07/06/2026
የፍትሕ ሚኒስቴር
MINISTRY OF JUSTICE
የፕሬስ መግለጫ
አዲሱ የወንጀል ሕግ ሥነ-ሥርዓትና ማስረጃ ሕግ በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ እስኪወጣ ድረስ ህዝብ እና ባለድርሻ አካላት በትዕግስት እንዲጠባበቁ የተሰጠ መግለጫ
የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ላለፉት 64 ዓመታት አገልግሎት ላይ ውሎ የቆየውን የወንጀል ሥነ-ሥርዓት ሕግ የሚተካውን የወንጀል ሥነ-ሥርዓትና ማስረጃ ሕግ አዋጅ ቁጥር 1410/2018 መጋቢት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. ማፅደቁ ይታወቃል። በዚህ መሰረት የፀደቀው የወንጀል ሥነ-ሥርዓትና ማስረጃ ሕግ በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ እና ወጥቶ ሙሉ በሙሉ ወደ ተፈፃሚነት እንዲገባ ለማስቻል የመጨረሻው የቃላት ማስተካከያ እና ሌሎች የሕግ እርማት ሥራዎች (Editorial Works) በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና በፍትሕ ሚኒስቴር በኩል በጥንቃቄ እና ትኩረት እየተከናወነ ይገኛል። ይህም አንዳንዶች መታዘብ እንደሚችሉት ሕጉ ለህዝብ በይፋ ባልተሰራጨበት ሁኔታ በተለያዩ ጊዜያት ሲዘጋጁ የነበሩ የወንጀል ሥነ-ሥርዓትና ማስረጃ ሕግ ረቂቆች ለተለያዩ ተቋማዊ አገልግሎቶች እና ስልጠናዎች በተለያዩ አካላት ዘንድ ጥቅም ላይ የሚውሉ የጽሁፍ መረጃዎች መሆናቸው ተስተውሏል።
የመጨረሻው የአርትኦት ሥራ ሳይጠናቀቅ ማንኛውም ይፋዊ ያልሆነ ሰነድ ለሥራ ማስፈጸሚያነትም ሆነ ለሌሎች ተያያዥ ተግባራት መዋል በአፈጻጸም ላይ የቃላትና የአንቀጽ አለመጣጣም እንዲሁም ሌሎች በርካታ ችግሮች እንዲከሰቱ በመፍጠር በፍታሕ ሥርዓቱ ላይ መደናገር መፍጠር ስለሚችል ይፋዊ ያልሆነ ሰነድ እስኪወጣ ድረስ ከእንዲህ መሰሉ አጠቃቀም ላይ ጥንቃቄ መደረግ እንዳለበት የፍትሕ ሚኒስቴር በጥብቅ ያሳስባል።
ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የመጨረሻው የአርትኦት ሥራ ሲጠናቀቅ ሕጉ በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ለህዝብ ተደራሽ የሚሆን መሆኑን ከገለጸ በተጨማሪ በሚኒስቴሩ ድረ-ገጽ የማህበራዊ ሚዲያ አማራጮች ላይም ይፋዊው ሰነድ በይፋ ከወጣ በኋላ የሚሰራጭ መሆኑን እያረጋገጠ በፍታሕ ሥርዓቱ ውስጥ ያሉ የሕግ ባለሙያዎች በትዕግስት እንዲጠባበቁ እና አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርጉ ሚኒስቴሩ ጥሪ ያቀርባል።
የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር
ግንቦት 30/2018 ዓ.ም