Negesse Asnake Law Office

Negesse Asnake Law Office It is licensed lawyer and consultant of law

17/02/2024

የማታለል ወንጀሎች በኢ.ፌ.ዲ.ሪ የወንጀል ህግ
➖➖➖➖➖➖➖➖➖➖➖➖➖
ወንጀል በሰው ልጆች አካል፣ ክብር ወይም ንብረት ላይ ሊፈፀም የሚችል እኩይ ተግባር ሲሆን የተለያዩ ማህበራዊ፣ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም ስነ ልቦናዊ ጉዳትን ያስከትላል፡፡ ወንጀል እንዳይፈፀም መከላከል አንደኛው እና ዋናው የፍትህ አካላት እና የህብረተሰብ ሀላፊነት ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ የወንጀል ድርጊት ተፈፅሞ ሲገኝ ደግሞ ተገቢውን ህጋዊ የእርምት እና የቅጣት እርምጃ መውሰድ ተገቢ ነው፡፡ በመሆኑም የወንጀል ህግ ወንጀል ናቸው ብሎ እንዳይፈፀሙ የከለከላቸውን ወይም ደግሞ ያለመፈፀም ወይም ያለማድረግ የወንጀል ሀላፊነት እንደሚያስከትል የተቀመጡትን ድንጋጌዎች ማክበር ግድ ይላል፡፡ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. የወንጀል ህግ ለንብረት ጥበቃ ከሚያደርጉእና በንብረት ላይ ሊፈፀሙ የሚችሉ ወንጀሎች ከሚዘረዝሩ ድንጋጌዎች መካከል የአታላይነት ወይም የማታለል ወንጀል አንዱ ነው፡፡ የተለያዩ የማታለል ድርጊቶችን በመፈፀም የሰዎች ንብረት የአታላዮች ሲሳይ ሲሆን መስማት በእለት ተእለተ እንቀስቃሴችን ውስጥ የሚያጋጥመን ጉዳይ ነው፡፡ በመሆኑም በዚህ አጭር የንቃተ ህግ ፅሁፍየማታለል ወንጀል ምንነት፣በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. የወንጀል ህግ የተካተቱ የአታላይነት ወንጀሎች፣ ስለ ከባድ አታላይነት እንዲሁም ወንጀሎቹ የሚያስከትሉት የወንጀል ተጠያቂነት ይዳሰሳሉ፡፡

• የማታለል ወንጀል ምንነት

ማታለል ሆን ብሎ ሰውን በማጭበርበር ዋጋ ያለውን ነገር በአብዛኛው የገንዘብ ጥቅምን ለማግኘት የሚፈፀም ተግባር ነው፡፡ በአጠቃላይ ማታለል የሚፈጸመው ለማሳሳት ወይም ለማታለል የታሰበ የሀሰት መግለጫዎችን ወይም ታማኝነት የጎደለው ድርጊት በመጠቀም ሲሆን በንብረት ላይ ጉዳት የማስከተል ውጤት ይኖረዋል፡፡ የማታለል ድርጊት የወንጀል እና ፍትሐ ብሄር ሀላፊነትን የሚያስከትል ሲሆን የፍትሐ ብሄር ሀላፊነት ንብረቱን የማስመለስ ወይም ካሳ ማስከፈልን ተግባራዊ ያደርጋል፡፡ በሌላ በኩል የወንጀል ተጠያቂነት የእስራት እና የገንዘብ መቀጮ ቅጣቶችን የሚያስከትል ሲሆን በመቀጠል በወንጀል ህጉ የአታላይነት ምንነት ለመረዳት የሚጠቅመንን የህግ ድንጋጌ እንመለከታለን፡፡

በ1996 ዓ/ም በወጣው የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. የወንጀል ህግ አንቀፅ 692 ስር እንደተደነገገው ማንም ሰው የማይገባ ብልፅግና ለራሱ ለማግኘት ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ አሳሳች የሆኑ ነገሮችን በመናገር፣የራሱን ማንነት ወይም ሁኔታ በመሰወር ወይም መግለጽ የሚገባውን ነገር በመደበቅ ወይም የሌላውን ሰው የተሳሳተ እምነት ወይም ግምት በመጠቀም፣በማድረግም ሆነ ባለማድረግ ሌላውን ሰው አታልሎ የራሱን ወይም የሶስተኛ ወገንን የንብረት ጥቅም የሚጎዳ አድራጎት እንዲፈፀም ያደረገ እንደሆነ የአታላይነት ወንጀል እንደተፈፀመ ያስቀምጣል፡፡ በመሆኑም ይህ ወንጀል በቀላል እስራት ወይም እንደነገሩ ከባድነትከአምስት ዓመት በማይበልጥ ፅኑ እስራትና በገንዘብ መቀጮ ያስቀጣል፡፡

ከድንጋጌው መገንዘብ እንደሚቻለው የአታላይነት ወንጀልን ለማቋቋም አራት መሰረታዊ ማቋቋሚያዎች ያሉ ሲሆን እነሱም፡-
 ወንጀለኛውበአንቀፁ የተዘረዘሩትን ተግባራት ሆን ብሎ የፈፀመ እንደሆነ ፣
 በዚህ ድርጊት የተነሳ ተበዳዩ ከተታለለ ወይም በአጥፊው ወይም በወንጀለኛው የተገለፀውን አምኖ የተቀበለ እንደሆነ(ለምሳሌ ስለሞያው ወይም ስለስራው የተሳሳተ ንግግር ተበዳዩ ያመነ እንደሆነ፣የሀሰት ውክልና አሳይቶ ያንን ውክልና ያመነ እንደሆነ)፣
 በሀሰት የተገለፀውን በማመን የፈፀመው ተግባር ያለ እንደሆነ (ለምሳሌ ገንዘብ፣ጌጣ ጌጥ፣ንብረት የሰጠ እንደሆነ፣በቂ ገንዘብ የሌለውን ቼክ በመቀበል ግብይት ፈፅሞ እንደሆነ)፣
 እንደዚሁም ተበዳዩ በመታለሉ የተነሳ የራሱ ወይም ሶስተኛ ወገን ያጣው የገንዘብ ወይም ዋጋ ያለው ነገር ጥቅምመኖር መቻል ያለበት መሆኑ ናቸው ፡፡

ከባድ አታላይነት

አንድ የማታለል ወንጀል በከባድ አታላይነት የሚያስቀጣው ፡-
o አድራጊው የማህበር፣ የባንክ፣ የንግድ፣ የአክሲዮን ገበያ ወይም የኢንዱስትሪ መስሪያ ቤት አክሲዮን፣ የእዳ ሰነድ፣ የቦንድ ወይም ማናቸውንም የዋስትና ሰነድ በማውጣት ከህዝብ ገንዘብ ለመሰብሰብ ጥሪ ያደረገ ወይም ለራሱ ወይም ለድርጅቱ ወይም አድራጊው የአክሲዮን ባለድርሻ ለሆነበት ድርጅት የሸጠ እንደሆነ ወይም
o ወንጀሉን የፈፀመው በሕዝብ አስተዳደር ወይም በሕዝብ አገልግሎት ላይ እንደሆነ ከአስር አመት በማይበልጥ ፅኑ እስራትናእስከ ብር ሃምሳ ሺህ በማይበልጥ መቀጮ እንደሚቀጣ በወንጀል ህጉ አንቀፅ 696 ስር ተደንግጎ ይገኛል፡፡
በሌላ በኩል የማታለል ወንጀል የተፈፀመው በየመንግስት ወይም የህዝባዊ ድርጅት ሠራተኛ ከሆነ ከሶስት ዓመት እስከ አስር ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት እና ከሶስት ሺህ ብር እስከ ሰላሳ ሺህ ብር በሚደርስ የገንዘብ መቀጮ እንደሚያስቀጣ የሙስና ወንጀሎች አዋጅ ቁጥር 881/2007 አንቀፅ 32/1 ይደነግጋል፡፡ እንዲሁም በማታለል ወንጀሉ የተገኘው ጥቅም ከፍተኛ ወይም በመንግስት ወይም በህዝባዊ ድርጅት ወይም በህዝብ ጥቅም ላይ የደረሰው ጉዳት ከፍተኛ ከሆነ፣ በወንጀል አድራጊው የስልጣን ደረጃ የወንጀሉ አፈፃፀም ከባድ አድርጎት እንደሆነ ቅጣቱ ከአምስት ዓመት እስከ አስራ አምስት ዓመት የሚደርስ ፅኑ እስራት እና ከአስር ሺህ ብር እስከ አንድ መቶ ሺህ ብር በሚደርስ የገንዘብ መቀጮ እንደሚቀጣ የአዋጁ እንቀፅ 32/2 ያስቀምጣል፡፡ በተጨማሪም ወንጀሉ የተፈፀመው በሕዝብ አስተዳደር ወይም በሕዝብ አገልግሎት ላይ እንደሆነ እንደነገሩ ሁኔታ ከላይ ከተመለከቱት ቅጣቶች በአንዱ እንደሚቀጣ በአዋጁ እንቀፅ 32/3 ስር ተደንግጎ ይገኛል፡፡

ማታለልን ያካተቱ ወንጀሎች እና የሚያስከትሉት ቅጣት

የተለያዩ የማታለል ወንጀሎች በተበዳዮች ላይ ሲፈፀሙ እንሰማለን፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የራስን እውነተኛ ማንነት በመደበቅ በማህበራዊ ሚዲያ ነፃ የትምህርት እድል እንደሚሰጡ በመግለፅ፣ የፍቅር ጓደኝነት በመመስረት ከተግባቡ በኋላ ወደ ወጪ ሀገር እንደሚወስዱ በመግለፅ በተለያየ መንገድ በማሳመን ገንዘብ መቀበል፣ ፈጣን ሎተሪ ደርሶት ገንዘቡን ለመውሰድ መታወቂያ ስለሌለው በተበዳይ መታወቂያ እንዲያወጣ በማሳመን ለመያዣነት ስልክ፣ ገንዘብ፣ ኮምፒውተር፣ ገንዘብ እና የመሳሰሉትን በመቀበል መሰወር ፣ በባንክ ደብተር ውስጥ በቂ ገንዘብ ሳይኖር ገንዘብ እንዳለ በማሳመን ግብይት መፈፀም፣የስልክ ቁጥሩ የሎተሪ አሸናፊ እንደሆነ በመግለፅ ገንዘቡ እንዲላክላቸው የሞባይል ካርድ እንዲሞሉ ወይም የባንክ አካውንት ውስጥ ገንዘብ እንዲያስገቡ በማሳመን ገንዘብ መቀበል ለአብነት ሊጠቀሱ የሚችሉ የማታለል ወንጀሎች ናቸው፡፡

እነዚህ እና ሌሎች የማታለል ድርጊቶች በወንጀል ህጉ ያላቸውን ሽፋን እና የሚያስከትሉትን ቅጣት እንደሚከተለው እናያለን፡፡

 የሚያዝበት ገንዘብ ሳይኖር ቼክ ማውጣት በወንጀል ህጉ እንቀፅ 693/1/ እና 2 ስር የሚስጠይቅ ሲሆን ማንም ሰው ቼክ በሚያወጣበት ወይም ለባንክ በሚያቀርብብት ጊዜ የሚያዝበት በቂ ገንዘብ አለመኖሩን እያወቀ ቼክ ያወጣወይም የሰጠ እንደሆነ በቀላል እስራት (ከአስር ቀን እስከ 3 ወር) ወይም እንደነገሩ ከባድነት ከአስር ዓመት በማይበልጥ ፅኑ እስራትና በመቀጮ እንደሚቀጣ ይደነግጋል፡፡ እንዲሁም በቼክ የማታለል ድርጊቱ የተፈፀመው በቸልተኝነት(ለምሳሌ ተከሳሹ በአካውንቱ ውስጥ በቂ ገንዘብ ያለው መስሎት ያለውን የገንዘብ መጠን ሳያረጋግጥ የፈረመ) እንደሆነ በገንዘብ መቀጮ ወይም ከአንድ አመት በማይበልጥ ቀላል እስራት ይቀጣል፡፡
 በተጭበረበረ ሁኔታ የአክሲዮን ገበያን ንግድ ማካሄድ ሌላው በወንጀል ህጉ የተካተተ የማታለል ወንጀል አይነት ሲሆን ማንም ሰው በአክሲዮን ገበያ ወይም በሌላ ገበያ አማካኝነት የአክሲዮን ወይም የአክሲዮን የገቢያ ዋጋ በሚመለከት የህዝብ አክሲዮን ንግድ እንዳለ የሚያስመስል ሀሰተኛ ወይም አሣሣች መልክ ለመፍጠር በማሰብ፡-
o በአክሲዮን ባለቤትነት ላይ ምንም ጠቃሚ ለውጥ የማያመጣ የአክሲዮን ንግድ ያካሄደ እንደሆነ፣
o አክሲዮኖቹ በተጠየቁት ተቀራራቢ መጠን ፣ተቀራራቢ ጊዜ እና በተቀራራቢ ዋጋ በዚያው ሰው ወይም በሌላ ሰው እንደተገዛ ወይም ለዚያው ሰው ወይም ለሌላ ሰው የገዢው ጥያቄ እንደቀረበ ወይም እንደሚቀርብ እያወቀ አክሲዮኖቹን ለመግዛት ጥያቄ ያቀረበ እንደሆነ ወይም፣
o አክሲዮኖቹ በተጠየቁት ተቀራራቢ መጠን፣ተቀራራቢ ጊዜ እና ተቀራራቢ ዋጋ በዚያው ሰው ወይም በሌላ ሰው እንዲሸጡ ወይም ለዚያ ሰው ወይም ለሌላ ሰው የሽያጭ ጥያቄ እንደቀረበ ወይም እንደሚቀርብ እያወቀ አክሲዮኖችን ለመሸጥ ጥያቄ ያቀረበ እንደሆነ በቀላል እስራት ወይም ነገሩ ከባድ ሲሆን ከአምስት ዓመት በማይበልጥ ፅኑ እስራት ይቀጣል፡፡

 በአክሲዮኖች ወይም በሸቀጦች መቆመር ፡- ማንም ሰው በሀገር ውስጥም ሆነ ከአገር ውጪ የተመዘገቡ ወይምያልተመዘገቡ ኩባንያዎች ወይም ሌሎች የንግድ ድርጅቶች አክሲዮኖች ወይም ማናቸውም ዕቃዎች ወይም ሸቀጦች ዋጋቸውን ዝቅ ወይም ከፍ ማለቱን ምክንያት በማድረግ ገቢ ወይም ትርፍ ለማግኘት በማሰብ አክሲዮኖቹን ወይም ዕቃዎቹን ወይም ሸቀጦቹን የራስ የማድረግ እውነተኛ ሀሳብ ሳይኖረው እነዚህን ነገሮች የሚሸጥ ወይም የሚገዛ በማስመሰል ማናቸውንም ዓይነት ውል በፅሁፍም ሆነ በቃል ያዘጋጀ ወይም የፈረመ እንደሆነ በቀላል እስራት ወይም ነገሩ ከባድ ሲሆን ከአምስት ዓመት በማይበልጥ ፅኑ እስራት እንደሚቀጣ በአንቀፅ 695 ስር ተደንግጎ ይገኛል፡፡

 ኢንሹራንስ በሚመለከት የሚፈፀም የአታላይነት ድርጊት በወንጀል ህጉ አንቀፅ 698 መሰረት የሚያስቀጣ ሲሆን ማንም ሰው የማይገባ ብልፅግና ለራሱ ለማግኘት ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ፡-
o ኢንሹራሱን የተገባበትን አደጋ በመፍጠር ወይም
o በውል ውስጥ በተገለፀው ጥቅም ላይ ተፅዕኖ በሚያደርግ አኳኃን የኢንሹራንሱን ገንዘብ ልክ፣ የውሉን ዘመን፣ ወይም የኢንሹራንሱን ተጠቃሚዎችን የሚመለከት ፍሬ ነገር በመደበቅ፣በማሳሳት፣በማረጋገጥ ወይም ይህንኑ በሚመለከት ሀሰተኛ መግለጫ በመስጠት አንድ የኢንሹራንስ ማህበርን ካታለለ፣
o በማናቸውን ሌላ መንገድ ከኢንሹራንስ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ የአታላይነት ድርጊት ከፈፀመ በቀላል እስራት ወይም ሁኔታዎች ይበልጥ ከባድ ሲሆኑ ከአምስት ዓመት በማይበልጥ ፅኑ እስራትና ከብር ሀምሳ ሺ በማይበልጥ መቀጮ ይቀጣል፡፡

 በህዝብ እምነት በመጠቀም ማታለል፡- ማንም ሰው ለራሱ ብልፅግና ለማግኘት አስቦ መንፈስ እጠራልሃለሁ፣ጋኔን እስብልሃለሁ፣ ደንቃራ እጥልልሃለሁ፣ እጠነቁልልሃለሁ፣ ዕድልህን እነግርሃለሁ፣ ነገርን እገልፅልሃለሁ፣ ኮከብህን እቆጥርልሃለሁ፣ ህልምን እፈታልሃለሁ፣ የወደፊት ዕድልህን አውቅልሃለሁ፣ ወስጥ እጅህን አነብልሃለሁ፣ ከሞተ ሰው ጋር አነጋግርሃለሁ በማለት፣ ወይም በሰው እምነት ያለአግባብ መገልገል በሚያስችል በማናቸውም ሌላ መንገድ ሰውን ያታለለ እንደሆነ የግል አቤቱታ ሲቀርብበት አፈፃፀሙ በደንብ መተላለፍ ድንጋጌዎች የሚያስቀጣ ካለሆነ (ቀላል ካልሆነ) በቀር በመቀጮ ወይም የተደጋገመ ወንጀል በፈፀመ ጊዜ በቀላል እስራት ወይም ነገሩ ከባድ ሲሆን ከአምስት ዓመት በማይበልጥ እስራት እንደሚያስቀጣ የወንጀል ህጉ እንቀፅ 700 ይደነግጋል፡፡
በተጨማሪ ማንም ሰው ከባድ በሽታ ወይም ጉድለት አለብኝ ወይም ከፍተኛ አካላዊ ወይም ስነ- ልቦናዊ ጉዳት ወይም የገንዘብ ወይም ሌላ ማቴሪያላዊ ኪሳራደረሰብኝ በማለት የሀሰት ንግግር በማድረግ ወይም የሰዎችን ሀዘኔታ ስሜት በሚስብ በማናቸውም ሌላ የማታለል ዘዴ በመጠቀም ከግለሰብ ወይም ከሕዝብ ገንዘብ ወይም ማቴሪያላዊ ነገር የሰበሰበ እንደሆነ እንዲሁም ከላይ ከተዘረዘሩትነገሮች አንዱ በሌላ ሰው ላይ የደረሰ አስመስሎ የተባለውን ሰው ለሕዝብ በማቅረብ በመለመኛነት የተገለገለበት እንደሆነና ይህንኑ ለመርዳት ነው በማለት ከግለሰቦች ወይም ከሕዝብ ገንዘብ ወይም ማቴሪያላዊ ነገር የሰበሰበ እንደሆነ እንደነገሩ ሁኔታ በቀላል እስራት ወይም በመቀጮ ወይም ከአምስት ዓመት በማይበልጥ ፅኑ እስራት እና በመቀጮ ይቀጣል፡፡እንዲሁም ማንም ሰው በሌላ ሰው ላይ ጉዳት በማድረስ ከላይ ለተመለከተው ዓላማ የተጠቀመበት እንደሆነ ከሶስት ዓመት እስከ አስር ዓመት ለመድረስ በሚችል ጽኑ እስራት እና በገንዘብ መቀጮ ይቀጣል፡፡

በሌላ በኩል ማንም ሰው ፖለቲካዊ፣ ሃይማኖታዊ፣ ባህላዊ፣ ማህበራዊ ወይም ሰብዓዊ ጉዳዮችን ወይም ማናቸውንም ሌላ ዓላማ ምክንያት በማድረግ በህግ ወይም አግባብ ባለው ባለስልጣን ተፈቅዶለትም ሆነ ሳይፈቀድልት ከግለሰብ ወይም ከህዝብ ላይ ገንዘብ ወይም ማናቸውንም ማቴሪያላዊ ነገር ሰብስቦ ይህንኑ ገንዘብ ወይም ማቴሪያላዊ ነገር በሙሉ ሆነ በከፊል ከሰበሰበበት ዓላማ ውጪ ያለአግባብ ያዋለ እንደሆነ ገንዘብ ያለፍቃድ ስለመሰብሰብ የተመለከተው የወንጀል ህጉ አንቀፅ 862 ድንጋጌ እንደተጠበቀ ሆኖ ከአስር ዓመት በማይበልጥ ፅኑ እስራት እና ከሰላሳ ሺህ ብር በማይበልጥ መቀጮ ይቀጣል፡፡

በአጠቃላይ የሰዎችን እምነት በመጠቃም ወይም በተለያዩ ንግግሮች እና ድርጊቶች ሰዎችን በማሳሳት የገንዘብ ወይም ዋጋ ያለው ነገርን ለራስ ማድረግ በአታለይነት ወንጀል የሚያስጠይቅ ተግባር ነው፡፡ ማህበረሰቡ ንብረቱ የአታላዮች ሲሳይ እንዳይሆን በወንጀለኞች የሚደረጉ ንግግሮችን እና ድርጊቶች ከማመኑ በፊት መጠራጠር እና ቆም ብሎ ማሰብ ይኖርበታል፡፡ የበለጠም ጥቅምና ንብረቱን መጠበቅ እንዲሁም ንብረቱን ከመስጠቱ በፊት ጥንቃቄ ማድረግ ፣ ነገሮችን ማጣራትና ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ የማታለል ድርጊቶቹ ተፈጽማውሲገኙም ለሚመለከተው የህግ አካል በማቅረብ አጥፊዎች እንዲቀጡ ሌሎችም እንዲማሩ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡ ምንጭ:- በኢፌዴሪ ፍትህ ሚኒስቴር በንቃተ ህግ፣ትምህርትና ስልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ

24/11/2023

Hear both sides......

21/11/2023

የመድን ሕግ

የመድን ሕግ የመድን ውልን የሚዳኝ ሕግ ነው፡፡ የመድን ሕግ ብዙ ጥቅሞችን ያየዘና በግለሰብ ደረጃ ብቻ ሳይሆን ህብረተሰቡን ሊጠቅሙ የሚችሉ በርካታ ጉዳዮችን አካቶ የሚይዝ ነው፡፡ የመድን ውል በመድን ሰጪው (Insurer) እና በመድን ገቢው (Insured) መካከል የሚደረግ የሁለትዮሽ ውል ሲሆን መድን ሰጪው በውሉ ላይ "የተጠቀሰውን አደጋ በደረሰ ጊዜ በመድህን ገቢው ላይ የሚደርሰውን የምጣኔ ሀብት ኪሳራ በውሉ ላይ ከተጠቀሰው መጠን ሳይበልጥ የመካስ ግዴታን ሲቀበል መድን ገቢው በአንፃሩ በውሉ ላይ በተጠቀሰው ጊዜ እና መጠን የመድን መግቢያ ክፍያ (አረቦን) ለመድን ሰጪው የመክፈል ግዴታን ይወስዳል፡፡ ጉዳት የመድረስ ነገር ሲታሰብ በማንኛዉም አጋጣሚ ሊፈጠር የሚችልና ከሰው ልጅ ጋር አብሮ የሚኖር ነው፡፡ በመሆኑም በመድን ሕግ ጉዳትን አስቀድሞ እንዳይደርስ መከላከል ባይቻልም በጉዳቱ ሳቢያ የሚደርሱ የምጣኔ ሀብት ችግሮችን ለመከላከል የሚረዳ ሲሆን የተበታተነ ሀብትን በማሰባሰብ ኢንቨስትመንትና ቁጠባ እንዲያድግ ለስራ እንቅስቃሴ ከአደጋ በፊትም ሆነ በኋላ ፍርሀትንና ስጋትን ሊያስወግድ የሚያስችል በመሆኑ ጠቀሜታው የጎላ ነው፡፡ በዚህ አጭር ጽሁፍ ስለ መድን ምንነት፣ የመድን መሠረታዊ መርሆች፣ የመድን ገቢውና የመድን ሰጪው መብትና ግዴታዎችን እንዲሁም የመድንን ጠቀሜታ እንመለከታለን፡፡

የመድን ምንነት

ሃርቬይ ሩቢን ያዘጋጀው የኢንሹራንስ መዝገበ ቃላት ለመድን በሰጠው ትርጓሜ "Insurance contract is a legally binding bilateral agreement between an insured and an insurance company to indemnify the buyer of a contract underspecified circumstance in exchange for premium payment(s) the company covers Stipulated peril." ወደ አማርኛ ሲተረጎም" የመድን ውል በመድን ገቢውና በመድን ሰጪው መካከል የሚደረግ በሕግ አስገዳጅነት ያለው የሁለትዮሽ ውል ሲሆን በውሉም መድን ሰጪው ከመድን ተቀባይ ለመድን መግቢያ የሚከፈለውን ክፍያ (ዎች) እየተቀበለ በውሉ ላይ የተገለፀው አደጋ በመድን ተቀባይ ላይ በደረሰ ጊዜ የተወሰነ ገንዘብ ለመክፍል የሚደረግ ስምምነት ነው የሚል ትርጉም የሚሰጠን ይሆናል፡፡ ከዚህ ትርጓሜ መረዳት የሚቻለው የመድን ውል በመድን ገቢ እና በመድን ሰጪው (ኢንሹራንስ ኩባንያ) መካከል የሚደረግ ስምምነት ሲሆን ይህ ውል በእነዚህ ተዋዋይ ወገኖች ላይ ተነፃፃሪ መብትና ግዴታዎችን ያቋቁማል፡፡

በሀገራችንም በ1952 ዓ.ም በወጣው የኢትዮጵያ የንግድ ሕግ (የነባሩ የንግድ ሕግ 3ኛ እና 4ኛ መጽሀፍ ኢንሹራንስና ባንክን የሚመለከተው ያልተሻረ በመሆኑ) አንቀጽ 654(1) ላይ “የኢንሹራስ ውል ፖሊሲ ማለት ኢንሹራንስ ሰጪ የሚባለው በአንድ ወይም በብዙ የተመደበውን የኢንሹራንስ መግቢያ ዋጋ (ፕርምየም) ተቀብሎ በውሉ የተመለከተው አደጋ በደረሰ ጊዜ ኢንሹራንስ ለገባው ሰው የተወሰነ ገንዘብ ለመክፈል ግዴታ የሚገባበት ነው፡፡” በማለት ትርጉሙን አስቀምጧል፡፡
ከላይ የተገለፁትን ትርጉሞች መሠረት በማድረግ የምንረዳው መድን ወይም ኢንሹራንስ ማለት አንድ ሰው ባልተጠበቀ አደጋ ለመጣበት ህጋዊ የፍትሐብሔራዊ ተጠያቂነትን፣ በንብረቱ፣ በህይወቱ ወይም በአካሉ ላይ ለደረሰው ጉዳት አስቀድሞ ከኢንሹራንስ ድርጅት ጋር በገባው ስምምነት መሠረት የሚከፈለው የካሳ ክፍያ ስምምነት ማለት ነው፡፡ ይህም ማለት የኢንሹራንስ ድርጅቱ አስቀድሞ በተስማማው መሠረት የኢንሹራንስ መግቢያ ዋጋ (ፕርምየም) በመስብሰብ አደጋው በደረሰ ጊዜ ጉዳቱ ለደረሰበት ሰው ካሳ የሚከፍልበት እና ከጉዳቱ እንዲቋቋም የሚያደርግ መንገድ ነው፡፡

የመድ ውል መሠረታዊ መርሆች፡-

ኢንሹራንስ ወይም መድህን የሚመራባቸዉ መሰረታዊ መርሆዎች አሉ፡፡ እነዚህ መሰረታዊ ነገሮች ከራሳቸዉ ተጨባጭ ሁኔታ ጋር በማገናዘብ የሚመደብ ሲሆን ሊያሳካ የሚፈልገዉ የራሱን ዓላማን ይዞ የሚሔድ ይሆናል፡፡

• የላቀ ቅን ልቦና (Principle of Utmost Good Faith)፡- የመድን ውል ከሚፈልጋቸው መሰረቶች አንዱ ተዋዋይ ወገኖች በላቀ ቅን ልቦና ሆነው ውሉን የሚመለከቱ መረጃዎች በሙሉና ተገቢ በሆነ መንገድ መለዋወጥ ነው፡፡ ቅን ልቦና የሚያስፈልግበት ዋናው ምክንያት የቅን ልቦና መጓደል በተዋዋይ ወገኖች ያለዉን ግንኙነት ሊቀይርና ጉዳትን ከአንደኛዉ ወገን ወደ ሌላኛዉ ወገን ሊያስተላልፍ ስለሚችል ነው፡፡ በተለይ ኢንሹራንስ የሚገባው ተዋዋይ ወገን ለኢንሹራንስ ሰጪ ያሉትን አስፈላጊ መረጃዎች በቅንነትና በተሟላ መልክ ካልሰጠው ኢንራንስ ሰጪውን በእጅጉ ሊጎዳ ይችላል፡፡ የንግድ ሕግ ቁጥር 667 “ውሉን በሚዋዋልበት ጊዜ ተጠቃሚው የሚያውቃቸውን እና ኢንሹራንስ ሰጪው ኃላፊነት የሚወሰድባቸውን አደጋዎች ለማመዛዘን የሚያስችሉትን ማናቸውም ሁኔታዎች በትክክል መግለፅ እንዳለበት ግዴታ ይጥላል፡፡ በመሆኑም መድን ገቢው የመድን ውል በሚያደርግበት ወቅት የመድን ሽፋን እንዲሰጥለት በጠየቀበት ጉዳይ ላይ ያሉ መረጃዎችን በግልፅና በትክክል ለመድን ሰጪው ማስታወቅ ይጠበቅበታል፡፡

• መድን ለመግባት የሚያበቃ ጥቅም መኖር፡- የመድን ውል ስምምነት መድን ገቢው መድን ለመግባት የሚያበቃ ጥቅም ከሌለው እንዳልተደረገ የሚቆጠር ውል (Void Contract) ነው፡፡ የመድን ውል ስምምነት መድን ሊገባበት የሚያስችል ጥቅም መኖርን እንደ አንድ ትልቅ ሕጋዊ መስፈርት የሚጠይቅ ነው፡፡ መድን ለመግባት የሚያበቃ ጥቅም የመኖር ዋና ዓላማ የአንድ ንብረት ባለቤት ያልሆነ ሰው በዚህ ንብረት ላይ አደጋ በደረሰ ጊዜ የካሳ ክፍያ እንዲከፈለው ጥያቄ እንዳያቀርብ ወይም እንዳይከፈለው ወይም ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት የሚንቀሳቀሱትን ለመቆጣጠር ነው፡፡

• የጉዳት ካሳ መርህ /principle of Indeminity/፡- የመድን ውል ስምምነት የመድን ሽፋን በተሰጠባቸው አደጋዎች ምክንያት የሚደርስን የገንዘብ ጉዳት ለመተካት የሚደረግ የውል ዓይነት ነው፡፡ ይህም በአደጋ ሳቢያ የሚከሰተውን የንብረት ውድመት ወይም የገንዘብ ክስረት የመካስና በተቻለ መጠን ቀድሞ ወደ ነበረበት የመመለስ ተግባር ነው፡፡ መድን ለገባ ሰው ሊከፈለው የሚችለዉ በጉዳቱ መጠን ልክ ብቻ እንደመሆኑ ጉዳት ከሌለ ምንም አይነት የሚከፈል ነገር አይኖርም ማለት ነው፡፡ የሰው ልጅ ጤንነትን ወይም አካልን በተመለከተ በገንዘብ ተምኖ ለማስቀመጥ የሚቻል ባለመሆኑ የካሳው መጠን ኢንሹራንስ ገቢው ከኢንሹራንስ ሰጪው ጋር ተስማምተው በገቡት ውል መሰረት የሚፈፀም ይሆናል፡፡

የመድን ገቢው እና የመድን ሰጪው መብትና ግዴታዎች

በመድን ውል ውስጥ የመድን ገቢው እና የመድን ሰጪው ከሕግና ከውል የሚመነጩ መብቶችና ግዴታዎች አሏቸው፡፡

የመድን ሰጪው መብቶች

መድን ሰጪው በዋናነት ሁለት መብቶች ያሉት ሲሆን እነዚህም በውሉ መሠረት ሊከፈል የሚገባውን የመድን አረቦን ከመድን ገቢው መቀበል እና የመዳራግ መብት (right of subrogation) ናቸው፡:
የመዳረግ መብት የቃሉ ትርጓሜ በንግድ ሕጉ ድንጋጌዎች ያልተገለፀ ቢሆንም አንዳንድ ምሁራን እንደሚያስረዱት የመዳረግ መብት ማለት መድን ሰጪው በሌላ 3ኛ ወገን ጥፋት ምክንያት በመድን ገቢው ላይ ለደረሰው ምጣኔ ሀብታዊ ኪሳራ ወይም እጦት ተገቢውን ካሳ ከከፈለ በኋላ በመድን ገቢው እግር በመተካት ትክክለኛውን አጥፊ በመክሰስ ለመድን ገቢው የከፈለውን ካሳ (ገንዘብ) በከፊል ወይም በሙሉ የሚያስመልስበት የሕግ መርህ ነው፡፡

የመድን ሰጪው ግዴታዎች

መድን ሰጪ ውሉ ከተፈረመበት ጊዜ ጀምሮ ለደረሰው አደጋ ወይም ለተስማሙበት ሁኔታ መድን እየሰጠ መቆየቱ አንዱ ግዴታው ሲሆን የተፈራው አደጋ በደረሰ ጊዜ በስምምነቱ መሰረት ካሳ የመክፍል ግዴታ አለበት፡፡ (የአትዮጵያ የንግድ ሕግ ቁጥር 663(1) እና ቁጥር 665(1)) ሥር ተደንግጎ ይገኛል)

የመድን ገቢው መብት

ውሉ ከተፈረመበት ጊዜ ጀምሮ የመድን መግቢያ ክፍያውን በተገቢው ጊዜ እየከፈለ የቆየ እና የተፈራው አደጋ ወይም ሁኔታ መድረሱን ሕጉ ባስቀመጠው ጊዜ ለመድን ሰጭው የገለፀ መድን ገቢ በመድን ውሉ ላይ የተገለፀውን ካሣ የመቀበል መብት አለው፡፡ ይህን ከንግድ ሕጉ ቁጥር 663(1) እና ቁጥር 665(1) መረዳት ይቻላል፡፡ ሌላው ደግሞ የመድን ሽፋን የተሰጠው ንብረት በተላለፈ ጊዜ የሚኖር የመድን መብት አንዱ ሲሆን በሕጉ ቁጥር 673 እና ተከታዮቹ ተደንግጎ እናገኘዋለን፡፡

የመድን ገቢው ግዴታዎች

ስለ መድን ገቢው ግዴታዎች ሲታሰብ በቅድሚያ ወደ ኅሊናችን የሚመጣው በውሉ ውስጥ በመድን ሰጪው ሊከፍለው የተስማማው አረቦን በውሉ ላይ በተጠቀሰው መጠን እና ጊዜ የመክፈል ግዴታ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ አደጋው በተከሰተ ጊዜም የመድን ሽፋን የተሰጠው አደጋ መከሰቱን በተቀመጠው ጊዜ ለመድን ሰጪው የማሳወቅ እና የአደጋውን መመዘኛ ፍሬ ነገሮች በዝርዝር የመግለፅ ግዴታ አለበት፡፡

የመድን አስፈላጊነትና ጠቀሜታ

መድን ወይም ኢንሹራንስ እጅግ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታዎች አሉት፡፡ ከነዚህ ጠቀሜታዎቹ ውስጥ አንደኛው በአንድ ሰው ላይ የሚደርስን የፍትሐብሔራዊ ተጠያቂነትን፣ የንብረት ጉዳትን፣ ሞትን ወይም የአካል ጉዳትን መሠረት የሚደርስን የኢኮኖሚያዊ ኪሳራን በካሳ መልክ የኢንሹራንስ ድርጅቱ ስለሚከፍለው በተቻለ መጠን ኢንሹራንስ ገቢው ወይም ጉዳቱ ሞት ከሆነ የኢንሹራንስ ተጠቃሚ የሆነ ሰው ጉዳቱ ሳይደርስ ወደነበረበት የምጣኔ ሀብታዊ አቅሙ መመለስ ማስቻሉ ነው፡፡ ይህ በመሆኑም ጉዳት አድራሹ ወይም ጉዳት የደረሰበት ሰው የከፋ ኪሳራና አዘቅት ውስጥ እዳይገባ የሚያደርግ እና ማህበረሰቡም ከጉዳቱ በላይ በጉዳቱ ምክንያት ለሚከሰት የምጣኔ ሀብታዊ ቀውስ እንዳይዳረግ ያደርጋል፡፡

በሁለተኛነት ሊጠቀስ የሚችለው የመድን ጠቀሜታው የመድን ድርጅቶቹ ጉዳትን በተመጣጠነ ሁኔታ ማከፋፈላቸው ነው፡፡ ይህም ማለት የኢንሹራንስ ድርጅቶቹ ተመሳሳይ የጉዳት ስጋት ካለባቸው ሰዎች ተመጣጣኝ የኢንሹራንስ መግቢያ ዋጋ (ፕርምየም) በመሰብሰብ ጉዳት ለደረሰበት ሰው ካሳ ይከፍላሉ፡፡

በአጠቃላይ መድን የአደጋ ውጤት የሆነውን ኪሳራና ስጋት በማስወገድ በአደጋ ምክንያት የሚከሰቱ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ችግሮችን ለመቀነስ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያበረክታል፡፡ በመሆኑ መድን ገቢም ሆነ መድን ሰጪው ሕግን መሰረት አድርገው በቅን ልቦና ሊሰሩ ይገባል፡፡
በንቃተ ህግ ትምህርትና ስልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ

21/11/2023

ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ተገልጋዮች ጥራቱን የጠበቀ ፈጣን አገልግሎት እንዲያገኙ በቴክኖሎጂ የተደገፈ ከብልሹ አሰራር የፀዳ እንዲሆን ጥረት እየተደረገ ይገኛል፡፡
ይህንን ጥረት ከግብ ለማድረስ ተገልጋዮች ስለሚፈልጉት አገልግሎት እና ማሟላት ስላለባቸው መስፍርቶች በቂ መረጃ እንዲኖራቸው ያስፈልጋል፡፡
ለዚህም ግንዛቤ የሚያስጨብጡ ጠቃሚ መረጃዎችን በተከታታይ በዚሁ ገጽ ላይ የምናስተላልፍ ይሆናል ፡፡
ክቡራን ተገልጋዮቻችን መረጃዎችን ለሌሎች እንዲደርስ ሼር በማድረግ ዜጎችን ከእንግልትና ከሙስና እንዲታደጉ በማክበር እንጠይቃለን፡፡
ውልና ማስረጃ ምን አለ❓https://t.me/EntrustConsultant
በየትኛውም ቦታ ሁነው ሰነዶች ማረጋገጫ(ውልና ማስረጃ) ጉዳይ አላችሁ❓
👉ውክልና
👉 ብድር ውል
👉 የሺያጭ ውል
👉ቃለ ጉባዔ
👉ሼር መግዛት /መሸጥ........ወ.ዘ.ተ
ሌሎችንም አገልግሎት በአካል መገኘት ሳይጠበቅብዎች በአሉበት ቦታ ሁነው መረጃውን ይሰጡና በባለሙያ ተፅፎ በቴሌግራም፣ ዋትስአፕ ወይም በኢሜል ይላክላችኋል።
ከእናንተ የሚጠበቀው ፕሪንት አድርጎ ወደ አቅራቢያ ሰነዶች ማረጋገጫ በመሄድ ምን ጊዜ ሳያባክኑ አገልግሎት ማግኘት ብቻ።
ስለ አስፈላጊ ሰነድ መረጃ በነፃ ይገኛሉ።
ይደውሉ:- 0909039999
የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት (ውልና ማስረጃ) ሲፈልጉ
Emails:-
[email protected]
[email protected]
[email protected]

India, New Delia
21/11/2023

India, New Delia

19/11/2023
17/11/2023

የስርቆት እና የመሸሸግ ወንጀሎች ተጠያቂነት

ስርቆት በተንቀሳቃሽ ንብረት ላይ ከሚፈፀሙ ወንጀሎች መካከል በስፋት የሚፈፀምና በርካቶች ንብረታቸውን እንዲያጡ የሚያደርግ የወንጀል ተግባር ነው፡፡ ይህ ድርጊት በሀገራችን የወንጀል ህግ በወንጀል የሚያስጠይቅ ከመሆኑም በተጨማሪ በስርቆት የተገኘን ንብረት መሸሸግም በተመሳሳይ ተጠያቂነት ያስከትላል፡፡ በዚህ አጭር ፅሁፍ የስርቆት እና የመሸሸግ ወንጀሎችን ምንነትና የሚያስከትሉትን የወንጀል ተጠያቂነት እንመለከታለን፡፡

የስርቆት ወንጀል ምንነት

በወንጀል ህግ አንቀጽ 665 መሰረት ስርቆት ማለት የማይገባን ብልፅግና ለማግኘት ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ የሌላ ሰው ንብረት የሆነውን ተንቀሳቃሽ እቃ ወይም ከማይንቀሳቀስ ንብረት የተነጠለን እቃ አንስቶ መውሰድ፣ በቀጥታ የራስ ንብረት ማድረግ ወይም በተዘዋዋሪ ከራስ ንብረት ጋር እንዲቀላቀል ማድረግ ነው፡፡

የስርቆት ወንጀል የሚያስከትለው ቅጣት

በወንጀል ህግ አንቀጽ 665 መሰረት ማንም ሰው የማይገባን ብልፅግና ለማግኘት ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ የሌላ ሰው ንብረት የሆነውን ተንቀሳቃሽ እቃ ወይም ከማይንቀሳቀስ ንብረት የተነጠለን እቃ አንስቶ የወሰደ፣ በቀጥታ የራሱ ንብረት ያደረገ ወይም በተዘዋዋሪ ከራሱ ንብረት ጋር እንዲቀላቀል ያደረገ እንደሆነ እንደነገሩ ሁኔታ በቀላል እስራት ወይም ከአምስት አመት በማይበልጥ ፅኑ እስራት ይቀጣል፡፡ ቀላል አስራት ሲባል በወንጀል ህጉ ጠቅላላ ክፍል በአንቀጽ 106 እንደተደነገገው ከ10 ቀን እስከ ሶስት አመት በልዩ ሁኔታ ደግሞ እስከ አምስት አመት የሚደርስ ቀላል እስራት ነው፡፡

ይህ የስርቆት ወንጀል የተፈፀመው ተንቀሳቃሹን ዕቃ ሰራቂው እራሱ ከማይንቀሳቀስ ንብረት ላይ ነጥሎ በመውሰደው ከሆነ ወይም በወንጀሉ ምክንያት በተንቀሳቃሹ ወይም በማይንቀሳቀሰው ንብረት ላይ ጉዳት በማድረስ ከሆነ ከስርቆት ወንጀሉ በተጨማሪ በወንጀል ህጉ አንቀጽ 689 እስከ 691 በተደነገገው በንብረት ላይ ጉዳት በማድረስ ወንጀል በተደራቢነት በተጨማሪነት ይጠየቃል፡፡
በተጨማሪም በህጉ አንቀጽ 667 መሰረት በጋራ ንብረት፣ የሽርክና ወይም በወራሽነት ምክንያት የጋራ ሀብት በሆነ ንብረት ላይ የሚፈፀም የስርቆት ወንጀል የግል አቤቱታ ሲቀርብበት በቀላል እስራት ወይም በመቀጮ የሚያስቀጣ ነው፡፡

የስርቆት ወንጀል በህይወት ባለ ሰው ላይ ብቻ ሳይሆን በሞተ ሰው ላይም ሊፈፀም ይችላል፡፡ በዚሁ መሰረት በወንጀል ህጉ አንቀጽ 668 መሰረት ማንም ሰው ተገቢ ያልሆነ ብልፅግናን ለራሱ ለማግኘት ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ ከሙታን መቃብር ላይ ወይም ከመቃብር ቤት ውስጥ ወይም ከተቀበረ ወይም ካልተቀበረ አስከሬን ላይ እቃ የወሰደ እንደሆነ እንደ ወንጀሉ አፈፃፀም በቀላል እስራት ወይም ከአምስት አመት በማይበልጥ ፅኑ እስራት ያስቀጣል፡፡

ከላይ ያነሳነው የስርቆት ወንጀል በመደበኛው ሁኔታ ሲፈፀም ስለሚኖር የህግ ተጠያቂነት ነው፡፡ ከዚህ በከበደ መልኩ የስርቆት ወንጀል በተለየ አደረጃጀት እና በተጠና ሁኔታ ሲፈፀም ወንጀሉ ከባድ የሚሆንበትን ሁኔታ በወንጀል ህጉ አንቀጽ 669 በዝርዝር ድንግጎ ይገኛል፡፡ በዚሁ መሰረት እንደወንጀሉ ክብደት እና በተሰረቀው እቃ አይነትና በአሰራረቁ አይነት ወዘተ ቅጣቱ የሚከብድ ይሆናል፡፡ እንደሚከተለው በዝርዝር እንመለከተዋለን፡፡

1. ወንጀሉ የሚመለከታቸው፡-

• የተሰረቀው እቃ የሀይማኖት ሥርአት የሚፈፀምበት ስፍራ ውስጥ የሚገኝ የሀይማኖት እቃ፣ በቤተመዘክር ውስጥ የተቀመጠ እቃ፣ ለህዝብ ክፍት በሆነ ህንጻ ውስጥ የተቀመጠ ሳይንሳዊ፣ ኪነጠበባዊ ወይም ታሪካዊ ዋጋ ያለው እቃ ከሆነ
• የተለየ ጥበቃ የሌለው እንሰሳ ወይም ሰብል ወይም ቴሌኮሚኒኬሽን፣ የኤሌክትሪክ ሀይል፣ ለውሃና ፍሻስ ወይም ለማንኛም ሌላ ድርጅት አገልግሎት የሚውል ጠባቂ የሌለው መሳሪያ ወይም እቃ ወይም እንዲቀመጥ ወይም እንዲላክ ለእቃ ማከማቻ ፣ ለአንድ ድርጅት ወይም የመንግስት መስሪያ ቤት በተለይም ለፖስታ ቤት ወይም ለማመላለሻ ድርጅት የተሰጠ ሸቀጥ ወይም እቃ እንደሆነ

2. ወንጀል የተፈፀመበት ሁኔታ፡-

• የመከላከያ ሰራዊት አባል ሆኖ ወንጀሉን የፈፀመው በጓደኞቹ ወይም በአለቆቹ ላይ ሲሆን ወይም የተሰረቀው እቃ ሰራዊቱን የሚያገለግል ሲሆን ወይም እንዲያገለግል የተመደበ ሲሆን
• የመንግስት ሰራተኛ ወይም አንድ የንግድና ይህን የመሳሰሉ ልዩ ሥራ የሚያከናውን ሰው የባንክ ሰራተኛ፣ ጠበቃ፣ ውል አዋዋይ፣ ወኪል፣ የተሰጠውን የንግድ ሥራ እያከናወነ የሚገኝ የንግድ ሥራ አስኪያጅ ሆኖ ድርጊቱን የፈፀመው በተለይ በተሰጠው ስልጣን ምክንያት በእጁ በገባው የመንግስት፣ የህዝብ ወይም የግል ንብረት ላይ ሲሆን
• በሆቴል፣ የቤት አከራይ፣ እቃ አመላላሽ፣ ተሸካሚ ወይም ይህን የመሳሰለ ሥራ የሚያካሂድ ሆኖ የተሰረቀው ንብረት የደንበኛው ሲሆን፣
• የቤት ሰራተኛ፣ ሰራተኛ ወይም ሥራ ለማጅ ሆኖ ሥራውን ምክንያት በማድረግ በአሳዳሪው ወይም በአሰሪው ላይ ጉዳት በሚያደርስ ሁኔታ ሲሆን

3. ወንጀል አድራጊው፡-

• በሰዎች ወይም ንብረት ላይ ወንጀል ለመፈፀም የተቋቋመ ቡድን አባል ሲሆን
• ስርቆቱን የፈፀመው በተለይ አደገኛ መሆኑን በሚያሳይ በማናቸውም ሌላ ሁኔታ ይልቁንም የማጥቂያ ወይም የመከላከያ የጦር መሳሪያ ወይም የቤት መሰርሰሪያ በመያዝ ሲሆን፣ ወይም በሌሊት ወይም ቅጥር በመጣስ፣ አጥር በመዝለል፣ በር በመስበር፣ ግድግዳ በመሰርሰር፣ በቡድን በመሆን ሲሆን ወይም ያልተጠበቀ አደገኛ ሁኔታን፣ የህዝብ ብጥብጥን ወይም መቅሰፍትን ይልቁንም እንደግርግር፣ ቃጠሎ፣ ጎርፍ፣ ማእበል የመሳሰለውን ሽፋን በማድረግ የተፈፀመ ሲሆን
ድርጊቱ ከባድ የስርቆት ወንጀል የሚሆን ሲሆን ቅጣቱም እንደ ወንጀሉ አፈፃፀም ከአንድ አመት የማያንስ ቀላል እስራት ወይም ከአስራ አምስት ዓመት የማይበልጥ ፅኑ እስራት ይሆናል፡፡

የመሸሸግ ወንጀል ምንነት

በአንፃሩ በወንጀል ህጉ አንቀጽ 682 መሰረት የስርቆት ወንጀል ማለት በንብረት ላይ በተፈፀመ ወንጀል የተገኘን ንብረት መሆኑን እያወቁ ይህንኑ እቃ መግዛት፣ በተውሶ፣ በስጦታ ወይም በመያዣነት መቀበል፣ በመሰል አኳኋን መውሰድ፣ መገልገል፣ ማስቀመጥ፣ መደበቅ፣ አሳልፎ መሸጥ፣ በመሸጥ መለወጡ ውስጥ አገናኝ ሆኖ መርዳት፣ በስርቆት ወንጀል በተገኘው እቃ ምትክ በልዋጩ የተገኘን ወይም በሽያጩ ዋጋ የተገዛን ሌላ ነገር ወይም ጥሬ ገንዘብ መቀበል ነው፡፡

የመሸሸግ ወንጀል የሚያስከትለው ቅጣት

በወንጀል ህጉ አንቀጽ 682 መሰረት ማንም ሰው በንብረት ላይ በተፈፀመ ወንጀል የተገኘን ንብረት መሆኑን እያወቀ ይህንኑ እቃ የገዛ፣ በተውሶ፣ በስጦታ፣ በመያዣነት የተቀበለ፣ በመሰል አኳኋን፣ የወሰደ፣ የተገለገለ፣ ያስቀመጠ፣ የደበቀ፣ አሳልፎ የሸጠ፣ በመሸጥ መለወጡ ውስጥ አገናኝ ሆኖ የረዳ፣ በወንጀል ተግባር በተገኘው እቃ ምትክ በልዋጩ የተገኘን ወይም በሽያጩ ዋጋ የተገዛውን ሌላ ነገር ወይም ጥሬ ገንዘብ ተቀብሎ ከላይ የተገለፁትን ድርጊቶች ከፈፀመ እንደ ወንጀሉ አፈፃፀም በቀላል አስራት ወይም ነገሩ ከባድ ሲሆን ከአምስት ዓመት በማይበልጥ ፅኑ እስራትና በመቀጮ ያስቀጣል፡፡

የመሸሸግ ድርጊቱ የተፈፀመው በቸልተኝነት ከሆነ ከአንድ አመት በማይበልጥ ቀላል እስራት ያስቀጣል፡፡ የመሸሸግ ወንጀሉ በተደራጀ ቡድን ሲፈፀም፣ የንግድ ሥራ ፈቃድን እንደሽፋን በመጠቀም ከሆነ፣ ንብረቱን የሸሸገው፣ የውንብድና፣ የዘረፋ፣ የቅሚያ፣ የማስፈራራት ፍሬ ወይም እቃው ከመከላከያ ሰራዊት ንብረት ወይም ከመንግስት ሀብት ውስጥ መሆኑን እያወቀ ከሆነ በህጉ አንቀጽ 683 መሰረት የእስራት ቅጣቱ እስከ አስራ አምስት ዓመት ፅኑ እስራት መቀጮውም እስከ ብር ሃያ ሺህ የሚደርስ ይሆናል፡፡

የስርቆት ሆነ የመሸሸግ ወንጀሎች ከባህል፣ ከሞራል፣ ከእምነት እና ከህግ ተቃራኒ የሆኑ ድርጊቶች ናቸው፡፡ በመሆኑም ማህበረሰቡ እራሱን ከወንጀሎቹ ማቀብ፣ ልጆቹን በሥነ ምግባር ማሳደግ እና ለፍትህ ሂደቱ የበኩሉን እርዳታ ማድረግ የሚጠበቅበት ሲሆን የፍትህ አካላትም ወንጀሎቹን በመከላከል እና አጥፊዎች ተጠያቂ እንዲሆኑ በማድረግ ሀላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባል፡፡

በንቃተ ህግ ትምህርትና ስልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ

Address

Addis Ababa

Telephone

+251912356800

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Negesse Asnake Law Office posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to Negesse Asnake Law Office:

Share