08/01/2026
በገቢ ግብር የማሻሻያ አዋጅ ቁጥር 1395/2017 ማሻሻያ የተደረገባቸው ጉዳዮች
መግቢያ
ግብር የአንድ አገር ኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነት ከሚረጋገጥባቸው መንገዶች አንዱ ሲሆን መንግሥትም የዜጎችን ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ እድገት በማረጋገጥ ረገድ ያለበትን ኃላፊነት ለመወጣት የሚያስፈልገውን ገቢ የሚያገኝበት ምንጭ ነው። የግብር ሕግ እንደማንኛውም ሌሎች ሕጎች ሁሉ ማኅበረሰቡ የደረሰበትን ሁለንተናዊ የእድገት ደረጃ ከግምት ባስገባ መልኩ ተቀርፆ በሥራ ላይ የሚውል እንደመሆኑ በየወቅቱ የሚኖሩ ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ሌሎች ለውጦችን ታሳቢ ባደረገ መልኩ መሻሻል ይኖርበታል።
የአገራችንም የግብር ሥርአት በየጊዜው የሚከሰቱ ለውጦችን ከግምት ባስገባ መልኩ የተለያዩ ማሻሻያዎችን በማድረግ አሁን ካለበት ደረጃ ደርሷል። በቅርቡ ማሻሻያ ከተደረገባቸው የግብር ሕግ አይነቶች አንዱ የገቢ ግብር አዋጅ ቁጥር 979/2008 ሲሆን በአዋጅ ቁጥር1395/2017 ማሻሻያ ተደርጎበታል። በዚህ አጭር ጽሑፍ የማሻሻያ አዋጁ ያካተታቸውን ዋና ዋና ጉዳዮች በአጭሩ እንዳስሳለን።
የማሻሻያ አዋጁ ያካተታቸው አዳዲስ ጉዳዮች
ከመቀጠር፣ ከቤት ኪራይ፣ ከንግድ ሥራ እና ከዕድል ሙከራ የሚገኝ የገቢ ግብር
ከመቀጠር፣ ከኪራይ፣ ከንግድ ሥራ እና ከዕድል ሙከራ የሚገኝ የገቢ ግብር ምጣኔዎች በማሻሻያ አዋጁ ማሻሻያ ተደርጎባቸዋል፡፡ ይኸውም በቀድሞ የገቢ ግብር አዋጅ (አዋጅ ቁጥር 979/2008 አንቀፅ 11) ተደንግጎ የነበረው ከግብር ነፃ ከሚሆነው ከመቀጠር የሚገኝ ወርሃዊ ገቢ መጠን ጀምሮ እስከ ከፍተኛው የግብር ምጣኔ ድረስ ማሻሻያ ተደርጎበታል፡፡ በቀድሞው ሕግ ከገቢ ግብር ነፃ የሆነው እስከ ብር ስድስት መቶ (600) ያለ ገቢ የነበረ ሲሆን በማሻሻያ አዋጁ አንቀፅ 2(6) መሠረት እስከ ብር ሁለት ሺ (2,000) ድረስ ያለ ከመቀጠር የሚገኝ ወርሀዊ ገቢ ከግብር ነፃ እንዲሆን ተደርጓል። በተጨማሪም ከፍተኛው የማስከፈያ ምጣኔ የሆነው 35% ከአስር ሺ ዘጠኝ መቶ (10,900) ብር ወርሃዊ ገቢ ጀምሮ ይጣል የነበረ ሲሆን በማሻሻያ አዋጁ ግን ይሄው የ35% ምጣኔ ከአስራ አራት ሺ (14,000) ብር በላይ ወርሀዊ ገቢ ባላቸው ተቀጣሪዎች ላይ ብቻ የሚጣል ይሆናል።
ሌላው በአዋጅ ቁጥር 1395/2017 ማሻሻያ የተደረገው በኪራይ እና ንግድ ሥራ ገቢዎች ምጣኔ ላይ ነው። በቀድሞው የገቢ ግብር አዋጅ (አንቀፅ 14(2)) እና 19(2) መሠረት እስከ ብር ሰባት ሺ ሁለት መቶ (7,200) ድረስ ያሉ አመታዊ የኪራይ እና የንግድ ሥራ ገቢዎች ከግብር ነፃ የነበሩ ሲሆን ይኸው መጠን በማሻሻያ አዋጁ አንቀፅ 2(😎 እና 2(10) መሠረት ማስተካከያ ተደርጎበት ወደ ብር ሃያ አራት ሺ (24,000) አመታዊ የኪራይ እና የንግድ ሥራ ገቢ ከፍ እንዲል ተደርጓል። ከፍተኛው የ35% የግብር ምጣኔ የሚጣልበትን የኪራይ እና የንግድ ሥራ የገቢ መጠን በተመለከተ በማሻሻያ አዋጁ በቀድሞ አዋጅ ከነበረው ከብር አንድ መቶ ሰላሳ ሺ ስምንት መቶ (130,800) በላይ ከፍ በማድረግ ከብር አንድ መቶ ስልሳ ስምንት ሺ (168,000) በላይ አመታዊ ገቢ ላይ እንዲሆን ተደርጓል።
ሌላኛው ከግብር ምጣኔ አንፃር ለውጥ የተደረገው ከዕድል ሙከራ በሚገኙ ገቢዎች ላይ ነው። ቀደም ሲል ከዕድል ሙከራዎች ገቢ ያገኘ ሰው የገቢውን 15% (አስራ አምስት በመቶ) ግብር እንዲከፍል የሚደረግ ሲሆን (አዋጅ ቁጥር 979/2008 አንቀፅ 57(1)፤ በማሻሻያ አዋጁ አንቀጽ 2(22) መሰረት ከዕድል ጨዋታ ገቢ ያገኘ ሰው ከገቢው ላይ 20% (ሃያ በመቶ) ግብር መክፈል ይጠበቅበታል። ነገር ግን ይሄ የግብር መጠን በዕድል ሙከራ ከአንድ ሺ ብር በታች ባገኘ ሰው ላይ አይጣልም።
የግብር ከፋይ ደረጃዎች
ሌላኛው በማሻሻያ አዋጁ ለውጥ ከተደረገባቸው ነጥቦች መካከል አንዱ የግብር ከፋይ ደረጃዎችን የተመለከተው ነው። በቀድሞው የገቢ ግብር አዋጅ 979/2008 አንቀፅ 3 መሠረት የደረጃ “ሀ”፣ “ለ” እና “ሐ” በሚል በሶስት የግብር ከፋይ ደረጃዎች ከፋፍሎ ያስቀመጣቸው ሲሆን ክፍፍሉም ጠቅላላ አመታዊ ገቢን ታሳቢ ያረገ ነው። በዚህም መሰረት ድርጅት ወይም ጠቅላላ አመታዊ ገቢው ብር አንድ ሚሊዮን (1,000,000) ወይም ከዚያ በላይ የሆነ ማንኛውም ሰው በደረጃ “ሀ” ስር የሚመደብ ሲሆን፣ ከብር አንድ ሚሊዮን (1,000,000) በታች እና ከብር አምስት መቶ ሺ (500,000) በላይ አመታዊ ገቢ ያላቸው (ድርጅቶችን ሳይጨምር) ደግሞ ደረጃ “ለ” ስር ይጠቃለላሉ። ድርጅትን ሳይጨምር አመታዊ ጠቅላላ ገቢው ከብር አምስት መቶ ሺ (500,000) በታች የሆኑ ግብር ከፋዮች በደረጃ “ሐ” ስር ይመደባሉ።
ነገር ግን በማሻሻያ አዋጁ አንቀፅ 2(2) መሠረት በሶስት ደረጃዎች የመክፈሉ ሂደት ቀርቶ የግብር ከፋዮች ደረጃ “ሀ” እና “ለ” በሚሉ ሁለት ደረጃዎች ብቻ እንዲከፈል ተደርጓል። ከአመታዊ ገቢ ምጣኔውም አንፃር ቀደም ሲል የነበረው እንዲሻሻል ተደርጎ በደረጃ “ሀ” ስር የሚወድቁ ግብር ከፋዮች ድርጅቶች ወይም ጠቅላላ አመታዊ ገቢያቸው ከብር ሁለት ሚሊዮን (2,000,000) እና በላይ የሆኑ ሌሎች ሰዎች ሲሆኑ ከዚህ መጠን በታች የሆነ ጠቅላላ አመታዊ ገቢ ያላቸው ሰዎች (ድርጅቶችን ሳይጨምር) በደረጃ “ለ” ስር እንዲመደቡ ተደርጓል።
የገቢ ምንጭ (የታክስ መሰረት) ማስፋት
የገቢ ግብር ማሻሻያ አዋጁ በቀድሞው አዋጅ ያልነበረ አዲስ የግብር ምንጭ አካቶ የወጣ ነው። ይኸውም በማሻሻያ አዋጁ ላይ ከዲጂታል ይዘት ፈጠራ የሚገኝ ገቢም ግብር እንደሚከፈልበት በግልፅ ተደንግጓል። በገቢ ግብር የማሻሻያ አዋጅ አንቀፅ 2(1) መሰረት ከዲጂታል ይዘት ፈጠራ የሚገኝ ገቢ ማለት አንድ ግለሰብ ወይም ድርጅት የቪዲዮ ማጋሪያ አገልግልቶችን፣ የማኅበራዊ ሚዲያ መድረኮችን፣ የድምጽ ማስተላለፊያ (ፖድካስት) አገልግሎቶችን እና የቀጥታ ስርጭት መድረኮችን ጨምሮ በኦንላይን (በበይነ መረብ) መድረኮች ላይ ዲጂታል ይዘትን በመፍጠር እና በማሰራጨት የሚያገኘው ማንኛውም በገንዘብ ወይም በአይነት የሚገኝ ገቢ ነው። ይህም ከማስታወቂያዎች እና ስፖንሰርሺፖች፣ ከምርት ስም ስምምነቶች እና ድጋፎች፣ ከአጋርነት ግብይት እና የምርት ምደባዎች፣ ከደጋፊዎች አስተዋጽኦ፣ ከገንዘብ ስጦታዎች ወይም የብዙሃን የገንዘብ ማሰባሰብ (ክራውድ ፈንዲንግ)፣ ከአባልነት ክፍያዎች፣ ከዲጂታል ወይም ከአካላዊ ሸቀጦች ሽያጭ፣ ከማስተዋወቂያ እንቅስቃሴ ምትክ የተገኙ ዕቃዎች ወይም አገልግልቶች እና ተመሳሳይነት ያላቸው ሌሎች ክፍያዎችን ያካትታል፡፡ በዚህም መሠረት በኢትዮጵያ ነዋሪ ወይም ነዋሪ ያልሆነ ሰው በኢትዮጵያ ውስጥ የዲጂታል አገልግሎት በመስጠት ከሚያገኘው ገቢ 5% የማይበልጥ የገቢ ግብር እንደሚከፍል በአዋጅ አንቀጽ 2(17 ተደንግጓል)። የዲጂታል አገልግሎት ምንነትን በተመለከተ፣ የማስከፈያ ምጣኔ፣ የአከፋፈል ሁኔታ እና ሌሎች ተያያዥነት ዝርዝር ጉዳዮችን በተመለከተ የሚንስትሮች ምክር ቤት በሚያወጣው ደንብ መሠረት የሚወሰን ስለመሆኑ በማሻሻያ አዋጁ ተጠቅሷል።
ከዲጂታል ይዘት ፈጠራ ሥራው ትርፍ ለማግኘት ታስቦ በመደበኛነት የሚከናወን ከሆነ፣ ፈጣሪው ድርጅት ከሆነ፣ የሂሳብ መዝገብ የሚያዝ ከሆነ ወይም ከንግድ ጋር የተያያዙ ወጪዎች ተቀናሽ የሚደረጉለት ከሆነ የሚገኘው ገቢ እንደ ንግድ ሥራ ገቢ እንደሚቆጠር ከማሻሻያ አዋጁ አንቀጽ 2(11) መረዳ ይቻላል፡፡ ከእነዚህ ሁኔታዎች ውጭ ከዲጂታል ይዘት ፈጠራ የሚገኙ ገቢዎች እንደሌላ ገቢ ተቆጥረው በአዋጁ ሠንጠረዥ “መ” መሠረት ግብር የሚጣልባው ሲሆን ዝርዝር አፈፃፀሙም በሚኒስትሮች ምክር ቤት በሚወጣ ደንብ መሠረት የሚወሰን ይሆናል። ስለሆነም የዲጂታል ይዘት አመንጪዎች እንደማንኛውም ግብር ከፋይ ሁሉ መለያ ቁጥር የማውጣት፣ ገቢን የማስታወቅ እና ሌሎችም የታክስ ከፋዮች ግዴታዎች ይኖሩባቸዋል ማለት ነው።
አማራጭ አነስተኛ ግብር
የገቢ ግብር ማሻሻያ አዋጅ ካካተታቸው አዳዲስ ጉዳዮች አንዱ አማራጭ አነስተኛ የግብር ሥርአት ነው። ግብር ከፋዮች ምንም አልሰራንም (ገቢ አላገኘንም) ወይም ስለከሰርን ግብር ልንከፈል አይገባም በማለት ማስታወቅ የተለመደ ነገር ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ማናቸውም በንግድ ሥራ ላይ የተሰማራ ሰው ለአመታት በኪሳራ ሊቀጥል እንደማይችል ግልፅ ነው። ይህም ግብር ሳይከፍሉ ገቢ በሚያስገኝ ሥራ ላይ የተሰማሩ ሰዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ ያስገንዘበናል። ከዚሁ መነሻ ከግብር ለመሸሽ ኪሳራ የሚያስታውቁ ትክክለኛውን ግብር እንዲከፍሉ፣ በትክክል ኪሳራ ያጋጠማቸው ደግሞ መክሰራቸው ሲረጋገጥ የከፈሉት ግብር እንዲካካስ ለማስቻል ሲባል አማራጭ አነስተኛ የግብር ሥርአት እንዲካተት ተደርጓል።
አማራጭ አነስተኛ የግብር ምጣኔን በተመለከተ በአዋጅ ቁጥር 1395/2017 አንቀፅ 2(11) መሠረት ማናቸውም ድርጅት ወይም ሰው ግብር በሚወሰንበት የግብር አመት ከሁሉም የንግድ ሥራ የገቢ ምንጮች ባገኘው ትርፍ ላይ ሊከፍል የሚገባው ግብር በዚሁ የግብር አመት ካገኘው ጠቅላላ ገቢ ከ2.5% (ከሁለት ነጥብ አምስት በመቶ) በታች ከሆነ በአዋጁ በተመለከተው የማስከፈያ ምጣኔ መሠረት አማራጭ አነስተኛ ግብር መክፈል እንደሚኖርበት ተደንግጓል።
በጥሬ ገንዘብ የሚደረግ ግብይት ላይ የተደረገ ገደብ
ሌላኛው የተሻሻለው የገቢ ግብር አዋጅ ይዞት የመጣው ጉዳይ በጥሬ ገንዘቦች የሚደረጉ ግብይቶች ላይ ገደብ ማበጀት ነው። በጥሬ ገንዘብ የሚደረግ ግብይት ስለግብር ከፋዩ ግብይት በቂ መረጃ እንዳይኖር በማድረግ ለታክስ መሰወር ድርጊት በር ከፋች ይሆናል። ይህንንም ለመቀነስ እንዲያስችል ማናቸውም ግብር ከፋይ ወደ ባንክ ሂሳብ ገቢ በሚደረግ ቼክ፣ ወደ ባንክ ሂሳብ ገቢ በሚደረግ የባንክ ድራፍት፣ ከባንክ ሂሳብ ወደ ባንክ ሂሳብ ገንዘብ በማስተላለፍ ወይም በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ፈቃድ በተሰጣቸው የክፍያ መፈጸሚያ መንገዶች ካልሆነ በስተቀር በአንድ ቀን ውስጥ ከአንድ ሰው ጋር በተደረገ ጠቅላላ ግብይት ወይም ከአንድ ግብይት ጋር በተያያዘ የሚፈጸም ክፍያ ወይም ከአንድ ሰው ጋር ከተፈጸመ አንድ ግብይት ወይም ተግባር ጋር የተያያዘ ክፍያ/ግብይቶች ከሃምሳ ሺ (50,000) ብር በላይ በጥሬ ገንዘብ መቀበል አይቻልም። ነገር ግን ይህ ገደብ በመንግሥት መስሪያ ቤቶች፣ በመንግሥት የልማት ድርጅቶች፣ በባንኮች እና በማይክሮ ፋይናንስ ድርጅቶች እንዲሁም የገንዘብ ሚኒስቴር በሚያወጣው መመሪያ መሠረት በተለዩ ሰዎች ወይም ድርጅቶች ላይ ተፈፃሚ እንደማይሆን ከማሻሻያ አዋጁ አንቀፅ 2(28) ድንጋጌ መረዳት ይቻላል።
ማጠቃለያ
በአጠቃላይ የገቢ ግብር ማሻሻያ አዋጅ ቁጥር 1395/2017 ከላይ የተጠቀሱትን ዋና ዋና ማሻሻያዎች ጨምሮ ገቢ ስለሚጣመርበት ሁኔታ፣ ግብር ቀደም ብሎ የሚከፈልበትን አሰራር እና ሌሎች ማሻሻያዎችን አካቶ ወደ ሥራ የገባ ሕግ ነው። ምንጭ የፍትሕ ሚኒስቴር
ታማኝ ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት የቢሮውን ማኅበራዊ ሚዲያ ማስፈንጠሪያ ይጠቀሙ እናመሰግናለን!!
ዌብሳይት:- aabof.com.et
ፌስቡክ:-https://www.facebook.com/aabof.gov.et?mibextid=ZbWKwL
ቴሌግራም:- https://t.me/AACABOFP
ዩቲዩብ:- youtube.com/channel/UCTPN7Re7T7tp_ekAhVuw2uA
ዋትሳፕ:-https://chat.whatsapp.com/FLSn12vRmsR9JsKUVDWxgtuuuu