18/01/2026
ይርጋ በውርስ ጉዳይ
አንድ ሰው በሕይወት ዘመኑ በጥረቱ ያፈራቸው ንብረቶች ባለቤት ሲሆን ይኸውም የንብረት መብት በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገመንግሥት አንቀጽ 40 መሠረት ጥበቃ ተደርጎለታል፡፡ አንድ ሰው በሕይወት ዘመኑ በጥረቱ ያፈራውን ንብረት የመያዝ፣ የመጠቀም፣ የመሸጥ፣ የማውረስ መለወጥ እና የማስተላለፍ መብት አለው፡፡ ይህ የንብረት መብት በባለንብረቱ መሞት ወደ ሕጋዊ ወራሾቹ የሚተላለፍ ሲሆን እነዚህ ወራሾችም የአውራሹን መሞት ተከትሎ የንብረቱ ባለቤትነት በውርስ እንዲተላለፍላቸው መጠየቅ ይችላሉ፡፡ ታዲያ ከአውራሹ መሞት በኋላ በምን ያህል ጊዜ ውስጥ የይገባኛል ጥያቄ ማቅረብ ይኖርባቸዋል? የውርስ ይገባኛል ጥያቄያቸውን በሕግ በተወሰነው የጊዜ ገደብ ውስጥ ባያቀርቡ መብታቸው ምን ይሆናል? የሚለው መሠረታዊ ጉዳይ ነው፡፡ በዚህ አጭር ጽሁፍም የይርጋን ምንነት መሠረታዊ ጽንሰ ሀሳብ እና የሕግ ሽፋን የምንዳስስ ይሆናል፡፡
የይርጋ ሕግ ምንነት
እንደ ብላክስለው መዝገበ ቃላት ይርጋ ማለት አንድ መብቱ ወይም ጥቅሙ የተነካበት ሰው በሌላ ሰው ላይ ክስ፣ አቤቱታ ወይም የይገባኛል ጥያቄ እንዲያቀርብ በሕግ ተለይቶ የተቀመጠ የክስ ማቅረቢያ ጊዜ ነው፡፡ በዚህም በሕግ በግልጽ የተደነገገን መብትና ወይም ግዴታ በሕጉ በተወሰነዉ ወይም በተገደበዉ ጊዜ ዉስጥ እንዲፈጸም ለፍርድ ቤት ወይም ሥልጣን ላለዉ አካል ጥያቄ ካልቀረበ መብቱ ወይም ግዴታው ቀሪ ይሆናል፡፡ የይርጋ ፅንሰ ሃሳብ እንዲኖር ያስፈለገባቸው መሠረታዊ ምክንያቶችም ከሳሽ በተገቢ ትጋትና በቂ ምክንያት መብቱን እንዲጠይቅ ለማስቻል፣ ተከሳሽ በጣም ዘግይተው የሚመጡ ክሶችን ለመከላከል ማስረጃዎች እንዳያጣ ለማድረግ እና እጅግ ዘግይተው የሚቀርቡ ክሶችና አቤቱታዎች ፍትሕ ከማስገኘት ይልቅ ለማጥቂያ መሳሪያነት ስለሚውሉ ይህንኑ ለመከላከል ነው፡፡
አብዛኛዎቹ የሕግ ጉዳዮች ላይ ክስ ለማቅረብ ወይም መብትን ለመጠየቅ የሚቻልባቸው ሁኔታዎች በጊዜ ገደብ ተለክቶ ክስ የማቅረቢያ ጊዜ የተቀመጠላቸዉ ናቸው፡፡ በመሆኑም ማናቸዉም ባለገንዘብ መብቱን በጊዜ መጠየቅ ይኖርበታል፡፡ ባለዕዳዉም ቢሆን ዕድሜ ልኩን ባለዕዳነቱን እያሰበ ተሸማቆ ሊኖር አይገባም፡፡ በሕግ በተወሰነዉ ጊዜ ዉስጥ መብትን በመጠየቅ ክስ ካልቀረበ የንብረት ጠያቂው መብት በይርጋ የሚታገድ እንደመሆኑ ንቁ ባለእዳ ክሱን በሕግ በተወሰነዉ የጊዜ ገደብ ዉስጥ ባለማቅረቡ የተነሳ በይርጋ መታገዱን ገልጾ ውድቅ እንዲደረግ ሊከራከር ይችላል፡፡ የውርስ ይርጋም የአውራሽን መሞት ተከትሎ የውርስ ይገባኛል ጥያቄ ለማቅረብ የተቀመጠ የጊዜ ገደብ ሲሆን ዝርዝሩን እንደሚከተለዉ እንመለከታለን፡፡
የውርስ ይርጋ
በኢትዮጵያ የፍትሐብሔር ሕግ 5ኛ አንቀጽ የአገሪቱ የዉርስ ሕግ ተደንግጎ ይገኛል፡፡ ዉርስ የሟች ንብረት ያለ ኑዘዜ ወይም በሟች ኑዛዜ መሠረት ለወራሾች የሚተላለፍ እንደመሆኑ በሁለቱም የውርስ ሥርአት ሕጉ የይርጋ ጊዜ ደንግጎ ይገኛል፡፡
የኑዛዜን መጽናት በመቃወም የሚቀርብ ክስ ይርጋ ጊዜ
ውርስ በሟች ኑዛዜ መሠረት በሚፈጸምበት ጊዜ ኑዛዜው ሲነበብ የነበሩ ወይም በሌላ ሰው የተወከሉ ወራሾች ኑዛዜ አይጸናም በማለት ወይም በውርስ አጣሪዉ በቀረበዉን የድልድል አመዳደብ ሀሳብ ላይ ተቃውሞ ካላቸው በፍትሐብሔር ሕጉ ቁጥር 973 መሠረት ኑዛዜዉ ከተነበበት አንስቶ በሚቆጠር የ15 ቀናት ጊዜ ውስጥ መቅረብ አለበት፡፡ ይህን ተቃውሞ ለዉርስ አጣሪዉ ከገለጹ በኋላ ባሉት ቀጣይ 3 ወራት ዉስጥ ደግሞ ክሳቸውን ካላቀረቡ ኑዛዜው ወይም በኑዛዜው የተነገረውን ዝርዝር ቃል አይጸናም በሚል ክስ ለማቅረብ አይችሉም፡፡ በሌላ በኩል በፍትሐብሔር ሕጉ አንቀጽ 974(1) መሠረት ኑዛዜው ሲነበብ በራሳቸው ላልነበሩ ወይም በተወካይ ቀርበው ላልሰሙ ሰዎች የይርጋ ጊዜው መቆጠር የሚጀምረው ውርስ አጣሪው ስለ ድልድሉ አመዳደብ፣ ስለ ክፍያው ሀሳቡን ከነገራቸው ቀን ጀምሮ ነው፡፡
ከዚህ ባለፈ በሕጉ በአንቀጽ 974(2) መሠረት ኑዛዜ ከፈሰሰበት (ከተነበበት) ጊዜ ወይም ኑዛዜ ከሌለ አውራሽ ከሞተበት ጊዜ አንስቶ ከአምስት ዓመት በኋላ ስለ ኑዛዜ መጽናት፣ ስለ ክፍያ፣ አመዳደብ፣ በአጣሪ የቀረበውን የድልድል ሀሳብ በማናቸዉም ምክንያት መቃወም አይቻልም፡፡ ስለዚህ የኑዛዜን አይጸናም ክስ ማቅረብ የሚፈልጉ ወራሾች ጉዳያቸውን እንደ ሁኔታው ከላይ በገለጽናቸው ጊዜ ገደብ ውስጥ ማቅረብ እንዳለባቸዉ የፍትሐብሔር ሕጉ ቁጥሮች 973 እና 974 ያስገነዝባሉ፡፡ በዚሁ ጊዜ ውስጥ ያልቀረበ የኑዛዜ መቃወሚያ ሕጋዊ ተቀባይነት የለውም፡፡
ይህንኑ ጉዳይ በማስመልከት የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በቅጽ 27 በመዝገብ ቁጥር 245055 ላይ በመጋቢት 27 ቀን 2016 ዓ.ም በሰጠው ውሳኔ ኑዛዜ ሲነበብ(ሲፈስ) በአካል ያልነበሩ፣ ያልተወከሉ፣ አልያም ስለ ክፍያ፤ ድልድል አመዳደብ ሃሳብ በውርስ አጣሪ ያልተነገራቸው ሰዎችን የሚመለከተው በፍሐብሔር ሕግ ቁጥር 974(2) ሥር የተመለከተው የአምስት ዓመት ይርጋ መሆኑን እና ይሄውም ይርጋ ፍፁም (Absolute) ይርጋ ስለመሆኑ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ ሰበር ሰሚ ችሎቱ የሕጉን አንቀጽ 973(3) እና 974(1) ከቁጥር 974(2) ጋር በማነጻጸር የ3 ወር እና የ5 ዓመት ኑዛዜ መቃወሚያ ይርጋን ልዩነት በተመለከተ አመልካች ኑዛዜዉ ሲነበብ ያልነበሩ ከሆነ በጉዳዩ ላይ ተፈጻሚነት ያለው ይርጋ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 974(2) ሥር የተመለከተው የአምስት ዓመት ይርጋ መሆኑን እና በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 973(3) እና 974(1) መሠረት የተደነገገው የ3 ወር ይርጋ አለመሆኑን ወስኗል፡፡ እዚህ ላይ መታወቅ የሚገባው ኑዛዜ ሲነበብ ወይም ሲፈስ መኖርና አለመኖርን፣ ስለ ክፍፍሉ፣ ድልድል ሀሳቡ በውርስ አጣሪው አለመነገር ኑዛዜውን ወይም በኑዛዜው የተነገረን ቃል ለመቃወም የሚቻልበትን የጊዜ ገደብ ላይ ያለውን ሕጋዊ ውጤት ነው። ኑዛዜን የሚቃወም ወራሽ በውርሱ መነበብ ወይም መፍሰስ በራሱም ሆነ በውክልና ባይገኝ ወይም ስለ ውረሱ ድልድል፣ አመዳደብ ሀሳብ በውርስ አጣሪው ባይገለጽለትም የኑዛዜውን መጽናት በመቃወም ክስ ማቅረብ የሚቻለው በአምስት ዓመት የጊዜ ገደብ ውስጥ ብቻ ሲሆን ይህ ጊዜ ካለፈ በኋላ የሚቀርብ የኑዛዜ ይፍረስልኝ ክስ በማናቸውም ምክንያት ተቀባይነት የለውም፡፡
ኑዛዜ ሳይኖር በወራሾች የሚቀርብ የውርስ ይገባኛል ክስ ይርጋ
ሌላው የሚነሳው የውርስ ይርጋ ወራሽ ሳይሆን ያለአግባብ የውርሱን ንብረት በእጁ ካደረገዉ ሰዉ ላይ ንብረቱን ለማስመለስ የሚቀርበዉ ክስ የሚቀርብበት የጊዜ ገደብ ነው፡፡ እንዲህ ባለው ጊዜ ከሳሹ የውርሱ ንብረቶች በተከሳሹ መያዛቸዉን ባወቀ በ3 ዓመት ጊዜ ዉስጥ ክሱን ማቅረብ እንዳለበት በፍህትሐብሔር ሕጉ አንቀጽ 1000(1) ተገልጿል፡፡ ከሳሹ ይህን ጉዳይ ያላወቀ ከሆነ ሟቹ ከሞተ ወይም ከሳሹ በመብቱ ለመሥራት ከቻለበት ቀን አንስቶ 15 ዓመት ካለፈ በኋላ የውርስ ንብረት ለማስመለስ ጥያቄ ለማቅረብ እንደማይቻል የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1000(2) ድንግጎ ይገኛል፡፡
የውርስ ንብረቱ የመሬት ይዞታ መብት ከሆነም በዚሁ አግባብ የሚታይ ሲሆን ከውርስ ውጪ በሆነ ሁኔታ የገጠር መሬት ባልተገባው ሰው ተያዘብን በሚል የሚቀርብ ክስ በገጠር መሬት አስተዳደር እና አጠቃቀም አዋጅ ቁጥር 1324/2016 አንቀጽ 64(2) መሠረት መብቱን መጠየቅ ከነበረበት ወይም ካወቀበት ጊዜ ጀምሮ በ15 ዓመት ውስጥ ክስ ካላቀረበ በይርጋ ቀሪ እንደሚሆን ደንግጎ ይገኛል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ትርጉም ሰጥቷል፡፡ በዚሁ መሠረት በመዝገብ ቁጥር 52407 (በቅጽ 11 የታተመ) እንደወሰነው የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1000 ላይ የተመለከተው የይርጋ ድንጋጌ ተፈጻሚነት የሚኖረው ወራሽ በሆኑ ተከራካሪዎች መካከል መሆኑን ነገር ግን ወራሽ በሆኑ እና ባልሆኑ ወገኖች መካከል ክርክሩ የሚደረግ ከሆነ ተፈጻሚነት ያለው የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1000 ድንጋጌ ሳይሆን በየፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1845 ላይ የተመለከተው የ10 ዓመት የይርጋ ድንጋጌ መሆኑን የሕግ ትርጉም የሰጠበት ጉዳይ ነው፡፡ ይህ የ10 ዓመት ይርጋ ጊዜ መቆጠር የሚጀምረው አውራሽ ከሞተበት ወይም ከሳሽ መብቱን ለመጠየቅ ሕጋዊ ችሎታ ካገኘበት ቀን ጀምሮ እንደሆነ ሕጉ ያመለክታል፡፡ እዚህ ላይ ፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በመዝገብ ቁጥር 171038 በየካቲት 25 ቀን 2012 ዒ.ም እና በመዝገብ ቁጥር 239453 በሐምሌ 26 ቀን 2015 ዓ/ም እንደወሰነው የሟች ንብረት ወራሽ ባልሆኑ ሰዎች ሲያዝ ህጻናት የነበሩ የሟች ወራሾች በመብታቸው መሥራት እና ንብረቱ እንዲለቀቅ ክስ ማቅረብ የሚችሉት እድሜያቸው 18 ዓመት ሲሞላ ሲሆን የውርስ ንብረቱ ሲያዝ አካለ መጠን ያልደረሱ የሟች ልጆችም ተፈጻሚነት ያለው የይርጋ ጊዜ 10 ዓመት ሲሆን ይህ የ10 ዓመት ጊዜ መቆጠር የሚጀምረው እድሜያቸው 18 ዓመት ከሞላበት ጊዜ ጀምሮ ስለመሆኑ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ በዚህም ሟች ወይም አውራሽ ሲሞት ወይም የውርስ ንብረቱ በማይገባው ሰው መያዙን ሲያውቁ እድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ወራሾች እድሜቸው 18 ዓመት ከሞላበት ቀን ጀምሮ ቀጥሎ ባሉ 10 ዓመታት የውርስ ንብረት ይገባኛል ክስ አቅርበው የውርስ ንብረቱን ካላስመለሱ ክሱ በይርጋ ቀሪ ይሆናል ማለት ነው፡፡
ማጠቃለያ
በኑዛዜም ሆነ ያለ ኑዛዜ የሚቀርብ የውርስ ንብረት ይገባኛል ክስ በማናቸውም ጊዜ የሚቀርብ ሳይሆን ሕጉ ባስቀመጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ መቅረብ ያለበት ነው፡፡ በውርስ ሕጉ መሠረት ይህን አውቆ ክሱን የይርጋ ጊዜው ከማለቁ በፊት ያላቀረበ ወራሽ የመውረስ መብቱን አውቆ በራሱ ነጻ ፈቃድ እንደተወው ግምት ተወስዶ መብቱን ያጣል፡፡ ስለሆነም የውርስ ይገባኛል ክሶች የይርጋ ጊዜያቸው ከማለቁ በፊት ሥልጣን ላላቸው ፍርድ ቤቶች ቀርበው ውሳኔ ማግኘት ይኖርባቸዋል፡፡