12/10/2021
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል መንግስት መቀመጫ ዋና ከተማ ማነው?
፨፨፨፨፨፨፨፨፨ደምኢህክ፨፨፨፨፨፨፨፨ደምኢህክ።።።።።።
አዲሱ ክልል ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ በአዲስ የተስፋ ብርሐን ፈና ወጊ ክልል እንደሚሆን ይጠበቃል። በዚሁ ማዕቀፍ ብሔር ብሔረሰቦች እና ህዝቦች ተፈቃቅደውና ተቻችለው የጋራ ቤታቸውን ይገነባሉ። ለመገንባትም ሚሊየኖች በህዝበ ውሳኔው ድምፅ አረጋግጠዋል። ስለሆነም የጋራ ቤታቸውን ተቀምጠው የሚገነቡበት ዋና ከተማ ያስፈልጋቸዋል። ይህንኑ ተከትሎ የመዋቅራችን ከተሞች በየማህበራዊ ሚዲያ እያስተዋወቁ ይገኛል። ከተሞች ያላቸውን አቅም ሀብት መነሻ በማድረግ እያስተዋወቁ መገኘቱ ክፋት የለውም ወደፊትም ፅዱ፣ ውብ ፣ለኑሮና ለኢንቨስትመን ምቹ መሆናቸውን እያስተዋወቁ የከተሞችን ብልፅግና ማሳካት እንደሚኖርባቸው ይታመናል። ይሁን እንጂ ክፋቱ ማስተዋወቁ ሳይሆን የምናስተዋውቅበት መንገድ ጤነኛ መሆን አለበት። ዋና ከተማ ለመሆን ሲባል አንዱን በማንኳሰስ እና በማጥላላት የሌላው ደግሞ በማጋነን መሆን የለበትም። ዋና ከተማም መቀመጫ የሚመረጠው የአንድ ብሔረሰብን ህዝብ ቁጥርን ወይም አንድ መዋቅርን ወይም አንድ ከተማ ህዝብን ብቻ ለማገልገል አይደለም። ሰላም ደህንነት ወዳለበት በመሄድና ባለመሄድም አይደለም ይልቁኑ ዘላቂ ሰላምና ደህንነት እንዲሰፍን እንጂ ። ዋና ከተማ የሚሆነው ወይም የማይሆነው በማህበራዊ ሚዲያ ስለተዋወቀና ወይም ስላልተዋወቀ አይደለም። የከተማ መረጣው በመርህ እና በእውነተኛ ምክንያት እና መረጃ ተመስርቶ ብቻ እና ብቻ ነው።
፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨
ክልል የምንመሰርትበት ዋናው ምክንያት ከዚህ ቀደም በዚህ ገፅ እና 'የህዝብ አብሮነትና አንድነት ለጋራ ክልል ምስረታ' በሚለው የህዝብ ግንኘነት ሰነድ ላይ ለማመላከት ሞክረናል።ውይይትም አድርገናል። በዚሁ መሠረት ሁለት ቁልፍ ነገሮች "የፓለቲካና የኢኮኖሚ ስብራታችንን" መጠገን የሚያስችለንን እንደሆነ ከዚህ ቀደም በሚገባ መግባባት ላይ ደርሰናል። ከዚህ አንፃር ፍታሐዊ የፓለቲካ እና የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ብሎም የአከባቢውን ሰላምና ደህንነት በማረጋገጥ በህይወት የመኖር እና የመጠበቅ መብታችንን በቅርበት የሚያስጠብቅ መንግስት በማቋቋም ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ እድገትና ብልፅግና የበኩላችንን ሚና መወጣት እንደሆነ ተግባብተናል ። ይሁን እንጂ በየማህበራዊ ሚዲያ እና በሌሎች ሚዲያዎች ይህንን በሚቃረን መልኩ እኔ እኔ ነኝ በሚል ስሜት በመዋቅሮች መካከል ውጥረትን ለመፍጠር ከመንቀሳቀስ መጠበቅና በጥንቃቄ መመራትም ወይም መያዝ ይኖርበታል ። በዚህ መሐል የለውጡ ውጤት የሆነው አዲሱ ክልል ስኬታማ እንዳይሆን ለፀረ -ህዝብ ሐይሎች ምቹ እንዲሆን ውጥረት መፍጠር የለብንም ።
፨፨፨ደምኢህክ፨፨፨ደምኢህክ፨፨፨ደምኢህክ፨፨
ህዝባችንም ሆነ ሌሎች ወንድሞቻችን የዚህ ክልል ስኬትን በጉጉት የሚጠብቁ አካላት የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ዋና ከተማ ማን ይሆን? በሚል ጥያቄው እየተንሸራሸረ ይገኛል። ዋና ከተማችን አንድ ከተማን በሚያፈረጥም ሌላውን በሚያዳክም መልኩ የሚመረጥ ከተማ ሳይሆን በመርህ እና በመስፈርት በስሜትና በዘፈቀደ ሳይሆን በእውነተኛ ምክንያታዊነት የሚፈፀም ነው። በህገ መንግስታችን ደረጃም ብዝሐ ዋና ከተሞች(Multicapital cities )ወይም ከአንድ ዋና ከተማ በላይ እንደሚኖረን እንጂ 'አንድ ዋና ከተማ ብቻ' የሚኖረን ባለመሆኑ በየመዋቅሮቻችን ያለው ህዝብ ሂደቱን በመረጋጋት መጠበቅ አለበት። ከአሉባልታና ለራስ ከሚገባ በላይ ባለ አመለካከት (ከOver expectation ego) ራሱን መጠበቅ ይኖርበታል።
፨፨፨ደምኢህክ፨፨፨ደምኢህክ፨፨፨ደምኢህክ፨፨
የአዲሱ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ዋና ከተሞች የሚመረጡት
1ኛ. የአለም አቀፍ ተሞክሮ ጥናት ተደርጎ የሚፈፀም ነው። ይህም በሂደት ላይ መሆኑን መረዳት ይኖርብናል ።
2ኛ. ከኛ ተጨባጭ ሁኔታ መስፈርቶችን አንጥሮ በማውጣት በውይይት በማዳበርና መግባባት ላይ የሚደረስ መሆኑ
3ኛ. በመስፈርቱ መሠረት ለመስፈርቶቹ ግልፅ ሳይንሳዊ መመዘኛ ክብደት በመስጠት የሚከናወን በመሆኑ
4ኛ. ሁሉንም የዞን እና የልዮ ወረዳ መቀመጫ ዋና ከተሞች ወይም በመዋቅሮቻቸው የተለዮት የተሻሉ ከተሞች የውድድሩ አካል እንዲሆኑ በማደረግ እንዲመዘኑ ተደርጎ የሚፈፀም መሆኑ
5ኛ. ከተመረጡ ዋና ከተሞች ውጭ ያሉ ከተሞች እንዴት አብሮ ተሳስሮ እንዲሚያድጉ ብሎም ፍታሐዊ እና የተመጣጠነት እድገት እንዲያስመዘግቡ በሚያስችል መልኩ እንዴት ማደግ እንዳለባቸው የሚመሩበት የህግ ማዕቀፍ በማዘጋጀት የሚፈፀም ይሆናል። ይህ ሁሉ ሲወሰን ሁላችንንም በፍትሐዊነት በሚጠቅም መልኩ በመፈቃቀድና በወንድማማችነት ወደ አንድ ክልል እንድንመጣ ካስገደዱን ገፊ ምክንያቶች ወይም ያጣነውን በሚያሰገኝ የጎደለብንን በሚሞላ መልኩ ብሎም ኢኮኖሚያዊ ፣ፓለቲካዊና ስትራቴጂያዊ በሆነ መልኩ የሚመለስ ይሆናል።
ሰለሆነም ከአንድ ዋና ከተማ ይልቅ ባለብዙ ዋና ከተሞች ባለቤት የሆነ ክልል የሚመረጥ መሆኑን ህዝባችን ተንዝቦ ካላስፈላጊ ውጥረት እና አሉባልታ ራሱን በመከላከል በትዕግስት መጠባበቅ ያለበት መሆኑን እንገልፃለን።