎት ዋጋ የማግኘት መብት እንዳለው መታወቅ ይኖርበታል፡፡
በአጠቃላይ በኢትዮጵያ የውርስ ህግ መሰረት ‹ውርሱን ስለማጣራት› የሚለው ጽንሰ ሀሳብ ምንነትና ይዘት እንደዚሁም ጠቀሜታ በጥንቃቄ ሊታይ የሚገባው ነው፡፡ የመጀመሪያው በምእራፍ ሁለትም ለመጠቆም እንደተሞከረው ‹የሟች ውርስ መከፈት› እና ‹የሟችን ውርስ ማጣራት› የሚሉት ጽንሰሀሳቦች እጅግ በጣም የተለያዩ ናቸው፡፡ የሟች ውርስ መከፈት የምንለው ሟች ህይወቱ ካለፈበት ቅጽበት ጀምሮ ምንም አይነት የሲቪል መብት ግዴታ ሊኖረው ስለማይችል ህጉ የሟች ህይወት ካለፈችበት ሰኮንድ ጀምሮ የሟች መብትና ግዴታ ለሟች ወራሾች ለማስተላለፍ የሚያደርጋቸውን ጥንቃቄ የሚመለከት ነው፡፡
የሟች ውርስ የሚከፈተውም ሟች መኖሪያ ስፍራና ሟች በሞተበት ጊዜ እንደሆነ በፍትሀ ብሄር ህግ ቁጥር 826 ተመልክቷል፡፡ የሟችን ውርስ ማጣራት የምንለው ደግሞ የሟችን ያለኑዛዜና በኑዛዜ ወራሾች የሚለዩበት፣ የሟች እዳ የሚከፈልበት፣ የሟች አበዳሪዎች እና ተበዳሪዎች የሚለዩበት፣ ንብረቱ በሟች ወራሾች እስኪተላለፍና ውርሱ እስከሚዘጋበት ቀን ድረስ የንብረት ማስተዳደር ስራዎች የሚከናወንበት ውስብስብ ተግባር ነው፡፡
አሁን በስራ ላይ ያለው የውርስ ህግ አጣሪ ስለሚሆኑ ሰዎች ሲደነግግ ቀዳሚውና የመጀመሪያው የውርስ አጣሪ የሚሆነው ሟች በኑዛዜ የውርስ አጣሪ አድርጎ የሾመው ሰው እንደሆነ ከገለጸ በኀላ ሟች በኑዛዜ የውርስ አጣሪ አድርጎ የሾመው ሰው ከሌለና በኑዛዜው የውርስ አጣሪ እንደሚሆንና ጠቅላላ ኑዛዜ የተደረገለት ሰው መገኘት የሟችን ያለኑዛዜ ወራሾች የአጣሪነት ስራ እንደሚያስቀረው በፍትህብሄር ህግ ቁጥር 948 ንኡስ ቁጥር 2 እና 3 የሚደነግግ ሲሆን የሟች ውርስ መዘጋት ማለት ደግሞ የሟችን ንብረት ለወራሾች በአግባቡ የማከፋፈል ስራን አይጨምርም፡፡
የውርስ አጣሪው ሀላፊነት ከላይ ያነሳናቸውን ተግባር በመፈጸምና የሟችን ወራሾችና የሟች ከእዳ ተከፍሎ የሚቀረውን ንብረት በማጣራት፣ ዝርዝርና የመጨረሻ ሪፖርት ለወራሾቹ ማቅረብ ብቻ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ የውርሱን ንብረት ማስተዳደርም ሆነ የሟችን ንብረት መከፋፈል የወራሾች መብትና ሀላፊነት እንጂ የውርሱ አጣሪ አይደለም፡፡
በመሆኑም ውርስ አጣሪ በዋነኛነት ሊፈጽማቸው የሚችላቸው ተግባራት፣
ከሟች ውርስ መብት አለን የሚሉትን ሰዎች ሁኔታ መወሰን፣
የሟችን የውርስ ንብረት ማስተዳደር፣
የሟችን የውርስ እዳ መክፈል፣ ናቸው፡፡
©℗®
https://t.me/Consultancy2012
Call us for
©Ethio - Legal Service
Legal Service