26/04/2026
በወንጀል አፈፃፀም ላይ ተካፋይ መሆን የሚያስከትለው የወንጀል ተጠያቂነት
መግቢያ
ወንጀል ማለት አንድን አታድርግ የተባለ ድርጊት ወይም ተግባር ማድረግ (መፈፅም) (commission) ወይም አድርግ የተባለ ድርጊት አለማድረግ (አለመፈፀም) (omission) ነው፡፡ አንድ ወንጀል በአንድ ሰው የወንጀል ሀሳብ ጠንሳሽነት ተጀምሮ በዚሁ ሰው ፍጻሜ ሊያገኝ እንደሚችል ሁሉ በአንድ የወንጀል ተግባር ላይ ወንጀሉን በአካል ከሚፈጽመው ሰው በተጨማሪ ሌሎች ሰዎች ከአጀማመሩ እስከ ፍጻሜው ባለው ሂደት ወይም ከዚያ በኃላ በተለያየ ደረጃዎች ሊሳተፉ ይችላሉ፡፡ በዚህ ጽሁፍም የወንጀል ተካፋይነትን በአጭሩ እንመለከታለን፡፡
በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ መሆን (አንቀጽ 32)
በወንጀል ህግ አንቀጽ 32 መሰረት አንድ ሰው በሶስት ሁኔታዎች በዋና ወንጀል አድርጊነት ተካፋይ እንደሆነ ተቆጥሮ እንደሚቀጣ የደነገገ ሲሆን ይኸውም
በወንጀል ህጉ አንቀፅ 32(1)(ሀ) መሰረት በቀጥታ ወይም በእጅ አዙር በተለይም በእንስሳ ወይም በተፈጥሮ ኃይል አማካይነት ወንጀሉን አድርጐ እንደሆነ በዋና ወንጀል አድራጊነት ወንጀል እንደፈፀመ ተደንግጓል፡፡ በእጀ አዙር ሲባል ለምሳሌ በሰው አካል እና ጤና ላይ ጉዳት ለማድረስ በማሰብ በእብድ ውሻ ሰውን ማስነከስ ወይም የተፈጥሮ ሀይልን እንደ ውሃ፣ እሳት በመጠቀም በሰው ንብረት ላይ ጉዳት ማድረስ እንደ ዋና ወንጀል አድራጊ ተቆጥሮ የሚቀጣ ይሆናል፡፡
በወንጀል ህጉ አንቀፅ 32(1)(ለ) መሰረት ወንጀሉን እሱ ራሱ በቀጥታ ባያደርግም እንኳን በመላ አሳቡና አድራጐቱ በወንጀሉ ድርጊቱና በሚሰጠው ውጤት ሙሉ ተካፋይ በመሆን ድርጊቱን የራሱ ያደርገ ሲሆን ነው፡፡ ይህም ከድርጊቱና ውጤቱ ጋር የተሟላ የሀሳብ ውህደት ያለው ማለትም በቀጥታ በአካል ወንጀሉን የሚፈፅመውን ሰው ሙሉ በሙሉ የመደገፍና የድርጊቱን ውጤት እንደ እራስ ድርጊትና ውጤት አድርጎ መቁጠር ነው፡፡
በወንጀል ህጉ አንቀፅ 32(1)(ሐ) መሰረት ሕፃንን ወይም አእምሮው ያልተስተካከለውን ወይም የአእምሮው ህመምተኞችን ማለትም ሁኔታውን የማያገናዝበውን ሰው ወንጀል ለማድረግ መሣሪያ ያደረገ ወይም ሌላውን ሰው ወንጀል እንዲያደርግ ያስገደደ ሲሆን እንደ ዋና ወንጀል አድራጊ ተቆጥሮ የሚቀጣ ይሆናል፡፡
በልዩ ወንጀል ተካፋይ መሆን (በወንጀል ህግ አንቀጽ 33)
አንዳንድ ወንጀሎች በባህሪያቸው በሁሉም ሰዎች ሊፈፀሙ የማይችሉ ዓይነት ተደርገው ሊወስዱ ይችላሉ፡፡ ለምሳሌም ወታራዊ ወንጀልን ለመፈፀም ወታደር መሆንን፣ በስልጣን ያለአግባብ መገልገል ወንጀልን ለመፈፀም የመንግስት ሰራተኛ መሆንን እና ሴትን አስገድዶ ለመድፈር ወንድ መሆን በዋናነት ሊጠይቅ ይችላል፡፡ ሆኖም አንድ ሰው ወንጀሉን ለመፈፀም የተለየ ጠባይ ያላቸውን ወንጀሎች ለመፈፀም የሚያስችለው ሁኔታ ባይኖረውም በመላ አሳቡ፣ በሙሉ ፈቃዱና በአድራጎቱ እነዚህን ወንጀሎች ለመፈፀም የተለየ ሁኔታ ካላቸው ሰዎች ጋር ከተባበረ በዋና ወንጀል አድራጊነት ሊጠየቅ የሚችልበት ሁኔታ ይኖራል፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው የመንግስት ሰራተኛ ሣይሆን በሙሉ ሀሳብ እና ድርጊት ወይም በተዘዋዋሪ መንገድ የመንግስት ሥራ ላይ ጉዳት እንዲደርስ ቢያደርግ በዋና ወንጀል አድራጊነት ሊጠየቅ ይችላል፡፡
በህብረት ስለሚፈፀም ወንጀል (አንቀጽ 35)
ቁጥራቸው ከአንድ በላይ የሆኑ ሰዎች ወንጀል ተፈጽሟል ተብሎ ሲገመት እያንዳንዱ ሰው በመርህ ደረጃ በወንጀሉ ውስጥ የነበረው ወይም ያደረገው ተሳትፎ በማስረጃ መረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ ነገር ግን እንደ አድማ እና አምባጓሮ በመሳሰሉት ወንጀሎች በተፈፀሙ ጊዜ በህብረቱ ውስጥ መገኘቱ የተረጋገጠበት ሰው ከቅጣ ነፃ የሚሆነው እራሱ በወንጀሉ ተካፋይ አለመሆኑን ማረጋገጥ ሲችል ብቻ ነው፡፡
ማነሳሳት
የወንጀል ህጉ በአንቀፅ 36(1) መሰረት ማንም ሰው ወንጀል እንዲደረግ አነሳሳ የሚባለው አስቦ ሌላውን ሰው በመጐትጐት፣ ተስፋ በመስጠት፣ በገንዘብ፣ በስጦታ፣ በማስፈራራት ወይም በማናቸውም ሌላ ዘዴ አንድ ወንጀል እንዲያደርግ ያግባባ እንደሆነ ነው፡፡ የማናሳሳት ድርጊት አንድ ሰው ወንጀል ፈፃሚውን ወንጀል እንዲፈፅም ቁርጠኛ ውሣኔ ላይ እንዲደረስ ሲያደርገው ሲሆን በወንጀል የሚጠየቀው የወንጀል ህጉ አንቀፅ 36(2) መሠረት ዋና ወንጀል አድራጊው (ተነሳሺው) ቢያንስ ወንጀሉን የመፈፀም ሙከራ አድርጎ እንደሆነ ነው፡፡ ቅጣቱም የሚወሰነው ሊደረግ ለታሰበው ወንጀል ህጉ በተደነገገው ቅጣት ልክ ሲሆን በዋና ወንጀል አድራጊው የተፈፀመው ወንጀል አነሳሹ ከፈለገው በላይ በሆነ ጊዜ አነሳሹ የሚቀጣው እርሱ በፈለገው ወይም ይሆናል ብሎ ሊገምተው በሚችለው ወንጀል ብቻ ይሆናል፡፡ ይህም በሚሆንበት ጊዜ ዋና ወንጀል አድራጊው ላደረገው ከባድ ወንጀል እራሱ ብቻ ሀላፊ እንደሚሆን ከወንጀል ህጉ አንቀፅ 36(4) መረዳት ይቻላል፡፡
አባሪነት
በወንጀል ህጉ አንቀፅ 37(1) መሰረት ማንም ሰው በወንጀል ድርጊት አባሪ ነው ተብሎ የሚቆጠረው ዋና ወንጀል አድራጊው ወንጀል ከማድረጉ በፊትም ሆነ ወይም በሚያደርግበት ጊዜ ወሬ በማቀበል፣ በመምከር፣ ወንጀል የሚያደርግበትን ዘዴ ወይም መሣሪያ ወይም ግዙፋዊ እርዳታ በመስጠት ወይም ለወንጀሉ አፈፃፀም በሚጠቅም በማናቸውም ሌላ ዓይነት መንገድ አስቦ የረዳው እንደሆነ ነው፡፡
በወንጀል ህጉ አንቀፅ 37(2) እና (3) መሰረት ታስቦ ለሚደረግ ወንጀል አባሪ መሆን ሁል ጊዜም የሚያስቀጣ ሲሆን አባሪው የሚቀጣው ወንጀሉ ቢያንስ የተሞከረ ሲሆን እንደሆነ ከህጉ ድንጋጌ መረዳት ይቻላል፡፡
ወንጀል ከተፈፀመ በኋላ ወንጀለኛን መርዳት
አንድ ሰው ወንጀል ከፈፀመ በኃላ በዚሁ ወንጀል እንዳይከሰስ ወይም እንዳይቀጣ እርዳታ የሚሰጥ ሰው ወንጀለኛን በመርዳት ተጠያቂ እንደሚሆን ከወንጀል ህጉ አንቀፅ 40 መረዳት ይቻላል፡፡ ወንጀለኛን መርዳት ከአባሪ ወይም አነሳሽነት የሚለየው በመርህ ደረጃ አባሪነትና አነሳሽነት ዋናው ወንጀል አድራጊ በሚከሰስበት የወንጀል ድንጋጌ የሚያስከስስና በዛው ድንጋጌ ላይ በተቀመጠው ቅጣት ልክ የሚያስቀጣ መሆኑ ነው፡፡ ወንጀለኛን መርዳት አስቀድሞ በተፈፀመው የወንጀል ድርጊት ያደረገው አስተዋጽኦ ባለመኖሩ እራሱ ለፈፀመው የወንጀል ድርጊት ብቻ በወንጀል ህጉ ልዩ ክፍል በተደነገገ አግባብነት ባለው ድንጋጌ የሚቀጣ ይሆናል፡፡
የህግ ሰውነት የተሰጠው ድርጅት የወንጀል ተካፋይነት
የወንጀል ህጉ አንቀፅ 34 የህግ ሰውነት የተሰጠውን ድርጅት የመንግስት አስተዳደር አካላትን ሳይጨምር በህግ ላይ በግልጽ በተደነገገ ጊዜ በዋና ወንጀል አድራጊነት፣ በአነሳሽነት ወይም በአባሪነት በወንጀል ሊቀጣ የሚችልበትን ሁኔታ በግልጽ ደንግጓል፡፡ ይኸውም ድርጅት ወንጀል እንዳደረገ ተቆጥሮ ቅጣት የሚጣልበት ከሀላፊዎቹ ወይም ከሰራተኞቹ አንዱ ከድርጅቱ ሥራ ጋር በተያያዘ የድርጅቱን ጥቅም በህገወጥ መንገድ ለማራመድ በማሰብ ወይም የድርጅቱን ህጋዊ ግዴታ በመጣስ ወይም ድርጅቱን በመሳሪያነት በመጠቀም በዋና ወንጀል አድራጊነት፣ በአነሳሽነት ወይም በአባሪነት ወንጀል ሲፈፅም ነው፡፡ በዚህ መልኩ ወንጀል ውስጥ ተሳትፎ የሚገኝ ድርጅት የሚቀጣው በወንጀል ህጉ በአንቀጽ 90 መሰረት በሚጣል በመቀጮ ሲሆን አስፈላጊ በሆነ ጊዜም ድርጅቱ እንዲታገድ፣ እንዲዘጋ ወይም እንዲፈርስ ተጨማሪ ቅጣት ሊጣልበት ይችላል፡፡
ማጠቃለያ
የወንጀል ህጉ በተለያየ ሁኔታ በወንጀል ተሳትፎ መገኘት የሚያስከትለውን የወንጀል ተጠያቂነት የደነገገ በመሆኑ ህብረተሰቡ በጉዳዩ ዙሪያ ያለውን ግንዛቤ በማሳደግ መሰል ድርጊቶች ከሚያስከትሉት የወንጀል ተጠያቂነት እራሱን ሊጠብቅ ይገባል፡፡
በንቃተ ሕግ ትምህርትና ስልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ
የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገጽን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://www.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701 ...
LinkedIn
https://www.linkedin.com/.../ministry-of-justice.../about/
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_externa