08/05/2024
ህግን የማወቅ አስፈላጊነት
መግቢያ
ሰዎች በተለያዩ መስኮች እውቀት ሊኖራቸው ይችላል። ይህን እውቀታቸውን እንደ ሞያ ወይም እንደመተዳደሪያ ሊጠቀሙበት የሚችሉ ሲሆን ከሞያቸው ውጪ በሆኑ ጉዳዮች ላይ የሚኖራቸው እውቀት ደግሞ እንደ ጠቅላላ እውቀት ሊጠቀሙበት ይችላሉ። ስለአንዳንድ ጉዳዮች ማወቅ በምርጫ ሊወሰን የሚችል ቢሆንም ሌሎቹን ማወቅ ግን ግድ የሚሆንባቸው ሁኔታዎች ይታያል። ከነዚህም ውስጥ በባለሞያ ደረጃ ባይሆንም ህግን ማወቅ ግድ የሚሆንበትን ሁኔታ ከተለያዩ ህጎች መገንዘብ እንችላለን። በዚህ አጭር ፅሁፍ የህግን ምንነት፣ ህግን የማወቅ ጠቀሜታ እና ህግን አለማወቅ በህጉ የሚታይበትን ሁኔታ በአጭሩ እንመለከታለን።
የህግ ምንነት
ህግ የሚለው ቃል በማህበረሰቡ ዘንድ በስፋት የሚታወቅ ቃል ሲሆን አስገዳጅ መሆኑን የሚገነዘብ ለመሆኑ ቀደም ባለው ጊዜ በየዕለት ኑሮ ፀብ ሲገጥመው እንኳን “በህግ አምላክ” ብሎ ፀብ የማብረድ ልምድ የነበረው መሆኑ ማሳያ ነው፡፡ ሆኖም ማህበረሰቡ ህግን የሚረዳው በተለምዶአዊው ሁኔታ እንጂ የዘርፉ ባለሞያዎች በሚረዱበት መልኩ አይደለም፡፡
በእርግጥ ህግ ለሚለው ቃል ትርጓሜ መስጠት ቀላል ሥራ አይደለም፡፡ ምክንያቱም የቃሉ ፅንሰ ሀሳብ ከጊዜ ወደ ጊዜ የሚለዋወጥ በመሆኑ እና የተለያዩ ምሁራን ቃሉን በተለያየ መንገድ የሚገልፁት በመሆኑ ነው፡፡ እንዲሁም የቃሉ ፍቺ ሊደረስባቸው በሚፈለጉት የተለያዩ ዓላማዎች ምክንያት ሊለያይ ይችላል። ለህግ ቃላት ትርጉም በመስጠት የሚታወቀው ብላክስ ሎው የህግ መዝገበ ቃላት በተሻሻለው ስድስተኛ እትሙ (Black’s Law Dictionary, 6th ed.,) ለህግ ትርጉም ሲሰጥ law is “a body of rules of action or conduct prescribed by controlling authority, and having binding legal force, which must be obeyed and followed by citizens subject to sanctions or legal consequence is a law.” ወደ አማርኛ በግርድፉ ሲመለስ ህግ ስልጣን ባለው አካል የተደነገገው አስገዳጅ ኃይል ያለው እና ዜጎች አክብረው ሊተገብሩት የሚገባ፤ አለመከበሩ ደግሞ ተጠያቂነት የሚያስከትል የተግባር ወይም የምግባር ድንጋጌ ነው።
ሕግን የማወቅ ጠቀሜታ
ሕግ የሀገርን ሰላም ለማስጠበቅ፣ የግለሰብ መብቶችን ለማስጠበቅ፣ ማኅበራዊ ፍትህን ለማስፈን (promote social justice) እና ሌሎች አገልግሎቶች ያሉት እንደመሆኑ ህግን ማወቅ በዋናነት
• መብትን ለመጠቀም እና ግዴታ ለመወጣት
• ለህግ ተገዢ ለመሆን
• የሌሎችን መብት ለማክበር
• እራስን ከሀላፈነት ወይም ከተጠያቂነት ለማዳን ጠቀሜታ አለው።
ህግን አለማወቅ/ስህተት ከተጠያቂነት የማያድን መሆኑ
የወንጀልም ሆነ የፍትሐብሔር ህጎቹ በህግ አውጪው አካል ወጥተው ከፀደቁበት ቀን ጀምሮ በሥራ ላይ እንደሚውሉ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም ዜጎች የህጎቹን መኖር ወይም መውጣት የማወቅ ግዴታ አለባቸው፡፡ ይህንም ህግን አለማወቅ ወይም የህግ ስህተት ከተጠያቂነት አያድንም የሚለው የህግ መርህ በላቲን Ignorantia juris non excusat ወይም በእንግሊዘኛ "ignorance of the law has no excuse" ከሮማውያን ህግ የተወሰደ ሲሆን ህግን የማያውቅ ሰው ይዘቱን ባለማወቅ ብቻ ህጉን በመተላለፍ ከተጠያቂነት ሊያመልጥ እንደማይችል የሚገልፅ የህግ መርህ ነው። ይህ ማለት አንድ ሰው ህግ ከጣሰ ህጉን ስለመጣሱ ምንም እውቀት ባይኖረውም ተጠያቂ ይሆናል ማለት ነው፡፡ በዚህም ሰዎች ህጉን አላውቀውም በማለት ድርጊታቸውን ሊከላከሉ አይችሉም፡፡ የዚህ መርህ ምክንያት ሰዎች የህጉን መኖር ቢያውቁም ህጉን አላወኩም በሚል ሰበብ ከተጠያቂነት ለማምለጥ እድል ሊያገኙ የማይገባ መሆኑ ነው፡፡
በኢትዮጵያም ህግ አለማወቅ ወይም የህግ ስህተት ከተጠያቂነት እንደማያድን መሆኑ በወንጀል ህጉ አንቀፅ 81 ስር ህግን አለማወቅ ወይም በህግ ላይ መሳሳት መከላከያ ሊሆን እንደማይችል እና በፍትሐብሔር ህግ አንቀፅ 2035/1 እና 2 ስር አንድ ሰው በህግ ላይ በትክክል የተገለፀውን ድንጋጌ፣ ልዩ ደንብና ሥርዓት የጣሰ እንደሆነ ጥፋተኛ እንደሆነ እና ህግን አለማወቅ ይቅርታ ሊያስገኝ የማይችል መሆኑ ተደንግጎ ይገኛል፡፡ መንግስትም ማህበረሰቡ ህግን አውቆ እንዲያከብር ህጎችን በተያዩ ዘዴዎች ማሳወቅ ያለበት ሲሆን በሀገራችን ዋነኛው መንገድ በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ እንዲወጣ በማድረግ ነው።
ማጠቃለያ
በአጠቃላይ ህግ የሀገርን እና የዜጎችን ሰላም ከማረጋገጥ አንፃር ጉል ሚና ያለው እንደመሆኑ እና ህግን አለማወቅም ከተጠያቂነት የማያድን በመሆኑ ዜጎች በህግ ዙሪያ ያላቸውን ግንዛቤ ማሳደግ ይጠበቅባቸዋል፡፡
በንቃተ ህግ ትምህርትና ስልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ
የፍትህ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ትስስር ገፆችን ይቀላቀሉ
Facebook
https://www.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...